Translate

Monday, May 20, 2013

አሸባሪው ማን ነው?


አሸባሪው ማን ነው?


Author and writer Tesfaye Zenebe from Norway
ከተስፋዬ ዘነበ (ኖርዌይ በርገን)
ከሳምንታት በፊት በልእለሀያሏ አሜሪካ በቦስተን ከተማ የደረሰውን በአሸባሪዎች ጥቃት ህይወታቸውን ላጡና  ከባድና ቀላል የአካል ጉዳት ለደረሰባቸው የሃገሪቱ ዜጎች በህዝብ ይሁንታ ስልጣን ላይ ያሉት ፕሬዘዳንት ባራክ ኦባማ በሰላማዊ ህዝብ ላይ ለደረሰው አደጋ ሀዘናቸውን ለመግለፅና የወንጀሉን ፈፃሚዎች በቁጥጥር  ስር ለማዋል መመሪያ ሲሰጡ ሰዓታት  እንዳልወሰደባቸው ስንመለከት ወራት አልተቆጠረም፡፡በመሰረቱ ይህንን ዘግናኝ ጥቃት የፈፀሙት ፅንፈኛ አክራሪዎች ብዙም ሳይቆዩ በሃገሪቱ የፀጥታ ሃይሎች ታድነው በአጭር ጊዜ ውስጥ መያዛቸው ለሕዝቡ ታማኝ  የሆነ መንግስት ዜጎቹን ከጥቃት ለመታደግ ምን ያህል እረፍት እንደሌለው የሚያመላክት ነው፡፡
ከላይ እንደመነሻ ያነሳሁት ሃሳብ ለዛሬው ፅሁፌ እንደ መንደርደሪያ እንዲረዳኝ እንጂ እውነተኛው የዲሞክራሲያዊ ስርዓት አራማጆች ለዜጎቻችቸው የሚሰጡት ክብር የሚሳት ሆኖ አይደለው፡፡

ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን ከቃል በዘለለ በተግባር የማያውቁት የወያኔ ቡድን፣ ፍትህና እርህትህ፣ ነፃነት ላጣው ሕዝብ ለውጥ ለማምጣት አጥንታችንን ከሰከስን ደማችንን አፈሰስን የሚሉት የዛሬዎቹ አምባገነን መሪዎች፣ የብሄር ብሄረሰቦችን  መብት በኢትዮጲያ፣ ለማስፈን ደከመን ሰለቸን ሳንል ታተርን የሚሉን ጥቂት ዘረኛ ቡድኖች፣ ሃገሪቷንም  ሕዝቧንም በሁለት አሃዝ በልማት አሳደግን ብለው ቀን ከሌት የሚደሰኩሩልን ጥቂት የዘረኛ ቡድን ሞኖፖሊስቶች፣ ከወረቀት ያልዘለለ የመናገርና አሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት አጎናፀፍን የሚሉን የዛሬዎቹ ተሸባሪ ሽብርተኞች በጀሌዎቻቸው የንፁሃን ደም ማስፈሰስ  የሰነበቱበት የሃያ ሁለት አመት ተግባራቸው ቢሆንም በዚህ ሰሞን በባህር ዳር የተፈጸመውን ጅምላ ፍጅት በሙት መንፈስ አራማጁ በአቶ ሃይለማርያም ደሳለኝም ሆነ እሱን በሚመሩት የህውሃት ቡድኖች ምንም አለመባሉ ይህ እኩይ  ሰርዓት ምን ያህል የሕዝብ ንቀት እንዳለበት ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ እውነት ነው፡፡
ስለዚህ  ዘረኛ ስርዓት ብዙ ቢባልም በየጊዜው በህዝብ ላይ በሚያደርሳቸው ግድያዎችና የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እንዲሁም በሃገር ላይ የሚያደርሳቸውን መጠነ ሰፊ ችግሮች በተመለከተ ከሃገርና ከሕዝብ ወገኖች ተቃውሞ ሲደርስበት ወይንም ሰራሗቸው እያለ ከሚመፃደቅባቸው ልማት ተብዬዎችን አስመልክቶ ከሚሰግድላቸው ምህራባዊያን ሃገሮችም ሆነ ከአበዳሪ አለም አቀፍ ተቋማት ጋር የሚወዛገበው በቁጥር ጨዋታ መሆኑ ስርዓቱ ምን ያህል ግትርና ሞራለ ቢስ መሆኑን አመላካች ነው፡፡
የወያኔ ዘረኛ ቡድን  ከእድሜው መጀመሪያ ጀምሮ በዚች ሃገር ንፁሃን ዜጎች ላይ ለፈፀመው ፍጅት (ግድያዎች) አንድም ጊዜ በህግ የተጠየቀ አካል ካለመኖሩም ባሻገር የሟቾቹን ቁጥር በማሳነስ በዚህ አሸባሪ ስርዓት የተሰዉ ሰማህታት ቤተሰቦችንና ሕዝብን በመናቅ ሲሳለቁ መመልከት አዲስ ክስተት አይደለም፡፡ ሰሞኑን በባህር ዳር ከተማ የሆነውም ካለፈው ያልተማረው የወያኔ አምባገነን ቡድን የሆደበት የማደናገሪያ ተልካሻ ስልት መሆኑ ይህ ስርዓት በማን አለብኝነት የንፁሃንን ደም መጠጣቱ እንደቀጠለበት የሚያሳይ እውነት ነው፡፡
የጠለቀ ጥላቻ በዚች ታላቅ ሃገር ላይ ያለው ዘረኛው የህውሃት ቡድን ኢትዮጲያዊ መንፈስን ከሕዝብ ለመንጠቅ አንዱን ከአንዱ ለመለየት፣ በጎጥና በዘር እንዲሁም በእምነት ለመከፋፈል ሌት ከቀን ዘመኑን ሙሉ ለፍቷል፡፡ ሕዝብ አንድነትና ሕብረት እንዳይኖረው ውስጥ ውስጡን ሲያበጣብጥ፣ በዘር በተለከፉ ጀሌዎቹ አንዱን በአንዱ ላይ ለማስነሳት የሽብር ተግባር ሲከውኑ፣ በሌላ በኩል ደግሞ መጠሪያው የኢትዮጲያ ሕዝብ የሆነ ግን ደግሞ በሆድ አደር ካድሬዎች በሚመራው የሕዝብ ሃብት በሆነው ቴሌቪዥንና ሬድዮ ድርጅት  በኩል የፈጠራ ፕሮፓጋንዳ በመፈብረክ  የብሄር ብሄረሰቦች መብት መከበሩን ለማሳየት የሀሰት አታሞ ሲደልቅ ይታያል፡፡
በመሰረተ ሃሳብ ደረጃ ሸብር ማለት በማንም ይፈፀም በማን ሰላማዊውን ሕዝብ የሚያውክ፣ የተረጋጋ ህይወትን የሚረብሽ፣ የንፁሃንን ህይወት የሚቀጥፍ፣ ሕዝብን ያለፈቃዱ ከቀዬውና ከመንደሩ የሚያፈናቅል፣ የሰው ልጅ በተፈጥሮ የተቸረውን ነፃነት የሚቀማ፣ በሕዝብና በሃገር ላይ ጥፋትና ውድመትን የሚያስከትል . . . . .ወዘተ ከላይ በመጠኑ የተዘረዝሩት ሁሉ የዚህ ዘረኛ ቡድን መገለጫዎች መሆናቸው እንኳን ከሕዝብ ወገን ለተሰለፉ ነፃነት ናፋቂዎች ቀረቶ ስብእናቸውን ሸጠው ለሆዳቸው ላደሩት ለስርዓቱ ጀሌዎችም ቢሆን የሚጠፋቸው አይደለም፡፡  የሚገርመው ግን  ይህው እኩይ ስርዓት በሕዝብና በሃገር ላይ የሚፈፅመውን በደልና ግፍ እንዲሁም ዜጎች የሚደርስባቸውን የመልካም አስተዳደር ችግርና የሰብአዊ መብት ጥሰትን በብእራቸው ነቅሰው የሚዘግቡትን ለሞያቸው ስነምግባር እንዲሁም ለሕዝብና ለሃገር ቅድሚያ የሚሰጡትን ጋዜጠኞች፣ በህግ አግባብ የመደራጀት መብታቸውን ተጠቅመው አማራጭ አሳብ በማስቀመጥ በሰላማዊ መንገድ የታገሉ የህዝብ ልጆችን፣ በተጨማሪም በሃገሪቱ ህገ-መንግስት በተደነገገው መሰረት የእምነት ነፃነታቸውን በዚህ ከፋፋይ ስርዓት ለመነጠቅ ፈቃደኛ ያልሆኑ፣ መብታቸውን ፍፁም ሰላማዊ በሆነ መንገድ እየሞቱና እየተገረፉ ትግላቸውን ከአንድ አመት በላይ ያራመዱ የሙስሊሙ ማህበረሰብ የመፍትሄ አፈላላጊ መሪዎች፣ እነዚህ ከላይ ልዘረዝር የሞከርኳቸው ፍፁም ሰላማዊ የህብረተሰብ ክፍሎች በአሸባሪውና ተሸባሪው ዘረኛ ቡድን በተቆጣጠረው ነፃነት አልባው የፍትህ ስርዓት በአሸባሪነት ተፈርጀው በየማጎሪያው ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን በሃገሪቱ የተለያዩ ክልሎች የንፁሃንን ህይወት በጠራራ ፀሃይ የሚነጥቀውና የሕዝብን ሰላማዊ ኑሮ ላለፉት ሃያ ሁለት አመታት የሚያውከው የህውሃት ዘረኛ ብድን በምግባር አሸባሪነቱ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡
መቼም ህውሃት ውጥረት በነገሰበትና በደል ፅዋው ሞልቶ ተቃውሞ ሲበረታበት የሕዝቡን አመለካከት ለማስቀየር በስልጣን ዘመኑ ብዙ ተልካሻ ምክኒያቶችን ሲሰራ እንደ ነበረ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ በተለይ በአሁኑ ሰዓት የኢትዮጲያ አንድነት ለማፍረስና ለመበተን የስርዓቱ ሴረኝነት የበልጥ አግጥጦና አፍጦ የታየበት  ጊዜ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ በተለይ በአማራው ብሄር ተወላጆች ላይ የከፈተው ጥቃት ኢትዮጲያን እንደ ሃገር ያላት ታላላቅ እሴቶች ለማጥፋት የታለመ መሆኑ ማስረጃ አይቻውም፡፡ ይህንን ተከትሌ የተነሳውን በአለም አቀፍ  ደረጃ  በነፃ ሃገር ላይ የመናገርና ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብታቸውን ተጠቅመው በሃገራችውና በወገናቸው ላይ የሚደርሰውን በደልና ግፍ የስቆጣቸው ኢትዮጲያዊያን ያሳዩት ተቃውሞና ሆነ ውግዘት አንገቱን ያስደፋው ዘረኛ ቡድን ሰሞኑን ደግሞ የሕዝብን መነሳሳት አቅጣጫ ለማስቀየር የመጣበት መንገድ ግርምትን የሚፈጥር ነው፡፡ በመሰረቱ የአሳ ግማቱ ከወደ አናቱ የሚለውን የአበው ብሂል ያስታውሰናል፡፡ እንደሚታወቀው የስርዓቱ ቁንጮዎች ከራስ ፀጉር እስከ እግር ጥፍር የሰጠሙበት ሙስና፣ ከድሃው ሕዝብ ጉሮሮ ነጥቀው የበለፀጉበት ሙስና፣ ገዢዎቻችን በስልጣን ዘመናቸው በደሃው ሕዝባችን ስም ለምነው ካገኙት ገንዘብ 11ቢሊዮን ዶላር በላይ ነጥቀው ያሸሹበት ሙስና፣ እነኚሁ ዘረኛ ገዢዎቻችን በኢፈርት(EFFORT-Endowment Fund For the Rehabilitation of Tigray) ስም የሃገሪቱን የንግድ እንቅስቃሴ እንደ ሸረሪት ድር ተብትበው የንግድና እንደስትሪውን ካፒታል ሳይጨምር ከ50ቢሊዮን ብር በላይ ቋሚ ሃብት ባለቤት የሆኑበት በጥቂት የህውሃት ሰዎች የሚሸከረከር ሙስና፣ ይህንንና እጅግ ብዙ የሙስና ንቅዘቶች ያለበት ስርዓት የተወሰኑ ጭፍሮቺን የውም በብሄር ለክቶ አስሮ ሙስናን አጠፋለሁ እያለ የዛን መከረኛ ሕዝብ ጆሮ ያደነቁራል፡፡
የአፍሪካን አንድነት ስንመሰርት ነፃ የነበርን ዜጎች ከአምሳ አመት በሗላ የሗሊት ተጉዘን በዘረኞች መዳፍ ስር ወድቆ መገኘት በዜግነት ክብራችን ላይ አሉታዊ ተፅኖ ያሳድራል ስለሆነም በአንድም ይሁን በሌላ መንገድ የሃገርና የሕዝብ ጥቃት የሚሰማን እስከ ወኔያችን እስከ ቤሄራዊ ስሜታችን ያለን እራሳችንን ሃገራችንን ከግዞት ነፃ ማውጣት ይጠበቅብናል፡፡
በተጨማሪም ግንቦት 17 ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ በመገኘት የሕዝብ ይሁንታ በሌለው ዘረኛ ቡድን የሚደርስብንን አፈናና የሰብአዊ መብት ጥሰት ለአለም አቀፉ ህብረተሰብ እናጋልጥ፡፡ ከአመት በላይ ድምፃችን ይሰማ እያልን በሰላማዊ መንገድ ስንታገል በአሸባሪነት ተፈርጀን መብታችንን የተነጠቅን የሙስሊሙ ማህበረሰብ ይህንን ሰልፍ በመቀላቀል ለለውጥ በአንድነት መቆማችንን እናረጋግጥ፡፡
ድል  ለኢትዮጲያ  ሕዝብ!!!!
ሞት  ለወያኔ!!
Ethiocenter.blogspot.com

No comments:

Post a Comment