Translate

Thursday, June 6, 2013

“ይህ መንግሥት አይመጥነንም” የ“ምርቃና” መግለጫ ለኢህአዴግ ድንጋጤ

shemelis2-

ሰሞኑን ኢትዮጵያ የዓለም መገናኛ አጀንዳ ሆናለች። ለዘመናት እጇን ኢትዮጵያ ላይ ተክላ የኖረችው ግብጽ የምትዝተው ዛቻና፣ በቅርቡ ተቋቁሞ ታላቅ ታሪክ በማስመዝገቡ የተረጋገጠለት ሰማያዊ ፓርቲ ያዘጋጀው ሰላማዊ ሰልፍ አጀንዳዎቹ ናቸው።

በወጣት አመራሮች የተገነባውና በርካታ ሴት አባላት እንዳሉት የሚነገርለት ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ በዋናነት የተገኘው ድል የፍርሃት ደመና መገፈፉ ነው። አቶ መለስ ባስተላለፉት ትዕዛዝ በ1997 ዓ.ም ዜጎች አልመው በሚተኩሱ የአጋዚና ታማኝ የህወሃት አባሎች ደረትና አናታቸው እየተወጋ እንዲገደሉ ከተደረገ በኋላ የተቃውሞ ሰልፍ የማይታሰብ ሆኖ ላላፉት ስምንት ዓመታት ቆይቶ ነበር።
ከዳር እስከዳር ድምጽ አልባ ሆኖ የተሸነፈው ኢህአዴግ በጠመንጃ ፣ በወቅቱ የነበሩት የቅንጅት አመራሮች ታሪካዊና ሊረሳ የማይችል ስህተት ተዳምረው የህዝቡን ቅስም የሰበረው የ1997 ዓ ም ምርጫ ጣጣውና ቆፈኑ እንዲሁ በቀላሉ የሚለቅ እንዳልሆነ በወቅቱ አስተያየት ተሰጥቶ ነበር።
“ሁለት አስርት ዓመታት ወደኋላ ተመልሰናል” ተብሎ የተዘጋውን በር የበረገደው ሰማያዊ ፓርቲ ከህዝብ ባገኘው ድጋፍ አዲስ አበባን የተቃውሞ ጎርፍ አጎረፈባት። ሰላማዊ ሰልፉ ሰላማዊና የተሳካ እንደነበር ኢህአዴግ ራሱ ተናገረ። ህዝብ ተቃውሞውን ገልጾ የሶስት ወር ጊዜ ከሰጠ በኋላ ወደ ቤቱ ተመለሰ።
አዲስ አበባ አንድ ለአምስት፣ የጎንዮሽ፣ የሽቅብ፣ የህቡዕ፣ የገሃድ፣ የዘር፤ የታማኞች፣ የበጣም ታማኞች፣ የልማት፣ የአነስተኛ ስራ ፈጠራ፣ የጾታ፣ የዘር፣ የእድሜ፣ የተፈጥሮ ሁኔታ፣ የጥቅም ወዘተ የፈጠረው አደረጃጀት አፈር ድሜ መብላቱ ያስጨነቀው ኢህአዴግ ሰልፉ ተበትኖ ሲያበቃ ላንቃውን አላቀቀ።
እንደ ገበጣ ጠጠር በፈለገበት ጉድጓድ የሚወረውራቸውን ቅምጥ አሽከሮች ለመግለጫ አሰማራ። ለስምንት ዓመታት ታፍኖ የኖረ ህዝብ መቦረቁ አስደነገጠውና ከፊልም ክምችት ህግ መዝዞ ለመክሰስ ያመች ዘንድ ህጸጽ እንዲነቀስ አዘዘ። አቶ ሽመልስ ከፈረሹበት ፍራሽ ተነስተው በምርቃና የአፋቸውን ለሃጭ እንኳን በወጉ መቆጣጠር እያቃታቸው በሉ የተባሉትን ተፉ። አቶ ሬድዋንም ሰው በሌለበት የ2002 ምርጫ በስድብ አቶ መለስን በማስደሰታቸው ባገኙት ሃላፊነት ለጌቶቻቸው ምላስ ሆነው ህዝብ አወገዙ። እሳቸውም ተፉ።
