Translate

Thursday, June 6, 2013

ወያኔ የፈጠረዉ የፍርሀት ድባብ ሲሰበር . . .


በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚደርሰዉ በደልና መከራ ወለደን ብለዉ ለትግል ጫካ የገቡት ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች አዲስ አበባ ገብተዉ ከተደላደሉ በኋላ በህዝብ መብትና ነጻነት፤ በአገር አንድነትና በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ህዝብ ብሄራዊ ጥቆሞች ላይ ይህ ነዉ ተብሎ ሊነገር የማይችልና ከእነሱ በፊት ከነበሩት መንግስታት ጋር ሲተያይ እጅግ በጣም የከፋ በደል ፈጽመዋል እየፈጸሙም ይገኛሉ። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች አዲስ አበባ ገብተዉ የኢትዮጵያን መንበረ ስልጣን ከመቆጣጠራቸዉ በፊት ዕቅድ አዉጥተዉና ተዘጋጅተዉ የመጡት የኢትዮጵያን ህዝብ በዘር፤ በሐይማኖትና በክልል በመከፋፈል በጠመንጃ ኃይል የያዙት ስልጣን በግዜና በህገመንግስት ያልተገደበ መሆኑን ለማረጋገጥና የእኛ ነዉ ለሚሉት የህብረሰተብ ክፍልና ለሚተባበሯቸዉ ሆዳሞች ተቆጥሮ የማያልቅ ሀብት ማጋበስ የሚችሉበትን መንገድ ለመፍጠር ነዉ። የወያኔ መሪዎች ይህንን አገራዊ በደል ያለምንም ተቃዉሞ መፈጸም እንዲችሉ ከአገሩ ይልቅ የተወለደበትን ክልል ብቻ፤ ከብሔራዊ አንድነቱና አጋራዊ ጥቅሙ ይልቅ የራሱን ጥቅም ብቻ የሚመለከትና የእነሱን ኃይለኝነትና የተለየ ጀግንነት እየሰበከ የሚኖር በፍርሀት የተሸበበ ፈሪ ትዉልድ ለመፍጠር ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል።
የወያኔ ክፋት፤ ዘረኝነትና “ልማት” በሚል ሽፋን የተደበቀ አገር የማፍረስ ሴራ ከወዲሁ የገባቸዉ የኢትዮጵያ የቁርጥ ልጆች ከ1997ቱ ምርጫ በፊትም ሆነ በኋላ የወያኔን ገመና ለማጋለጥና የኢትዮጵያ ህዝብ ለመብቱ፤ ለነጻነቱና ለእኩልነቱ እንዲታገል ለማድረግ እንደሻማ እየቀለጡ ብርሀን ሆነዉ አልፈዋል።
ይህ የዕልፍ አዕላፋት የትግል መስዋእትነትና ምሳሌነት ፍሬ እያፈራ መጥቶ በላፈዉ እሁድ ግንቦት 25 ቀን የተካሄደዉንና ወያኔ ከሃያ አመታት በላይ ሲቋጥር የከረመዉን የፍርሀት መቀነት የበጠሰ እጅግ በጣም የሚያበረታታ ትዕይንተ ህዝብ እንዲደረግ አስተዋጽኦ እድርጓል፡፡ ይህ ባለፈዉ እሁድ የተካሄደዉ ሰላማዊ ሰልፍ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያስተባብሩት፤ አቅጣጫ የሚያሳዩትና ጉያዉ ዉስጥ ገብተዉ እያበረታቱ የሚመሩት መሪዎችን ካገኘ እንኳን ምንም አይነት ህዝባዊ መሠረት የሌለዉን ወያኔን የመሰለ ፀረ ህዝብ ሃይል ቀርቶ ለማንም የማይበገር ህዝብ መሆኑን ያስመሰከረ ሰልፍ ነዉ።
