Translate

Wednesday, June 12, 2013

ጉድ በል ሰላሌ 2

Abe Tokchaw
ልክ እሁድ ነግቶ ሰኞ ሲመጣ አንዲት ማስታወሻ ለዘመዶቼ ከትቤ ነበር፡፡ ማስታወሻዋ ብዙ ምላሾችን አምጥታለች፡፡ በሌላ አባባል ገበያዋ ደርቷል ማለት ነው፡፡ በመጀመሪያ ገበያዋን ያደሯትን ሁሉ ምስጋና ላቀርብ ይገባኛል፡፡ የመከራችሁኝ፣ የተቆጣችሁኝ፣ ያመሰገናችሁኝ፣ እንኳንስ ሌላው ቀርቶ ሙልጭ አድርጋችሁ የሰደባችሁኝ ሁሉ ለኔው ብላችሁ እንደሆነ እረዳለሁ፡፡ እንዲሁም የቤተዘመድ ስድብ ከምርቃት እኩል ነው ባዬ “ገለቶማ” እላለሁ፡፡
በመጀመሪያ ወዳጆቻችን ተቃውሞውን ያሰሙት ለካስ በግብፅ UNHCR ቢሮ ፊት ለፊት ነው፡፡ (በቅንፍም ራሴን እወቅሳለሁ፤ እንዴት ያለሁት ከንቱ ነኝ ባካችሁ… በኢትዮጵ ኤምባሲ ፊት ለፊት ብዬ ያሳሳትኳችሁን በሙሉ ይቅርታ ጠይቃለሁ፡፡) የሰልፉ አላማ ኢትዮጵያውን በአባይ ግድብ ጦስ በግብጻዊያኑ ጥቃት እየደረሰባቸው በመሆኑ በተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን ጥበቃ ሊያደርግልን ይገባል በሚል ነው፡፡ ይሄ በጣም ትክክለኛ ነገር ነው፡፡ እኛም እዚህ ሆነን የምንሰለፍለት ካልሆንልም ግብጽ ድረስ ሄደን የምንሰየፍለት የወገኖቻችን ጉዳይ ነው፡፡