አይ ጋዜጠኛነት – “አትነሳም ወይ”   
አንድ ህዝብ ለተቃውሞ ሲወጣ ሊያወግዝ፣ ሊዘልፍ፣ የፈለገውን ጉዳይ በማንሳት ሊራገም፣ ለተነሳበት ጉዳይ “ተነሱ” ብሎ በፍርሃትና ሚና ባለመለየት የተቀመጡትን ለመቀስቀስ፣ ለማበረታታት ነው። ከድሮ ጀምሮ አገርና ህዝብ እንዲተባበሩ ሲፈለግ፣ መሪዎች ሲገዝቱ በሠንደቅዓላማና የሁሉም ማተብ የሆነችውን አገር ስም በመጥራት ቅስቀሳ እንደሚያደርጉ የሚታወቅ ነው። ኢህአዴግም ቢሆን በጨነቀው ጊዜ ባወገዘውና በሚጠላው ሠንደቅ ሲነግድበት ታይቷል። አቶ መለስ “ጨርቅ” ብለው ባዋረዱት “ባንዲራ” እንዲገነዙ የፈቀደ ፓርቲም ነው። ታዲያ ከጥንት ጀምሮ ሰንደቅ ዓላማውን “ማተቤ” እያለ የሚጠራ ህዝብ የሰንደቁን flagስም እየጠራ “አትነሳም ወይ” በማለት ማዜሙ እንዴት ይበዛበታል? ደግሞስ ኢህአዴግና በዙሪያው የሰበሰባቸው አሽከር ባለስልጣኖቹ ስለ ሰንደቅ ክብር የመቆርቆር ሞራሉስ አላቸው?
ኢህአዴግን “ውሸትህ ሰለቸን” እያሉ ሲረግሙት ከነበሩት በመቶ ሺዎች ከሚቆጠሩ ሰዎች መካከል “ለምን አዲሱን ሰንደቅ ዓላማ ያዝክ” በሚል የሚጨቃጨቁ አስር የማይሞሉ ሰዎች በካሜራ አድኖ ሰልፉን “ህገ ወጥ” ለማስመሰል የዳዳው ጋዜጠኛ ሙያውንም ሆነ ራሱን ስለማርከሱ ጉልህ ማሳያ የሚነሳው እዚህ ላይ ነው።
ስለ ሰንደቅዓላማ ይነሳ ከተባለ ዜናው “በሰልፉ ላይ ባንዲራ ለምን አልወጣም? ሰንደቀዓላማውን የነፍሱ ያህል የሚያመልክ ህዝብ እንዴት አስቻለው? ሰንደቅዓላማ የተሸሸገበትስ ምክንያት ምንድን ነው?” የሚለውና ከዚሁ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች ነበሩ።
በባድመ ጦርነት ወቅት በዳግም ጥሪ አገሩን ሊታደግ የመከላከያ ሰራዊትን የተቀላቀለው /የደርግ ሠራዊት ሲባል የነበረውን/ ወገን ኩርፊያ ለማስታገስ “የቀድሞውን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ” በባላደራነት በመስጠት ኢህአዴግ የሰውን ልጅ ለማይጠቅም ጦርነት መማገዱን ለሚያወቁ ዜጎች ኢህአዴግ ስለ ሰንደቅ የመቆርቆር መብት እንደሌለው ይረዳሉ። እንዲህ ያለው “ድርጅታዊ ክህደትና ዓላማ ያለው አታላይነት” ዝም ተብሎ አስር ሰዎች ተሟገቱ ብሎ የክስ ማመቻቺያ ሪፖርት ማዘጋጀት ጋዜጠኛ አያስብልም። ሰዎቹ እነማን ናቸው? አንድ ባንዲራ ብቻ እንዴት ሊታይ ቻለ? ማን አመጣው? እንዴት መጣ? ብዙ መጠየቅ የሚቻልበት ጉዳይ ሆኖ ሳለ መታለፉ አስገራሚ ይሆናል። ለነገሩ ሰልፉን አስመልክቶ አቋም ይዞ የጻፈ የአገር ውስጥ ሚዲያም አላጋጠመኝም። ለለቅሶ ግጥምና ሙሾ የደረደሩ ጋዜጠኞች ለህዝባዊ ተቃውሞ የሰጡት ሽፋን ደረጃው ዝቅ ቢልም ከመወረፍ አያድናቸውም።
