Translate

Monday, May 20, 2013

ግንቦት 7 የፖለቲካ ድርጅት እንዳልሆነ ያውቁ ኖሯል?


አሰፋ ከዳላስ

ባለፈው ቅዳሜ ግንቦት 3፣ 2005 (May 11, 2013) በዳላስ ከተማ በተዘጋጀው የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌ ቪዥን (ኢሳት) የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ላይ ተገኝቼ ነበር:: እጅግ በጣም የተሳካ እና የደመቀ ፕሮግራም ነበር:: ታዲያ በዝግጅቱ ላይ ትኩረቴን የሳቡት ብዙ ነገሮች ቢኖሩም በዚች አጭር ፅሁፌ የማተኩረው የፕሮግራሙ ተሳታፊዎች ያነቧት ዘንድ ተሰራጭታ በነበረችው እና እኔም እጅ በገባችው አንዲት በራሪ ወረቀት ላይ ነው::Ginbot 7 press release in Amharic
ይቺ አንድ ገፅ በራሪ ፅሁፍ ስለ ግንቦት 7 ድርጅት የምታወራ ሲሆን ርዕሷም ግንቦት 7ን ያውቁት ኖሯል? የሚል ነው:: በበራሪ ወረቀቷ ላይ እንደተጠቀሰው “ግንቦት 7 ከሌሎች የፖለቲካ ድርጅቶች የሚለይበትን ዋና ነጥብ ተረድተዋል?” ይልና እንደ ምክንያትም “ግንቦት 7 የትምህርት: የኢ ኮኖሚ: የውጪ ጉዳይ… ወዘተ ፖሊሲ የለውም” በማለት ያትታል:: ርግጥ ነው አንድን ድርጅት የፖለቲካ ድርጅት ከሚያሰኙት ነገሮች ውስጥ ከላይ የተጠቀሱት ነጥቦች እንደሚገኙበት አያጠራጥርም::

