Translate

Wednesday, March 12, 2014

የአባ መላ (ብርሃኑ ዳምጤ) መገለባበጥና ኢሳት

እንደልቡ/ዳግም (ከቫንኮቨር፣ ካናዳ)

አባ መላ ማን ነው?
Aba Mela low rank Ethiopian government cadreበቅጽል ስሙ “አባ መላ” በእውነተኛ ስሙ ደግሞ ብርሃኑ ዳምጤ ተብሎ ይጠራል፣ በ60ዎቹ የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኝ አዛውንት ነው (ምንም እንኳ ስራው እንደ እድሜው ባይሆንም)። ፓልቶክ የሚባለውን የማህበራዊ መገናኛ መድረክ በመጠቀም በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ዲስኩር በማሰማት ይታወቃል። በወጣትነቱ ኢህአፓ ውስጥ ነበር የሚባለው ብርሃኑ ዳምጤ ወዲያውም የኢህአፓን መዳከም አይቶ ወደ ደርግ ቡድን መቀላቀሉን የሚያውቁት ይናገራሉ። በወቅቱ አብረውት በኢህአፓ ውስጥ ይሳተፉ የነበሩ ወጣቶችን ለደርግ በእጅ መንሻ መልክ አሳልፎ ሳይሰጥ እንዳልቀረ በደርግ ካድሬነት ቆይታው የሚያውቁት ይጠረጥራሉ አንዳንዶች ደግሞ አፋቸውን ሞልተው ይናገሩታል።

