Translate

Saturday, May 18, 2013

ታሪክን የኋሊት፤ የአቶ መለስ ድንጋጤ! (አቤ ቶኪቻው)


እንግዲህ ይህ ከሆነ አመቱ ሆነ አይደለ… ቅዳሜም ቅዳሜ፣ እሁድም እሁድ ነው እና ምናልባት ካልተገናኘን… እንዳንረሳው፤ ከወዲሁ ቀኑን እንደሚከተለው እንዘክረው… (በቅንፍም ኤድያ እነ እንትናዬ ደግሞ ሊበሳጩብኝ ነው… (በሌላ ቅንፍ እንግዲህ ይቻሉት እኛ ስንቱን ችለነው የለ…))

Melese Zenawi
በመጀመሪያም፤
ብስጭቴ
እኔ እኮ የምለው ሰው አይኑ እያየ የሰራውን ስራ እያወቀ ወደ አሜሪካ ለዛውም ወደ ዋሽንግተን ዲሲ ይሄዳል እንዴ!? እውነቱን ለመናገር እኔ አቶ መለስ ዜናዊን ብሆን ኖሮ ዲቪ እንኳ ቢደርሰኝ ሀገር ይቀየርልኝ እላለሁ እንጂ አሜሪካ አልሄድም። እነ ቻይና ባሉበት አለም እነ ሰሜን ኮሪያ በሚኖሩበት ምድር ሰው እንዴት ወደ አሜሪካ ይሄዳል? (ይቅርታ ሰው በሚል የተጠቀሱት ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ነው)