አትነሳም ወይ በሚል መፈክር ማውረድና የታሰሩ እስረኞች እንዲፈቱ መጠየቅ ህግን መተላለፍና የፍርድ ሂደት ላይ ተጽዕኖ መፍጠር እንደሆነ የሚዘግብ ዘጋቢ የሙያው ባለቤቶች ነን ለሚሉ ሁሉ አንገት የሚያስደፋ ነው። አቶ መለስ እንደ ቴአትር ቤት ድራማ ይጫወቱበት በነበረው ፓርላማ ፊት፣ በቀጥታ ስርጭት በሚተላለፍ ዝግጅት፣ በፖለቲካ እስረኞችና ተከሳሾች ላይ አስቀድመው ውሳኔ ሲሰጡና ብይን ያሰሙ በነበረበት አገር “እስረኞች ይፈቱ” ብሎ መጠየቅ ወንጀል ሆኖ “ህግ ተጥሷል” ሲያስብል መስማት ሞቶ መበስበስ ሲታሰብ የሚዘገንነውን ያህል ይቀፋል። ለዚያውም በአቶ ሽመልስ ከማል አንደበት ሲነገር።
“የስካር መግለጫ”
የአቶ በረከት ተላላኪ የሚባሉትና ለታይታ የሚኒስትር ታፔላ የተለጠፈባቸው አቶ ሽመልስ ሰልፉን አስመልክቶ መግለጫ ሲሰጡ ከንግራቸው በላይ መነጋገሪያ የሆነው በወቅቱ የነበሩበት የሙቀት ስሜት ነበር። አፋቸው ዳርና ዳር አረፋ ይደፍቃቸው ነበር። ሲያመነዥጉ የዋሉትን የጫት መጠንና አይነት መዘርዘር ቢከብድም ከፍራሽ ላይ ተጠርተው የችኮላ መግለጫ እንደሰጡ መደረጉን መሸሸግ አይቻልም። እዚህ ላይ “ምን አገባህ?” የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችል ይሆናል። ምን አልባትም የግል ጉዳይ እንደሆነ ተደርጎ ሊታይ ይችላል። እኔ እስከማወቀው ግን ሰክሮ የተከበረ ህዝብ ፊት መቅረብ፣ መናገር እስኪያቅት ድረስ አይን እያጉረጠረጡ ለህዝብ ማውራት አግባብ አይደለም። አንድ ኪሎ ጫት ከ100 ብር በላይ በሚሸጥበት ሁኔታ ቀን በቀን ጫት ማመንዠክ ከመንግሥት ሠራተኛ (ባለሥልጣንም ጭምር) ወርሃዊ ደመወዝ ጋር የሚመጣጠን ባለመሆኑ ለስርቆትና ሙስና ስለሚዳርግ የሚወገዝ ነው።
shemelisአንድ ክስተት ትዝ አለኝ፡፡ የቀድሞው የሩሲያ ፕሬዚዳንት የነበሩት ቦሪስ ዪልሲን በአልኮሆል አፍቃሪነታቸው ብዙ የተባለባቸው ነበሩ፡፡ እርሳቸው ከሥልጣን ለቅቀው በስፖርተኛነታቸው የሚታወቁትና በጁዶ የጥቁር ቀበቶ ተሸላሚው ቭላዲሚር ፑቲን ሥልጣን ከያዙ ጥቂት ዓመታት በኋላ ግመገማዊ ጥናት ተደረገ፡፡ በውጤቱም በዘመነ ዪልሲን እጅግ አሻቅቦ የነበረው የሰካራም ቁጥር ፑቲን ሥልጣን ከያዙ በኋላ መቀነሱ ይፋ ሆነ፡፡ ኢትዮጵያስ ድሮና ዘንድሮ…?
