Translate

Monday, June 17, 2013

የኢትዮጵያን ደስታ የፊፋ ዜና አቀዘቀዘው( Fisseha Tegegn)

_68206993_ethiአዲስ አበባ ላይ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድንን ያስተናገደው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ጌታሁን ከበደ እና የደቡብ አፍሪካው የፊታ አጥቂ በርናርድ ፓርከር በራሱ ጎል ላይ ባስቆጠሯቸው ጎሎች 2 ለ 1 አሸንፏል።
የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድን በተላይ በመጀመሪያዎቹ 20 እና 25 ደቂቃዎች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የመሀል ክፍል ኳሱን እንዳይቆጣጠር ለማድረግ በሚል ተጭኖ የተጫወተ ሲሆን አንዳንድ ጊዜ ሰባት እና ስምንት የደቡብ አፍሪካ ተጨዋቾችን የኢትዮጵያ ቡድን ግማሽ ሜዳ ላይ ማየት የተለመደ ነበር።
ሆኖም የጨዋታውን የመጀመሪያ የጎል ማግባት እድል የፈጠረው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሲሆን ሳልሀዲን ሰኢድ በግንባሩ የገጨውን ኳስ የደቡብ አፍሪካው ግብ ጠባቂ ኩኔ አድኖበታል።

15ኛው ደቂቃ ላይ ሳልሀዲን ሰኢድ ከርቀት በግሩም ሁኔታ የሞከረውን ኩኔ እንደገና ጎል ከመሆን ሲያከሽፍበት፣ ብዙም ሳይቆይ ፓርከር ከሌሾሎንያኔ የተቀበለውን ኳስ መትቶ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ግብ ጠባቂ ጀማል ጣሰው በግሩም ሁኔታ አድኖበታል።
ጨዋታው ግማሽ ሰአት ያህል እንደተጓዘ ፋላ ከማእዘን ምት ያሻማውን ኳስ ማቶሆ በጭንቅላቱ በመግጨት የሞከረውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ግብ ጠባቂ ጀማል ጣሰው በቡጢ የመለሰው ኳስ ፓርከር ጋር ደርሶ ለደቡብ አፍሪካው ካይዘርስ ቺፍስ ክለብ የሚጫወተው የፊት አጥቂ ያደረገውን የጎል ሙከራ የግቡ መስመሩ ላይ ቆሞ ሲጠብቅ የነበረው አይናለም ሀይሉ በአስደናቂ መከላከል ጎል ከመሆን አድኖታል።
የጨዋታው የመጀምሪያ ጎል የተገኘው 34ኛው ደቂቃ ላይ ሲሆን በረኛው ኩኔ በረጅሙ ወደ ኢትዮጵያ ሜዳ የመታውን ፓርከር ከኢትዮጵያ ተከላካዮች ፈጥኖ በመሮጥ የመታው ኳስ ጀማል ጣሰውን አልፋ መረብ ላይ በማረፏ ደቡብ አፍሪካ ጨዋታውን 1 ለ 0 እንድትመራ አስችሏታል።
የደቡብ አፍሪካ መሪነት የቆየው ግን ስምንት ደቂቃ ያህል ብቻ ሲሆን የመጀመሪያው ግማሽ የጨዋታ ክፍለ-ጊዜ ሊጠናቀቅ ሁለት ደቂቃዎች ያህል ሲቀሩት አዲስ ህንጻ፣ ሽመልስ በቀለ እና ጌታነህ ከበደ ያደረጉት ቅብብል የፈጠረውን የጎል ማግባት እድል ጌታነህ ከበደ በግሩም ሁኔታ ከመረብ አሳርፎ የመጀመሪያው ግማሽ የጨዋታ ክፍለ-ጊዜ 1-1 ተጠናቋል።
በሁለተኛው ግማሽ የጨዋታ ክፍለ-ጊዜም ልክ እንደ መጀመሪያው ሁሉ ደቡብ አፍሪካ ተጭኖ የተጫወተ ቢሆንም የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ጠንካራ የመከላከል እንቅስቃሴ ጥቃቱን ለመቋቋም አልተቸገረም ነበር። በተለይ ተቀይሮ የገባው ራንቴ ሜዳ ከገባ ብዙም ሳይቆይ ሁለት አደገኛ የጎል ማግባት ሙከራዎችን ቢያደርግም የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የመከላከል እንቅስቃሴሴ እና የራሱም የአጨራረስ ድክመት ሙከራውን አክሽፎበታል።
70ኛው ደቂቃ ላይ አበባው ቡጣቆ በቅጣት ምት ወደ ደቡብ አፍሪካ የፍጹም ቅጣት ምት ክልል የላከውን ኳስ የደቡብ አፍሪካው ፓርከር በግንባሩ ገጭቶ ባልተጠበቀ ሁኔታ በራሱ ጎል ላይ ግሩም ጎል በማሳረፉ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 2 ለ 1 በሆነ ውጤት ሊመራ ችሏል።
የጨዋታው የመጨረሻ 15 ደቂቃዎች በአብዛኛው ደቡብ አፍሪካ ጎል ለማግባት በሚያደርገው ማጥቃት፣ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ደግሞ ውጤት አስጠብቆ ለመውጣት እና በሚገኙ አጋጣሚዎች ኳሱን ወደፊት ለሳልሀዲን ሰኢድ እና ጌታነህ ከበደ በመላክ በማጥቃቱ ላይ በመሳተፍ በሚያደርጓቸው ጥንቃቄ የተሞላባቸው እንቅስቃሴዎች ከተጓዘ በኋላ በኢትዮጵያ 2 ለ 1 አሸናፉነት የተጠናቀቀው።
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ከጨዋታው በኋላ በሰጡት አስተያየት፦
“ይሄ ተአምር ነው። ዛሬ በምንም ቃል ሊገለጽ የማይችል ለኢትዮጵያዊያን ታላቅ ቀን ነው። ደቡብ አፍሪካ በመጀመሪያው ግማሽ ተጭኖን ተጫውቷል። ጠንካሮችም ነበሩ። በሁለተኛው ግማሽ ግን የአጨዋወት ለውጥ በማድረግ ሁለቱ የተመላላሽ ስፍራ ተጨዋቾችቼ አጥቅተው እንዲጫወቱ አደረኳቸው።
“ምክንያቱም በሜዳችን እንደመጫወታችን አቻ መውጣት በቂያችን አልነበረም። በደጋፊያችን ፊት ማሸነፍን እፈልግ ነበር። በርግጥ ያሸናፊነቷን ጎል የሰጠን ደቡብ አፍሪካዊ ተጨዋች ነው። ምን አልባት እግርዚአብሄር ድሉን ለኛ ሊሰጠን ስለወሰነ ይሆናል ያ የሆነው” ብለዋል።
የደቡብ አፍሪካው አሰልጣኝ ጎርደን ኢገንሰንድ ቡድናቸው ቢሸነፍም የተጋጣሚያቸው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እና ደጋፊውን ከማድነቅ ወደኋላ አላሉም።
“ኢትዮጵያዊያንን እንኳን ደስ ያላችሁ እላለሁ። በጣም አስቸጋሪ ጨዋታ ነበር። በተላይ ደጋፊዎቻቸው ግሩም ነበሩ” ብለዋል።
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከዚህ ውጤት በኋላ ምድቡን አንድን በ13 ነጥብ በመምራት አንድ የምድብ ጨዋታ እየቀረ በጥሎማለፍ መልክ ወደሚካሄደው የቀጣዪ ዙር የአለም ዋንጫ ማጣሪያ ማለፏን ቢያረጋግጥም የአለም አቀፉ እግርኳስ ፌዴሬሽን ፊፋ እሁድ ማምሻውን ባወጣው ዜና “የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአለፈው ሳምንት ቦትስዋናን 2 ለ 1 በረታበት ጨዋታ ላይ ተሰልፎ መጫወት ያልነበረበት ተጨዋች አሰልፎ አጫውቷል” በሚል ምርመራ እንደሚደረግበት ማስታወቁ በኢትዮጵያዊያን ላይ የተፈጠረውን ታላቅ የደስታ ስሜት አደብዝዞታል።
ፊፋ ኢትዮጵያን ጨምሮ በቶጎ እና ኢኳቶሪያል ጊኒ ላይ ተመሳሳይ ምርመራ የከፈተው የፊፋ የውድድር እና ስነ-ስርአት መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 55 እና የብራዚሉ አለም ዋንጫ ማጣሪያ መተዳደሪያ ደንብ ላይ አንቀጽ ስምንትን በመጥቀስ ነው።
የፊፋ የውድድር እና ስነ-ስርአት መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 55
የፊፋ የውድድር እና ስነ-ስርአት መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 55
የፊፋ የጨዋታ መዝገቦች እንደሚያሳዩት ከሆነ ምን አልባት መጫወት ሳይኖርበት የተጫወተው ምንያህል ተሾመ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ከደቡብ አፍሪካ ጋር 1 ለ 1 በተለያየችበት እና አዲስ አበባ ላይ ቦትስዋናን 1 ለ 0 በረታችበት ጨዋታዎች ላይ የቢጫ ማስጠንቀቂያ ካርዶች ያየ በመሆኑ በአለፈው ሳምንት ኢትዮጵያ ወደ ሎባትሴ አቅንታ ቦትስዋናን 2 ለ 1 በረታችበት ጨዋታ መሰለፍ አልነበረበትም።
ምንያህል ተሾመ በየነ የቢጫ ማስጠንቀቂያ ካርዶች ያየባቸው ጨዋታዎች (ምንጭ – ፊፋ ድረ-ገጽ)
ኢትዮጵያ ጥፋተኛ ሆና ከተገኘች የአለፈው ሳምንቷ ድል ይሰረዝ እና ለቦትስዋና የ 3 ለ 0 አሸናፊነት እና ሙሉ ሶስት ነጥብ የሚሰጥ ሲሆን፣ የምድብ አንድ የደረጃ ሰንጠረዥን ኢትዮጵያ በ10 ነጥብ ስትመራ፣ ደቡብ አፍሪካ በስምንት ነጥብ ሁለተኛ፣ ቦትስዋና በሰባት ነጥብ ሶስተኛ፣ መሀከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ በሶስት ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘው የሚከተሉ ይሆናል።
ስለዚህ ወደ ቀጣዩ ዙር የአለም ዋንጫ ማጣሪያ የሚያልፈውን የምድቡ አሸናፊ ለመለየት መሀከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ከ ኢትዮጵያ፤ ደቡብ አፍሪካ ከ ቦትስዋና የሚያደርጉት የምድቡ የመጨረሻ ጨዋታዎች ወሳኝ ይሆናሉ ማለት ነው።

No comments:

Post a Comment