Translate

Sunday, March 9, 2014

ህዝብን በመጨቆን ሀገርን መምራት አይቻልም!

በአሸናፊ ንጋቱ

የፖለቲካ ስርአትና የአንድ ሀገር እድገት ቀጥተኛ የሆነ ግንኙነት አላቸዉ። አንድ አገር ትክክለኛ ባልሆነ የፖለቲካ አገዛዝ ይበለፅጋል ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው። ሃገራችን ኢትዮጵያም የወያኔ መንግስት ባነገሰው የተዛባ አገዛዝ ሳቢያ ህዝባችን ለከፋ ችግር መዳረጉ በገሃድ የሚታይ ሃቅ ነው። ታዲያ በዚህ ወያኔያዊ የተዛባ አገዛዝ እንዴት ከችግር ልንወጣ እንችላለን? አገራችን ኢትዮጵያ ምንም እንኳ የጥንት ስልጣኔ ባለቤት ብትሆንም በአየር ንብረትም ሆነ በተፈጥሮ ሀብት ጥሩ ከሚባሉት ሀገሮች አንዷ ብትሆንም እንደ እድል ሆኖ መሪዎች ግን አልተሳኩላትም። ለምን ኢትዮጵያ የረሃብ አገር ተባለች ለምን ዜጎቿ ተደስተው በነጻነት መኖርን እንደተመኙ ህልማችዉ ከንቱ ሆነ? ብዙዎች የሞቱላት አገር  አንገታቸዉ ለሰይፍ ደረታቸዉ ለጥይት የሰጡላት አገር ኢትዮጵያ በህዝቦቿ ታታሪነት አለም ያደነቃት ለምን ተዋርዳ ተገኘች!?