ዋናው ወሬ፤
የሆነው ሆኖ ትላንት በዋሽንግተኑ ስብሰባ አቶ መለስ ዜናዊ ሲመጡ ከውጪ ያለውን የተቃውሞ ድምፅ በመከራ አልፈው የስብሰባ አዳራሽ ውስጥ ከገቡ በኋላ ደግሞ ጋዜጠኛ አበበ ገላው ተሰብሳቢው ፊት፤ ከውጪ ያለው ህዝብ በሰላማዊ ሰልፍ፣ እንዲሁም አዲሳባ ያለው ህዝብ ደግሞ በሰላማዊ ዝምታ በሆዱ ምን እያላቸው እንደሆነ ነጥብ ነጥቡን ነግሯቸዋል። እንደው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነውብኝ እንጂ “እስከ ዶቃ ማሰሪያቸው ድረስ ነግሯቸዋል!” ብል የበለጠ ይገልፀዋል መሰል!
የጋዜጠኛ አበበ ገላው ድርጊት ከዚህ በፊት ጆርጅ ቡሽ ላይ ጫማ ከወረወረው ጋዜጠኛ ጋር የሚቀራረብ ይመስላል። እንደውም በቪዲዮ እንዳየኋቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ የደረሰው የቅስም ስብራት “በጫማ መመታት በስንት ጣዕሙ!” ያሰኛል።
ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በስፍራው የተገኙት በባራክ ኦባማ ጋባዥነት ከቡድን ስምንት ሀገሮች ጋር ስብሰባ ሊቀመጡ እንደሆነ ባለፈው ግዜ አውርተናል፤ ከቡድን ስምንቱ ስብሰባ አንድ ቀን ቀደም ብሎ ታድያ  “ግሎባል አግሪካልቸር ኤንድ ፉድ ሴኪዩሪቲ” በተባለው ስብሰባ ላይ ቁጭ ብለው እንደተለመደው ፐርሰንታቸውን እየጠቀሱ ሳለ ድንገት አበበ ገላው፤ “መለስ ዜናዊ…” ብሎ ሲጠራ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን “የደነገጡት መደንገጥ… ከአንድ ታጋይ የሚጠበቅ አይደለም” ሲሉ አስተያየት የሰጡ አሉ። እኔም እንዳየሁት ጆሯቸውን ማመን አቅቷቸው “የድርጅቴን ብቅል እየፈጨሁ ነው…” ብለው ሊያልፉት የከጀሉ ሁሉ መስሎኝ ነበር።
ብቻ በጣም ክው ማለታቸውን ፊታቸው አሳበቀባቸው። ከዛ እንደምንም ተረጋግተው…“ሰበንቲ….ፐርሰንት” ብለው ንግግራቸውን ሊቀጥሉ ሲሉ የጋዜጠኛ አበበ ገላው ድምፅ ከመጀመሪያው ከፍ ብሎ “መለስ ዜናዊ ኢዝ ኤ ዲክታተር…” ማለቱን ቀጠለ አሁን ትንፋሽም ቃልም አጠራቸው። አስተያየታቸው “ምነው ዛሬ እግሬን በሰበረው!?” የሚሉ ይመስላሉ። ግን እንደምንም ብለው ለመቀጠል ሞከሩ። ድምፃቸውን ከአበበ ድምፅ ከፍ ለማድረግ እየጣሩ “ሰበንቲ…ፐርሰንት” አልቻሉም። “ምን ላይ ነበር ያቆምኩት…?” ለማለት የፈለጉ ይመስላሉ ባልንጀሮቻቸውን ቃኘት ቃኘት አደረጉ። እነርሱቴ “ራስህ ተወጣው!” ሳይሏቸው አይቀሩም… አበበ ቀጥሏል። “መለስ ዜናዊ ኢዝ ኤ ዲክታተር….” አሁን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከኛ በላይ ድምፅ ላሳር በሚመስል መልኩ ከአበበ በላይ ጮክ ብለው እና ድፍረታቸውን አሰባስበው፤ “ሰበንቲ ፐርሰንት ኦፍ ዘ ፖፕሌሽን ኢን አፍሪካ….” አሉ። ብሽሽቅ ነው የሚመስለው እንጂ የንግግራቸው አካል አይመስልም!
ድጋሚ አቋረጡ አበበ ግን የሚያቋርጥ አይመስልም በእንግሊዝ አፍ “እስክንድር ነጋ እና ሁሉም የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ፤ ምግብ ያለ ነፃነት ዋጋ የለውም! መለስ ዜናዊ አምባ ገነን ነው!” ብሎ እንቅጩን ነገራቸው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁና ቁና ሲተነፍሱ ኮምፒውተሬን አልፎ ሁሉ ይሰማ ነበር። በሆዴ “ይበልዎት አይሂዱ አላልኮትም ነበር!?” ብልም እውነቱን ለመናገር ግን አንጀቴን በልተውታል።
አቶ መለስ ከትላንትናው የበለጠ  ቅዳሜ ደግሞ ሌላ ተቃውሞ እንደሚጠብቃቸው ጭምጭምታ ሰምቻለሁ። ከዋሽንግተን ዲሲ ወጣ ብሎ የሚገኘው ካምፕ ዴቪድ ድረስ ህዝቡን ለማመላለስ የተሰናዱ አውቶቡሶች መኖራቸውን የደረሰኝ ጭምጭምታ ያስረዳል።
እኔማ የሚሰማኝ አጣሁ እንጂ ቀድሞውኑም ይሄ ስብሰባ ይቅርብዎ ብዬ ነበር። ይሄን ግዜ እርሳቸውም በሆዳቸው “ምነው ምነው ምነው በቀረብኝ” የሚለውን ሙዚቃ ሊያዜሙ እንደሚችሉ እጠረጥራለሁ። ምንም ጠቅላይሚኒስትር ቢሆኑ ሰው አይደሉ እንዴ…!? ምክሬን ባለመስማታቸው መፀፀት ካልቻሉ እውነትም ሰውየው ጠቅላይ ሚኒስትር እንጂ ሰው አይደሉም ማለት ነው!
ይህንን የጠቅላይ ሚኒስትሩን ቅስም ስብራት የሰማ አንድ ወዳጄ “ይሄኔ ጥሩ አዝማሪ ቢገኝ ይቺን ግጥም በል እስቲ ተቀበል ብሎ ማቀበል ነበር” ብሎኛል…
“አፄ መለስ ዜና እጅግ ተዋረዱ
ምግብ ብለው መጥተው አንጀት በልተው ሄዱ
አንተ አበበ ገላው እንደምን ቻልካቸው
መለስ ቀለስ ሲሉ ጎንበስ አረካቸው”
(አረ ጎበዝ ዜማ ፈልጉና ይችን ነገር ነጠላ ዜማ አደርገን እንልቀቃት በስንት ግዜ የተገኘ የግጥም አዚምን እንጠቀምበት እንጂ!)
በነገራችን ላይ ከዚህ ጋር በተያያዘ አንዳንድ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚሰጡት አስተያየት ከሆነ አቶ መለስ አዲሳባ ሲገቡ ወይ በጭፈራ ሞቅ ደመቅ አድርገን ካልተቀበልናቸው ወይ ደግሞ ለጥ ብለን ተኝተን ካልጠበቅናቸው በብስጭት ሊጨርሱን ይችላሉ ሲሉ ስጋታቸውን ገልፀዋል።
በመጨረሻም
ኦባማ ግን አራዳ መሆናቸው ነው ሰውየውን ጠርተው ልክ ልካቸውን የሚያስነግሯቸው!? የምር ሽምቅቅ አደረጓቸውኮ! (እኔ ልሸማቀቅ… ልላቸው ነበር አሁንማ አንዴ ጀምረውታል… ይወጡት እንግዲህ!)

No comments:

Post a Comment