በሰማያዊ ፓርቲ የተጠራዉና የብዙ ኢትዮጵያዉያንን ይሁንታ ያገኘዉ የእሁዱ ሰላማዊ ሰልፍ ወያኔ ያስረናል ወይም ይገድለናል እየተባለ አላግባብ እየተፈራ በቀጠሮ ሲተላለፍ የቆየዉን ህዝባዊ ትግል ከፍርሀትና እንደ ገመድ ከረዘመ ቀጠሮ ዉስጥ በጣጥሶ ያወጣና የህዝብን የትግል መንፈስ ያነቃቃ ሰላማዊ ሰልፍ እንደነበር በሰልፉ ላይ የታየዉ የህዝብ ስሜትና ለኢትዮጵያ ህዝብ የተላለፉት መልዕክቶች በግልጽ ይናገራሉ። ባለፈዉ እሁድ በተደረገዉ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የታየዉ ህዝብዊ መነሳሳት ሊበረታታ የሚገባዉና እንዲሁም በአገር ዉስጥና በዉጭ አገር የሚገኙ ኢትዮጵየዉያን የመብትና የነጻነት ትግላቸዉ አካል አድርገዉ ሊቀላቀሉት፤ ሊረዱት፤ሊተባሩትና ህዝባዊ ትግሉ የሚጠይቁዉን አመራር ሊሰጡት የሚገባ እጅግ በጣም አበራታች ጅምር ነዉ። ለትግልና ለመስዋዕትነት ዝግጁ የሆነዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ያጣዉ መሪ ነዉ እያልን አግባብ የሌለዉ ጩከት ከመጮህ ይልቅ አገራችንን የምንወድ የኢትዮጵያ ልጆች ሁሉ መሪዎችን በትግል ሂደት ዉስጥ የምንፈጥረዉ እኛዉ እራሳችን መሆናችንን ተረድተን ይህንን የሚያበረታታ ተስፋ የሰጠንን ሰላማዊ ሰልፍ የምናጠናክርበትንና ተከታታይነት ኖሮት ብዙ የህብረተሰብ ክፍሎችን የሚያካትትበትን መንገድ ልንቀይስ ይገባል።
የኢትዮጵያ ህዝብ አሁንም ቢሆን ለመብቱ፤ለነጻነቱና ለአንድነቱ ማናቸውንም አይነት መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆኑን ባለፈዉ እሁድ በግልጽ አሳይቷል። አሁን የሚቀረዉ ህዝባዊ ትግሉን የመምራት ታሪካዊ ሀላፊነት የወደቀበት የህብረተሰብ ክፍል ጨርቄን ማቄን ማለቱን ትቶ ወቅቱ የሚፈልገዉን የትግል አመራር መስጠት ብቻ ነዉ።
ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ አንዴ የታጠቀዉን ጠመንጃ በመጠቀም ሌላ ግዜ ደግሞ ፓርላማዉንና የህግ ተቋሞችን ተጠቅሞ ተቃዋሚ ኃይሎችን የሚያጠፋ ህግ በማዉጣት የኢትዮጵያን ህዝብ የፍትህና የነጻነት ፍላጎት ለማፈን ብዙ ጥሯል፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ እራሱን “ተራሮችን ያንቀጠቀጠ” ትዉልድ ብሎ በመጥራት ህዘብ በፍርሃት ጨለማ ዉስጥ እንዲኖር ለማድረግ ብዙ ታግሏል። ቆራጡ የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ስድቡን፤ ንቀቱን፤ እስራቱን፤ግድያዉንና ስደቱን እንዳመጣጡ መክቶ በፍርሀት ዉስጥ የማይኖር ህዝብ መሆኑን ባለፈዉ እሁድ ለወዳጁም ለጠላቱም በግልጽ አሳይቷል። ይህ እሁድ ግንቦት 25 ቀን 2005 ዓም አዲስ አበባ ዉስጥ የታየዉ የትግል መነሳሳት ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍሎች በማቀፍ ወያኔና በጠመንጃ ኃይል የመሰረተዉ ዘረኛ ስርአቱ እስከተወገዱና ኢትዮጵያ ፍትህ፤ ነጻነትን ዲሞክራሲ የነገሱባት ምድር እስክትሆን ድረስ መቀጠል ይኖርበታል፤ ይህንን ለማድረግ ደግሞ በአገር ዉስጥና በዉጭ አገር የሚኖረዉ ኢትዮጵያዊ እንደ አንድ ሰዉ ቆሞ መታገል ይኖርበታል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments:

Post a Comment