ወደጉዳዬ ስመለስ እንግዲህ እኚህ ሰው (ሽመልስ) ናቸው “ህገወጥ” በማለት የህዝብን ቁጣ የፈረጁት። የሚላላኩለት ኢህአዴግ ህግ አክባሪ ሆነና ይህ የታፈነ ህዝብ ህገ ወጥ ተብሎ ተፈረጀ። ኢህአዴግና ፍርድ ቤት የተለያዩ አካላት ተደርገው ታዩና “የፍርድ ሂደት ላይ ጫና ለመፍጠር የተደረገ ሙከራ፣ ቀናውን የፍርድ ሂደት ለመበረዝ …” የተቃጣ ሰልፍ ሆኖ ቀረበ። ዳሩ ኢህአዴግ የሚሰበስባቸውን ሰዎች ለሚያውቁ፣ አቶ ሽመልስን በቅርብ ለሚያውቃቸው ጉዳዩ አይገርምም። ስርዓቱ የቆመው እንዲህ ባሉ ሰዎች መሆኑ ግን ያሳዝናል። አሁን ከሶስት ወር በኋላ በሚካሄደው ሰልፍ “የባለሥልጣኖች የጫትና የሺሻ ኮታ ይፋ እንዲሆን እንጠይቃለን” የሚል ጥያቄ ቢቀርብ ማን ቀርቦ “ሰልፉ ህግ መንግስቱን የሚጻረር፣ ጸረ ሰላም ሰልፍ ነው” ይል ይሆን?
“ይህ መንግስት አይመጥነንም”
ለዚህ ጽሁፍ መነሻዬ ይህ ሃሳብ ነው። መንግስት ህዝብን ካልመጠነ ችግር ነው። የደህንነትና ፖሊስ ሃይል ህዝብን ከሚሰልል ይልቅ ከህዝብ ጋር ሆኖ አገርን በጋራ ሊጠብቅ እንደሚገባ የሚጠይቁ አገር ወዳዶች “የሚመጥናቸው መንግስት” አለማግኘታቸው አሳሳቢ ነው። 22 ዓመት ሙሉ ጥላቻ ቢሰበክም እርስ በርሱ ሳይጫረስ እዚህ ደረጃ መድረሱ የሚያናድዳቸው የኢህአዴግ አውራ መሪዎች “ዛሬም ድረስ አልረኩም” የሚሉ ሰልፉ ላይ ነበሩ። እነዚህ ሰዎች ሲሉ የነበሩት ጉዳይ ከመድረክ ተነሳ። “ይህ መንግስት አይመጥነንም” ሲባል ተጮኸ። ድጋፍ ተሰጠ። በማይመጥናቸው አገዛዝ መተዳደር የማይፈልጉ የፍርሃት ቀንበራቸውን ሰበሩ። ሰማያዊ ፓርቲ ይህን ገድል በልጅነቱ ሰራ።self
ሰማያዊ ፓርቲ ሰዎች በሚጥናቸው ፓርቲ መተዳደር እስኪችሉ ድረስ አስፈላጊውን መስዋዕትነት እንደሚከፍሉ ተናገረ። አሁንም በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች አስተጋቡ “አዎ” አሉ። ይህ እውነት ነው። የማይመጥን አገዛዝ የሚወከለው አገዛዙ በሚሰበስባቸው ተላላኪዎቹ ነው። በማይመጥነው አገዛዝ መመራት ያንገሸገሸው ህዝብ ተቃውሞውን ገልጾ ሲገባ “ህገ ወጥ ነህ” የሚሉት አስቀድሞ በካርዱ፣ ከስምንት ዓመት በኋላ በድምጹ፣ በየጊዜው በተለያየ መልኩ የሚያወግዛቸው “ገለባ” ባለጊዜዎች ነው። አስቀድሞ አትመጥኑንም የተባሉ፣ ቢናገሩ ማን ያደምጣል? የተሻሉ የሚባሉ ባለስልጣናት ቢኖሩም ዝምታን እስከመረጡ ድረስ ለህዝብ የሚሰጡት ዋጋ የለምና አብረው ከመደመር አይድኑም።
“አለ ገና” – ተባለ!