መንግስታችንም አልሰማ አለ እንጂ ብዙዎች የመከሩት፤ አባይን ለመገደብ ከመነሳቱ በፊት ማድረግ ከነበረበት ጉዳዮች ውስጥ ቅድሚያው ዜጎቹ ላይ ጥቃት ሳይደርስ ስራውን መስራት የሚችልበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነበር፡፡ ነገር ግን አልሰማም፡፡ ስለዚህም በአባይ ጦስ የገዛ ዜጎቻችን ብዙ ጥቃት እየደረሰባቸው ነው፡፡ ጥቃቱ የጀመረው በደሞዝ ነጠቃ ነው፡፡ አባወራው ልጆቹ በቤት እያለቀሱበት ለአባይ ብሩን መስጠት ግዴታው ነበር፡፡ በነገራችን ላይ እኔም ለስንት ወራት እንደሆን እንጃ እንጂ ይቅርብኝ ብዬ ከእለት ጉርሴ ቀንሼ ለአባይ ደሞዜን አስቆርጫለሁ… (ወደህ ነው…? አይሉኝም…)  ይህ ጥቃት ሲቀጥል ይሄው በግብጽ የሚኖሩ ዜጎቻችን ላይ ትልቅ ስጋት ሆኖ ቀጠለ፡፡ (የእነርሱ እንደውም ፈጥኖ የሚደርስላቸው አካል ካላገኙ፤ ደሞዝ ሳይሆን ደም የሚከፈልበት ሊሆን ይችላል)  ይሄንን ጥቃት መንግስታችን ሊከላከለው ተነሳሽነት አላሳየም፡፡ ጭራሹኑም ደስ ሳይለው አይቀርም፡፡ እኛ ግን ይህ ፍራሽ ዘርግተን የምንቀመጥበት ሀዘናችን ነው፡፡ እንደውም “ባንቺ የመጣ በአይኔ መጣ!” የሚለውን ዘፈን በግብፅ ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በሙሉ መጋበዝ እፈልጋለሁ፡፡
ችግሩ፤ በሰልፉ ላይ ከተያዙት መፈክሮች አንዱ “እኛ ኦሮሞዎች ነን እንጂ ኢትዮያዊ አይደለንም እና ተዉን” የሚል ይገኛል፡፡  ያ ማለት ሌሎቹን እንደፈለጋችሁ አድርጓቸው እኛን ብቻ አትንኩን ማለት ነው፡፡
በመሰረቱ ይሄ አንኳንስ ለሌላ ለራሳቸው ለተሰላፊዎችም የማይጠቅም ሀሳብ ነው፡፡ የግብፅ መንገስት እንኳንስ እንዲህ ብለውት ይቅርና እንዲሁም ተቃዋሚዎችን አስታጥቄ አበጣብጣችኋለሁ እያለን ነው፡፡ ስለዚህ እውነትም እናንት እንዲህ ብላችሁ የተሰለፋችሁ ወዳጆቻችን የUNHCR ጥበቃ ሳያስፈልጋችሁ ግብጽ ራሷ እቅፍ ድግፍ አድርጋ ትይዛችኋለች፡፡
UNHCR ም ይሄኔ በሆዱ ስለዚህ “እናንተን ኢትዮጵያዊ ስላልሆኑ አትንኳቸው ብዬ እነግርላችኋሁ ኢትዮጵያዊ ሆነው የጥቃቱ ሰለባ የሆኑትን ግን ጥበቃ አደርጋለሁ” ሳይላችሁ አይቀርም፡፡
የሆነው ሆኖ በ “ጉድ በል ሰላሌ” ጨዋታችን በውስጥ መስመር ሳይቀር ብዙ አስተያየቶች አስተናግጃለሁ፡፡
ለማብራራት ያህል፤
እኔ ኦሮሞ ነኝ፡፡ ኦሮሞነቴን የሰጡኝ አባቴ እና እናቴ ናቸው እንጂ ከሱፐር ማርኬት ገዝቼው አይደለም፡፡ እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ ኢትዮጵያዊነቴን ያገኘሁት ከእናት እና ከአባቴ እንጂ አንዳች አካል እላዬ ላይ ለጥፎብኝ አይደለም፡፡
በኢትዮጵያ በርካታ የኦሮሚያ አካባቢዎች ተዟዙሪያለሁ፡፡ የዛን ጊዜ ከ”አካም ቡልተኒ” ውጪ ምንም ኦሮምኛ አላውቅም ነበር፡፡ ነገር ግን በየባላገሩ ያሉ ኦሮሞዎች የኔ ቋንቋ አለመቻል አንድም ቀን አሳስቧቸው አያውቅም፡፡ ሰው በመሆኔ ብቻ አክብረው እርጎ አቅርበውልኝ፣ እርጎ የሆነ ፈገግታ ለግሰውኝ፣ ለራቸው ከሚተኙበት የተሸለ መኝታ ሰጥውኝ በእንክብካቤ ነው የሚያስተናገዱኝ፡፡
አንዳንዶች፤ ኦሮሞ ኢትዮጵያዊ አልመሆኑን ሊነገሩኝ ታሪክ እንዳነብ፣ አዋቂ እንድይቅ፣ ጸሎት እንዳደርግ ሁላ መክረውኛል፡፡ እኔ ግን ይሄንን ሁሉ ማድረግ ሳያስፈልገኝ ከኦሮሞ የሚፎካከር ኢትዮጵያዊ እንደሌለ አሁን በቅርቡ የዞርኩባቸው የኦሮሚያ ገበሪዎች አረጋግጠውልኛል፡፡ ይህንን ነገር እኔ ብቻ ሳልሆን በቅርብ የኦሮሞን ህዝብ ጠንቅቀው የሚያውቁት እነ ጀነራል ከማል ገልቹ አረጋግጠውታል፡፡ እነ አቶ ቡልቻ ደመቅሳም መርቀውታል፡፡ ለዛም ነው ዛሬ የጀነራል ከማል ገልቹ ኦነግ በስፋት ተቀባይነት እያገኝ የመጣው፡፡
እደግመዋለሁ መገንጠል የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ ቢሆን ኖሮ እንደ ኦሮሞ ህዝብ ጀግንነት እና ብዛት አርባ አመት ፈጅቶ አይኮላሽም ነበር፡፡
በአሁኑ ጊዜ የኦሮሞ ህዝብ እየተበደለ እንደሆነ ምንም ጥያቄ የለውም፡፡ በርካታ ወዳጆቼ ኦሮምኛ ተናጋሪ ስለሆኑ ብቻ ከዩንቨርስቲ ወጥተው እስር ቤት ገብተዋል፡፡ ከስራቸው ተባረው ለስደት ተዳርገዋል፡፡ ወዘተ ተደርገው ወዘተ ሆነዋል፡፡ ልክ እንደዛ ሁሉ ግን በደሉ ሌሎችም ዘንድ አለ፡፡ አማራውም ትግሬውም አዲሳቤውም ሁሉም ቁስል አለበት፡፡
እኔ ብቻ ነኝ የተበደልኩት ብሎ ማሰብ የትም አያደርስም፡፡ በደለኛው ሁሉ የራሴን ሀገር እሰራለሁ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ ከማለት ይልቅ ተባብሮ፣ በደል የሌለባት ሁሉም ተሳባስቦ የሁሉም መብት ተጠብቆ የሚኖርባት ሀገር እንድትኖረን ለማድረግ መትጋት ነው የሚሻለው፡፡
(አቦ በናታችሁ ብዙ ፖለቲካ አታናግሩኝ እኮ!)
በመጨረሻም 1
ኦባንግ ሜቶ እንዲህ አለ፡፡ “ኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ መንገዶች ተገንብተዋል፡፡ ነገር ግን አንድ መንገድ ይቀረናል፡፡ እርሱም የፍቅር መንገድ ነው” እኔም አልኩኝ፤ የፍቅርን መንገድ ዛሬውኑ የቻይና ኮንትራክተር ሳንጠራ ራሳችን ልንገነባው ይገባል፡፡
ኦባንግ ሜቶ ያድርግህ መቶ!
በመጨረሻም 2
ኮባ ኮርማ በጃምቦ ጆቴ!

No comments:

Post a Comment