Translate

Tuesday, August 1, 2017

ደባርቅ፦ጎንደር ግብር አንከፍልም ብሏል * ለማይወክለን መንግስት ግብር አንከፍልም

ከአስናቀው አበበ
የሠሜን ተራሮች መገኛ የሆነችው ደጋማዋ ከተማ ደባርቅ ወገብ በሚሰብር የግብር ጭማሬ ውሳኔ እየተረበሸች ትገኛለች፡፡ የዳባት ከተማን ጨምሮ ብዙ የወረዳ ከተሞች ተመሳሳይ ትርምስ አለ። ደባርቅ ዓመቱን ለነፃነት የተሰው ልጆቿን እያሰበች፣ ከቱሪስት የምታገኘውን ገቢ እንኳን ቅጥ ባጣው የወያኔ ኮማንድ ፖስት እንዳታገኝ የተደረገች፣ የዕለት ጉርሳቸውን ከበቅሎ ኪራይ፣ ከቱሪስት አስጎብኝነት እንዲሁም ከመኪና ኪራይ የሚያገኙ ልጆቿ ተጨማሪ እሴት ታክስን ጨምራችሁ ክፈሉ ተብሎ ተወስኖባቸዋል።
ትላንት ባልነበረ አሰራር የዓመታዊ ግብርን እንድትከፋሉ በሚል ማስፈራሪያ አዘል ዓለም የተረዳውን ዓመታዊ የቱሪስት ፍሰት ያላገናዘበ የግብር ጫና ሲጭኑበት ከቀየው ተፈናቅሎ ወደ ከተማ የገባውን የሰሜን ነጋዴ ደግሞ ለሆዳቸው እና ለወያኔ ባደሩ የከተማው የገቢዎች ኃላፊ እና ሌሎች ባለሙያዎች አማካኝነት እናንተ ካልከፈላችሁ የንግድ ድርጅታችሁን እናሽጋለን በማለት እያስፈፈራሩት ይገኛል፡፡
የሰሜኑ ፈርጥ የደባርቅ ግብር ከፋይ ግን ቅሬታውን በማቅረብ በግፍ የተጫነበትን የወያኔ ጠብመንጃ እና የወገኖቹ መግደያ የሆነውን የተጭበረበረ ግብር እንደማይከፍል በግልፅ ያሳወቀ ሲሆን በቀጣይም የተቃውሞ መግለጫ የሆኑትን እርምጃዎች በመውሰድ ከአምቦ (ከኦሮምያ ከተሞች )፣ ከአዲስ አበባ እንዲሁም ከጎጃም ወገኖቹ ጎን ለመቆም ዝግጅቱን ጨርሷል። ለመሳሪያ እና ለሞታችን ማፋጠኛ የሆነን የግብር ውሳኔ አንቀበልም።
ይህ ተጨምቆ የቀረበው ሃሳቡ የህዝብ ነው። ለዚህ ዘገባ አስጎብኝዎችን፣ ነጋዴውን ማህበረሰብ እንዲሁም ባለሙያዎችን አናግረናል። ህ/ሰቡ ብሶቱን የሚገልፅበት የአንድነት ጊዜን ይፈልጋል። ይህ ደግሞ ዳባት/ወገራ በተመሳሳይ እንደሆነ በደንብ ይታወቃል። ለሁሉም አይነት አድማዎች ህ/ሰቡ ዝግጁ መሆኑን ማወቅ ተችሏል።
ገቢዎች ግብር ይሰበስባል በሚሰበሰበው ገቢ ግን የልማት ተጠቃሚነቷ ዝቅተኛ የሆነች ከተማ እንደሆነች፣ መብራት ውሃ በየጊዜው እንደሚቋረጥ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤቶቿ ያረጁ፣ ሁለተኛ ደረጃ ት/ርት ቤቱ የቆየ፣ የህዝብ ቤተመፅሃፍቱ ለዘመናት የተዘጋ መሆኑን የተገነዘበው ግብር ከፋይ እራሱን ለሚያጠፉት ጉጅሌዎች መሳሪያ መግዣ የሚሆን ግብር እንደማይከፍል አምርሮ እየተናገረ ነው። የጎንደር ከተማ ህዝብም ለአዲስ ዙር የከተማ አመፅ በቋፍ ላይ ለመሆኑ የምናገኛቸው መረጃወች ያሳያሉ። በመላ ሃገራችን ህዝባችን ቦታ ሳይለየው ይህን የወያኔ ቡድን ከምን ጊዜው በበለጠ በአንድ ልብ በአንድ ድምፅ በቃኝ እያለ ነው።
ከደባርቅ ለቋሚ ዘጋቢያችን ምስጋና ይድረሰው!
ምስል ከክምችታችን የተወሰደ ነው።

No comments:

Post a Comment