ሰላማዊ ሰልፉን ያዘጋጀው ሰማያዊ ፓርቲ እንዳስታወቀው ላቀረባቸው ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች መልስ ካልተሰጠው ከሶስት ወር በኋላ ተመሳሳይ የተቃውሞ ሰልፍ እንደሚያዘጋጅ አስታውቋል። ሌሎች ፓርቲዎችም የሰማያዊ ፓርቲን ፈለግ ተከትለው በየክልሉና በሚታወቁ ከተሞች የተቃውሞ ሰልፍ ለማዘጋጀት ዝግጅት ላይ እንደሆኑ አስታውቀዋል። በኦሮሚያ የኦህዴድ መፋዘዝን ተከትሎ የከረረ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚካሄድ ይጠበቃል። እንደ ጠላት እየታየ የሚፈናቀለው የአማራ ክልል ተቃውሞ ማካሄድ ከጀመረ ከወረዳ ወረዳ የሚዘል እንደሚሆን ይታሰባል። በደቡብ ሲዳማ የተቃውሞ ሰልፍ ከጀመረ ከርሟል። በቅርቡ በተካሄደው የማሟያ ምርጫ ወቅት አምጾ ነበር። አሁንም በቋፍ ላይ ነው።
የተቀመጠበት መቀመጫ እንደ ምጣድ የጋለበት ኢህአዴግ አስቀድሞ ወደ ማስፈራራት የሮጠው አቶ መለስ  “በ97 የተፈጸመው ዓይነት ጥፋት ሁለተኛ አይታሰብም” በማለት የተናገሩትና ያስተላለፉት ትዕዛዝ “ኦርኔል” ስለታወሰው ነው “አለ ገና” መባሉ እንቅልፍ ስለነሳው ነው። ተቃውሞው ወደ ክልሎች ይዛወራል መባሉ ቅዠት ውስጥ ስለከተተው ነው። ሁሉም ወደ ፊት የሚታዩ ቢሆኑም ሰላማዊ ሰልፍ መፈቀዱ የሚመሰገን ነው። ተሰለፉ፣ ተቃወሙ ብሎ ፈቅዶ ለምን ጎነተላችሁኝ ብሎ ለክስና ለእስር መሯሯጥ ደግሞ ግለቱን የሚጨምር በመሆኑ ቢቀር የሚል የሚለውን ምክር እንደዜጋ ለመሰንዘር እወዳለሁ። ከሰሜን አፍሪካ ወደተነሳው የውሃ ፖለቲካ አውድማ ተምዘግዝገን ገብተናልና ቢያንስ ብሔራዊ አንድነታችንን ለማጠናከር ወደሚያስችለን መንገድ ብናመራ ይበጃል። የአሁኑ ሰልፍና ተቃውሞ ጅምር ነው። ኢህአዴግ ከሰማ የማስጠንቀቂያ ደወል ነው። ብሔራዊ መግባባት በመፍጠር አንድ የውስጥ ጉዳያችንን እንዝጋ:: ህዝብ ወሳኝ አካል እንዲሆን የፈሰሰውን ደም እናስብ። በፍርሃቻና በስካር መግለጫ በማስፈራራት ህብረት መፍጠር አይቻልምና። (የጎልጉል ሪፖርተር ካለበት የዘገበው)

No comments:

Post a Comment