ብርሃኑ ዳምጤ ከደርግ መውደቅ በኋላ በስደቱ ዓለም (ዳያስፖራ) ፖለቲካ መድረክ ብቅ ያለው በምርጫ 97 ወቅት የዝነኛውን ቅንጅት ማልያ ለብሶ ነበር። ይሁንና በስልጣን ላይ ያለው የህወሃት/ወያኔ መንግስት ምርጫውን አጭበርብሮ፣ የምርጫውን መጭበርበር የተቃወሙትን በገፍ በአደባባይ በጥይት ደብድቦ፣ ህዝቡ የመረጣቸውን የቅንጅት አመራሮች፣ ጋዜጠኞችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን ጨመሮ ከ50 ሺህ በላይ ባብዛኛው ወጣቶችን አስሮና በየጦር ካምፖቹ አጉሮ በአምባገነንነቱ ለመቀጠል ሲወስን ብርሃኑ ዳምጤም ባፋጣኝ የቅንጅትን ማልያ አውልቆ የህወሃት/ኢህአዴግን ማልያ ለብሶ ቁጭ አለ።
ሰሞኑን ደግሞ ብርሃኑ ዳምጤ አስደናቂ መገለባበጥን ፈጽሞ የህዝብን አይን አስበልጥጧል። እነዚህ ብርሃኑ ዳምጤ (አባ መላ) ሰሞኑን የሚፈጽማቸው መገለባበጦች በ1960ዎቹ እና 70ዎቹ ከነበሩት የመገለባበጥ ትሪኢቶቹ ለየት የሚያደርጋቸው ነገር ቢኖር አሁን መገለባበጡን የሚፈጽመው በቀጥታ ስርጭት ወቅት (በፓልቶክ) መሆኑና ጉዳዮን በመሪ ዜና መልክ የሚዘግብለት የቴሌቪዥን ጣብያ “ኢሳትን” ማግኘቱ ነው።
ብርሃኑ ዳምጤ ከጥቂት ወራቶች በፊት ነበር የተሰለፈበት የህወሃት/ኢህአዴግ ጎራ በተለይም ከወያኔው ቁንጮ መለስ ዜናዊ ሞት በኋላ እየተዳከመ መምጣትን አይቶና ገምቶ ወያኔዎችን “አፍንጫችሁን ላሱ፣ እኔ ከአሁን ብኋላ የድሮው አባ መላ አይደለሁም፣ እንዲያውም ጉዳችሁን አዝረጠርጣለሁ…” በማለት ፉከራ ቢጤ አሰምቶ የዲሞክራሲና የነጻነት ታጋዮችን ጎራ መቀላቀሉን ያበሰረው።
መንፈቅ እንኳ ሳይሞላ አባ መላ በመጣበት አይነት መንገድ ተመልሶ ህወሃት/ኢህአዴግን ለማገልገል መወሰኑን ይፋ አደርጓል። ለሱ እምብዛም አዲስ ያልሆነውን የክህደት ቁልቁለትም ዳግም ተያይዞታል።
አባ መላ፣ ኢሳትና ዳያስፖራው
የኢሳት ጋዜጠኞች፣ አንዳንድ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችና የተቃዋሚ ፖለቲከኞችም ጭምር ይህ አባ መላ የሚባለውን ቦታ እየቀያየረ ይሚጫወት ዝቅተኛ ካድሬ ከሚገባው በላይ ቦታ ሰጥተውት እንደነበር እገምታለሁ፣ በውጤቱም ተከታዮቻቸውን ያሳሳቱና ያዘናጉ ይመስለኛል። ይህንን ጉዳይ ማንሳቴ “ብዬ ነበር” ለማለት ሳይሆን ይልቁኑም ይህ ክስተት እንደ መማሪያ ሆኖ እንዲያልፍ በመፈልጌ መሆኑን አባብያን እንዲረዱልኝ እፈልጋለሁ።
እንደ አባ መላ አይነቱ ቀደም ሲል በተደጋጋሚ የመገለባበጥ ብቃቱን ያሳየ ወለፈንዴ ተቃዋሚ ጎራ ገብቻለሁ ሲል አያያዛችን ጥንቃቄ የተሞላበት፣ ሊሆን ይገባል። በቅርቡ ተገልብጦ ሊያሳፍረን ይችላል ብሎ መስጋት፣ ለጉዳዩ መጠነኛ የአየር ሰዓት መስጠትና ውሎ አድሮ ደግሞ መርጋቱን እያዩ ወደሌላው መተላለፍ ተገቢ ነው። እንደው በአንድ ጊዜ ይህን ከምላስ በስተቀር ቁም ነገር የሌለው ተራ ካድሬ ወደላይ ቆልሎ አንድ ጊዜ “አክቲቪስት” ሌላ ጊዜ ደግሞ “የፖለቲካ ተንታኝ” እያሉ በኢትዮጵያውያን ስም በዓለም አቀፍ ደረጃ የተቋቋመ ግብረ ሰናይ ድርጅትን እንዲመራ ማጨት ድረስ መጓዙና አሉ ከሚባሉ ፖለቲከኞች ጋር መድረክ እንዲጋራ ሁኔታዎችን ማመቻቸቱ አገባብ አልነበረም።
የኢሳት ባልደረባ ደረጀ ሃብተወልድ የአባ መላን መገልበጥ አስመልክቶ በፌስቡክ ገጹ ላይ እንዳሰፈረው ከሆነ ግን ኢሳቶች ከስህተቶቻቸው ሊማሩ የተሰናዱ አይመስልም ይልቁኑም አባ መላን አስመልክቶ ሊቀርቡ የሚችሉ ትችቶችን ቀድሞ ለመከላከል ነው ሙከራ የሚያደርጉ ያሉት። ደረጀ ሃብተወልድ እንዲህ ነበር ያለው፣
“ነገሩ ወዲህ ነው። አባ መላ ኢህአዴጎችን እየሰደበ ወደ ተቃዋሚው ጎራ ሲቀላቀል “አገኛለሁ” ብሎ ያሰላው ጥቅም ነበር። ሆኖም ሀሳብን በነፃነት ለመግለጽ ከሚያስችል ነፃ መድረክ ውጪ ሌላ ነገር ሊያገኝ አልቻለም። ባገኘው ነፃ መድረክም ማንም ሳይቆነጥጠው ከትንሽ እስከ ትልቅ የቀድሞ አለቆቹን እስከ ዶቃ ማሰሪያቸው ነግሯቸዋል። እኛንም አስቆናል። ስንስቅለት ጨምሮ ጨማምሮ አቅምሷቸዋል። እኛም፦“የአገሩን ሰርዶ ባገሩ በሬ” እያልን ተዝናንተናል። ከዚያ ባለፈ ግን ለቁም ነገር ያሰበው ሰው ስለመኖሩ እጠራጠራለሁ።”
የደረጀን አባባል ሁሉም ሰው የተቀበለው አይመስልም ይህን ለማሳየት ከተቃውሞ ሃሳቦች መካከል አንዱን ከዚያው ከደረጀ ሃብተወልድ የፌስቡክ ገጽ ልበደር፣
“የአባ መላን መገልበጥ ተከትሎ ኢሳቶች ከተወቃሽነት ለመዳን የዘየዳችሁት ይሄው ነው? ደረጀ “አባ መላን ለቁም ነገር ያሰበው ያለ አይመስለኝም” ያልከው ፈጽሞ ከእውነት የራቀ ነው፣ በሳውዲ ወገኖቻችንን ለመታደግ በተቋቋመው አለም አቀፍ ድርጅት ውስጥ ከታማኝ እና አበበ ገላው ቀጥሎ ሶስተኛ ሰው ተደርጎ አልነበረም? በጣም ብዙ ማለት ይቻላል… “እጄን በጄ” ሆኖብን እንጂ። ለማንኛውም ከስህተቶቻችሁ ተማሩ፣ በጣምም አንፍጠጥ ያስተዛዝባል።” Ethiopian Unity
ለማጠቃለል ያህል የሚሰራ ጋዜጠኛ፣ ለውጥ ለማምጣት የሚተጋ ፖለቲከኛና የዲሞክራሲ ታጋይ በሂደት ውስጥ ስህተት ሊሰራ ይችላል፣ ከስህተቶች ትምህርት ወስዶ ለሁለተኛ ጊዜ ተመሳሳይ ስህተትን ላለመድገም ጥረት ማድረግ ግን ሊለመድ ይገባል። ነገሮቻችን ሁሉ “ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ” እንዳይሆኑ ሃላፊነት ወስደን ከስህተቶቻችን ለመማር ዝግጁ እንሁን።

No comments:

Post a Comment