እውቀትን፣ ስልጣኔን፣ ጥበብን ለአለም ያበረከተች ሃገር ዛሬ ላይ በቤተ መንግስቱም ይሁን በቤተ ክህነቱ የተማሩ ሰዎችን ናፊቂ ሆናለች፡፡ ምክንያቱም ምሁራኑ በሃገራቸው ሊኖሩ የሚያስችላቸው እድል ስላልተመቻቸላቸው ሁሉም ጉዟቸው ወደ ውጭው አለም ስደት በመሆኑ ነው፡፡ በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህዝቦች በረሃብ አለንጋ የሚገረፍባት ሲኦልም ከሆነች ዘመናትን አስቆጥራለች፡፡ እንዲሁም መለያየትን ወይም ዘረኝነት በግልፅ የምትሰብክ የዘረኞችና የጎሰኞች መሰማሪያ ሜዳ ሆና ክፉ አድራጊዎች እንደፈለጉ እየዘፈኑባት ትገኛለች፡፡ በቃል ከሚወራ ዲሞክራሲ፣ እድገት፣ ብልፅግና በስተቀር በተግባር የሚታይ አንዳችም መልካም ነገር የማናይባት አሳፊሪ ሃገር ሆናለች፡፡ በደልና ጭቆና በዝቷል ድህነትና ጉስቁልና ከመቼዉም በባሰ ተንሰራፍቷል እስርና ሰቆቃ ተራ ነገሮች ሆነዋል። በአሸባሪዎች ስም እራሳቸዉ ቦንቦች አጥምደው ህዝቦች እየፈጁ ሰላማዊ ዜጎች በአሸባሪነት እየተፈረጁ ለስቃይ እየተዳረጉ ነዉ። ዛሬ በሃገራችን አርሶም ሆነ ነግዶ መኖር አይቻልም። መኖር የሚቻለዉ ኢሕአዴግ ልማት ነዉ የሚለዉን መዝሙር በመዘመር ብቻ ነዉ።
የሁሉም ነገር መሰረት እንደሆነ የሚታመንበት ትምህርትን ብንመለከት እንኳ ትምህርት በኢትዮጵያ ሞቷል ለማለት በሚያስደፍርበት ጀረጃ ደርሷል። ከተለያዩ ሀገሮች ያለምንም ጥናት በኩረጃ የሚያመጧቸዉ የትምህርት ፖሊሲዊች ምንም እንኳን ብዙ ወጭ ቢወጣባቸዉም የሚሰራባቸዉ ለአንድ የትምህርት መንፈቀ አመት ብቻ ነዉ። በኢትዮጵያ ወያኔ ልማት ነዉ በሚል አባዜ የተለከፈ ትልቅ ቦታ ይሰጠዋል። ልማታዊ መንግስት፣ ልማታዊ፣ ዘፋኝ፣ ልማታዊ አስተማሪ፣ ልማታዊ የእምነት ዘርፍ፤ ወዘተ… በማለት ከወያኔ ጎን ካልተሰለፉ ኢ-ልማታዊ/ ሽብርተኛ የሚል ስም ይሰጣቸዋል ይህንንም ተመርኩዞ ለእንግልትና ለእስራት ይዳረጋሉ። ‘‘ዶሮ ጭንቅላቷ ላይ ስጋ ተሸክማ ወይ አትበላዉ ወይ አታስበላዉ‘‘ እንደተባለዉ ማንንታቸዉና እዉቀታቸዉን ትተዉ የወያኔ መዝሙር ብቻ በመዘመር የሚኖሩ ጥቂት ሰዎች በኢትዮጵያ ዉስጥ የማይጠበቅ ኑሮን ሲኖሩ ይታያሉ። የሚላስ የሚቀመስ በጠፋበት በአሁኗ ኢትዮጵያ ዘይትና ሽንኩርት ለመግዛት እንኳ አንድ ግለሰብ የወር ደሞዙ በቂ አልሆን ባለበት ግዜ እንዴት ጥቂት ባላባቶች ፎቆችና ቪላዎች ይገነባሉ? የህዝብ ንብረት ካአልተዘረፈ በቀር እነሱ ከየት አመጡት? ወይስ ኢትዮጵያ ሲባል እነሱን አይጨምርም?  ከአዉሮፓ መንግስታት የሰዉ ፍጥረት በረሃብና በህክምና እጥረት ህይዎቱን ለማዳን ተብሎ የሚላከው ገንዘብ እነሱ ዉስኪ ሲራጩበት ሊሞዚንና አሉ የተባሉ ምርጥ በአለም ከታወቁ ካምፓኒዎች የተሰሩ መኪናዎች ሲገዙበት ለህዝቡ ድህነት  ባህላችን መሆኑን ዘላለም በመተረክ ይኖራሉ። በስብሰባ ፍቅር ብቻ የተለከፉ ባለስልጣናቶቻችን ስብሰባዉን እንደጨረሱ አበል በሚል ስም ገንዘብ ይከፋፈላሉ። ይህንን እንስሳዊ የሆነ አስተሳሰብ አልደግፍ ያሉት ደግሞ ፀረ ልማትና አሸባሪ በሚል ስም ለእንግልት ይዳረጋሉ። አሸባሪነት ለምን የፖለቲካ መጠቀሚያ ሆነ? አሁን የታሰሩት ዉብ የኢትዮጵያ ልጆች አሸባሪዎች እንደሆኑ የሁል ግዜ ለጆሮ የሰለቸ ንዝንዝ ነዉ፤ ስለዚህ አሸባሪነት ለአምባገነናዊ መንግስት አለመዘመር ከሆነ ወደድክም ጠላህም መኖርም ሆነ መስራት የሚቻለዉ ይህንኑ ስትዘምር ብቻ ነዉ። ለዚችው በሺህ የሚቆጠሩ የነፃነት ታጋዮች የታሰሩባት; ረሃብ፣ ጦርነት፣ሞትና ግድያ መለያየት የሰፈነባት፤ ዜጎችዋ በሰላም ወጥተው በሰላም ለመግባት ለሚሸማቀቁባት ሃገር ለታሪኳ ሁለ መበላሸት ተጠያቂው ወይም ተወቃሹ ገዳዩ የወያኔ አገዛዝ ነው፡፡
ስለዚህ የኢትዮጵያ የድንቁርና ፣ የመለያየት፣ የጦርነት፣ ያለማወቅ፣ የግድያ ጭለማ እንዴት ይወገድ ወደሚለው መፍትሄ ሃሳብ ስንመጣ፤ በኢትዮጵያ ያለው የክፉ ነገሮች ሁሉ ጨለማ የሚወገደው በወለደቻቸው እና ባሳደገቻቸው ኢትዮጵያውያን ሃገር ወዳድ ልጆቿ ነው፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ሰላም ናፍቋት የሰላም ያለህ እያለች ነው፡፡ ውድ ልጆቿም አረመኔው የወያኔ መንግስት በየጊዜው እየቀሰፈባት እረፍትን ትሻለች፡፡ በመሆኑም ይህን አምባገነናዊ  የወያኔ ስርዐት በማስወገድ  ; በሃገራችን የእውቀትና የሰላም ብርሃን እንዲፈነጥቅ ; ዜጎቿም በሰላም ወጥተው በሰላም እንዲገቡ;  መብቶቻቸውም ሊጠበቁ የሚችሉበትን እንዲሁም የምንፈልገውን ነፃነት፣ እድገት፣ፍትህ፣ ዲሞክራሲ በኢትዮጵያ ለማምጣት የራሣችንን ቁርጠኝነት ማሣየት ይጠበቅብናል!!!
ድል ለጭቁኑ ህዝብ!!!

No comments:

Post a Comment