ከላይ በጠቀስኳት በራሪ ፅሁፍ ላይ የተገለፁት ነጥቦች እንደተጠበቁ ሆነው በእኔ ግምት ግንቦት 7ን ከሌሎች የፖለቲካ ድርጅቶች የሚለየው ዋናው ምክንያት የፖለቲካ ድርጅት ባለመሆኑ ይመስለኛል:: ይህን ስል ግንቦት 7 ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ድርጅት አይደለም ለማለት እንደማይዳዳኝ አንባቢ እንደሚገነዘብልኝ እርግጠኛ ነኝ:: በአንድ ሀገር ውስጥ ፍትህና: ዲሞክራሲ እንዲሰፍን: የህግ የበላይነትና የመንግስት ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ የሚታገልን ድርጅት ፖለቲካዊ ይዘት ወይንም ፖለቲካዊ አላማ የለውም የሚል ሰው ካለ የሚናገረውን ነገር የማያውቅ ብቻ ነው:: እኔ ግንቦት 7 የፖለቲካ ድርጅት አይደለም ስል የፖለቲካ ፓርቲ አይደለም ማለቴ ነው::
ለመሆኑ የፖለቲካ ፓርቲ ማለት ምን ማለት ነው? የፖለቲካ ሳይንስ ምሁራን ይቅርታ እንደሚያደርጉልኝ ተስፋ አደርጋለሁ:: ከተሳሳትኩም ለመታረም ዝግጁ ነኝ:: እኔ እንደገባኝ የፖለቲካ ፓርቲ ማለት በአንድ ሀገር ውስጥ ወይንም በአንድ ፖለቲካዊ ማህብረሰብ ውስጥ በየደረጃው ያለ የመንግስት ስልጣንን ለመያዝ የሚጥር ይህንን ለማሳካትም የራሱን ፕሮግራምና ስትራቴጂ ቀይሶ የሚንቀሳቀስ የሰዎች ስብስብ (ድርጅት) ነው:: ይህ ከሆነ አንድ የፖለቲካ ድርጅት የመንግስት ስልጣን ለመጨበጥ ከሌሎች ተመሳሳይ አላማ ካላቸው የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር መወዳደር አለበት:: ፕሮግራሙን ለህዝብ ማሳወቅ አለበት:: ህዝብን ማሳመን አለበት (በጠመንጃ ወይንም በሀይል የመንግስት ስልጣን ስለሚያዝበት ህብረተሰብ ካላወራን በስተቀር ማለቴ ነው)::
በእኔ የፖለቲካ ፓርቲ ምንነት (Definition) ላይ ከተስማማን የፖለቲካ ፓርቲ በአንድ ሀገር ውስጥ አለ ለማለት 3 ነገሮች መሟላት አለባቸው::
1. የዚያ ድርጅት ዋና አላማ (ግብ) የመንግስት ስልጣን መያዝ ከሆነ
2. ድርጅቱ መወዳደርና ፕሮግራሙን ለህዝብ ማሳወቅ የሚችልበት የተመቻቸ ሁኔታ ካለ
3. ድርጅቱ መወዳደር ብቻ ሳይሆን ተወዳድሮ ካሸነፈ የመንግስት ስልጣንን የሚረከብበት የተመቻቸ ሁኔታ ካለ
የመጀመሪያውን ቅድመ ሁኔታ በተመለከተ እኔ እስከሚገባኝ ድረስ የወቅቱ የኢትዮጵያ ችግር ያገባናል በማለት የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች በተለይ በውጪ የሚገኙት አንዳቸውም ዋና አላማችን (ግባችን) የመንግስት ስልጣን ለመያዝ ነው ሲሉ አይደመጡም:: 2ኛ እና 3ኛ ላይ የተቀመጡት ሁኔታዎች ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሌሉ ግልፅ ነው:: እንግዲህ በኔ ስሌት ኢትዮጵያ ውስጥ በአሁኑ ወቅት የፖለቲካ ፓርቲ የለም ወይንም ሊኖር አይችልም ማለት ነው::
ብዙ ግዜ ከማውቃቸው ሰዎች ጋር ስለ ግንቦት 7 አንስተን ስንጫወት ግንቦት 7 የፖለቲካ ድርጅት (ፓርቲ) አይደለም ስላቸው ብዙዎቹ ግራ ይገባቸዋል:: ይህንን የምልበት አንዱና ዋናው ምክንያት እራሱ ግቦት 7 ያስቀመጠውን ፕሮግራም በማየት ነው:: ከላይ እንደገለፅኩት ከወቅቱ የኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ሲታይ የፖለቲካ ፓርቲ የለም ወይንም ሊኖር አይገባም ብዬ ስለማምንም ነው:: ግንቦት 7 በፕሮግራሙ ኢትዮጵያ ውስጥ መወዳደርም ሆነ ሀሳብን ማራመድ ተወዳድሮም በሀሳብ ማሸነፍ የማይቻል መሆኑን: በሀገሪቱ ላይ የሃይል አገዛዝ የሰፈነ መሆኑን በማያሻማ መልኩ ያስረዳል:: የግንቦት 7ን ፕሮግራም ላነበበ ሁሉ የድርጅቱ ዋና አላማ (ግብ) የመንግስት ስልጣን መያዝ ሳይሆን የመንግስት ስልጣን በምርጫ ብቻ የሚያዝበትን ሁኔታ በሀገሪቱ እንዲመቻች መታገል መሆኑን በግልፅ ይረዳል::
የሁሉንም ድርጅቶች ፕሮግራም ጠንቅቄ ባላውቅም የግንቦት 7ን ያህል ኢትዮጵያ የገባችበትን አጣብቂኝና የተጋረጠባትን ፈተና በአግባቡ የተረዳ ያንንም በፕሮግራሙ ላይ ቁልጭ አድርጎ ያስቀመጠ መኖሩን እጠራጠራለሁ:: ይህም ግልፅነት የመነጨው በኔ ግምት ነነፃነት እና ፍትህ በአንድ ሀገር ላይ እንዲሰፍን መታገል: የፖለቲካ ፓርቲ ሆኖ ስልጣን ላይ ለመውጣት ከሚደረግ ትግል ጋር የተለየ መሆኑን በሰከነ መንፈስ ከመረዳት ይመስለኛል፡፡ ርግጥ ነው የአላማ ጥራት ብቻውን የሚፈለገው ውጤት ላይ ለመድረስ በቂ አይደለም:: ያንን ያስቀመጡትን አላማ ከግብ ለማድረስ ብዙ ጥረት ማድረግን ይጠይቃል:: ነገር ግን ችግሩን በአግባቡ ተረድቶ ለችግሩ መፍቻ የሚሆን እቅድና አላማ በግlልፅ ማስቀመጥ ሊታለፍ የማይገባው የመጀመሪያ ርምጃ ነው:: እንደ እኔ ከሆነ ግንቦት 7 ይህንን የመጀመሪያ ርምጃ በተሳካ መልኩ ተራምዷል::
እኔን ግራ የሚያጋቡኝ እራሳቸውን የፖለቲካ ፓርቲ እያሉ የሚጠሩት ናቸው:: የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድን ድረገፅ ስንመለከት በምርጫ ቦርድ የተመዘገቡ 79 ‘የፖለቲካ ፓርቲዎች’ ይገኛሉ:: ይህ እንግዲህ በሀገር ውስጥ ያሉትን ብቻ እንጂ ከሀገር ውጪ ራሳቸውን ‘የፖለቲካ ፓርቲ’ ብለው በመጥራት የሚንቀሳቀሱትን አይጨምርም:: ምክንያቱም የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ከሀገር ውጪ የሚገኙ ድርጅቶችን በፖለቲካ ፓርቲነት የሚመዘግብ አይመስለኝም:: መቼም ከነዚህ መካከል በልጣን ላይ ያለው ቡድን ለስም ያስቀመጣቸው ለኖሩ እንደሚችሉ መገመት ከባድ አይደለም:: ሌሎቹስ በራሳችን ተቋቁመናል የሚሉት ርግጥ በሀገራችን ተጩባጭ ሁኔታ በፖለቲካ ፓርቲነት መንቀሳቀስ ውጤት አለው ብለው አምነውበት ነው?
የመወዳደሪያ ሜዳ በሌለበት በሌለበት: የመሮጫው ህግ ባልተወሰነበት: ያለውም ህግ በማይከበርበት ሁኔታ እነዚህ ቅድመ ሁኔታዎች እንዲመቻቹ በጋራ መስራት ነው ወይንስ እየተነሱ መሮጥ ነው የሚቀድመው? በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ እራሳቸውን የፖለቲካ ፓርቲ እያሉ የሚጡሩት እነዚህን ነገሮች ያሰቡባቸው አይመስለኝም:: በበኩሌ ከፈረሱ ጋሪው ቀድሟልና ይታሰብበት::
በነገራችን ላይ የግንቦት 7 አድናቂ እንጂ አባል አይደለሁም::

No comments:

Post a Comment