Translate

Monday, April 18, 2016

ኢትዮጵያዊነት ነው የሞተው!

(Dr. Bedilu Wakjira )
.
ሰሞኑን በጋምቤላ ክልል በሚኖሩ ወገኖቻችን ላይ በደቡብ ሱዳን ታጣቂዎች አሳዛኝ ጭፍጨፋ ደርሶባቸዋል፡፡ የኮምኒኬሽን ሚንስትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ትላንት (እሁድ) ለሮይተርስ የዜና አገልግሎት በሰጡት መግለጫ የሟቾቹ ቁጥር 208 እንደደረሰና 79 ሰዎች እንደቆሰሉ፣ በርካታ ህጻናት ታፍነው እንደተወሰዱ፣ 2000 ገደማ የቀንድና የጋማ ከብቶች እንደተነዱ ተናግረዋል፡፡
አሶሽየትድ ፕረስ እንደገለጸው፣ ከዚህ መግለጫቸው አንድ ቀን ቀደም ብሎ፣ ሚንስትሩ ጥቃቱን የፈጸሙት የደቡብ ሱዳን ሙርሌ አባላት መሆናቸውንና ከደቡብ ሱዳን መንግስት ጋር ግንኙነት እንደሌላቸው አስታውቀዋል፡፡ ለአልጃዚራም ቅዳሜ እለት፣ "They haven't crossed the border [yet], but they will if that's what it takes" ( የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እስካሁን ድንበሩን አልተሻገሩም፤ አስፈላጊ ከሆነ ግን ያደርጉታል)፡፡ ምን ሲሆን ነው ድንበር ማቋረጥ የሚያስፈልገው? በመሰረቱ ሚንስትሩ የሰጡት አስተያየት የኢህአዴግ መንግስት ስለዜጎቹ ያለውን አቋም ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ እንጂ አዲስ አይደለም፡፡ ቀደም ብሎ አሸባሪው አይ.ኤስ ዜጎቻችንን እንደከብት ሲያርድ፣ በእሳቸው ቦታ የነበሩት ባለስልጣን፣ አለም ኢትዮጵያዊነታቸውን እየመሰከረ እሳቸው፣‹‹ገና ኢትዮጵያዊ መሆናቸው አልተረጋገጠም›› ብለው ነበር፡፡
.
እኔ ለአቶ ጌታቸው ጥያቄ አለኝ፡፡ ታጣቂዎቹ ከደ.ሱዳን መንግስት ጋር ግኝኙነት የላቸውም የሚለው እኛን የሚያሳስብ ጉዳይ ነው? ይህንን መግለጫ መስጠት የነበረበት የኢትዮጵያ መንግስት ወይስ የደ.ሱዳን? የአካባቢው የአይን ዕማኞች ከታጣቂዎቹ መካከል የደ.ሱዳንን ወታደሮች የደንብ ልብስ የለበሱ እንዳሉበትና እስከ አርፒጂ ከባድ መትረየስ የታጠቁም እንደሆኑ ለተለያዩ የውጭ የዜና አገልግሎቶች ተናግረዋል፡፡ የደ.ሱዳንም እስካሁን ድረስ ስለጉዳዩ መግለጫ እንዳልሰጠ ነው የማውቀው፡፡ ኢህአዴግ ጉዳዩን በመንግስት ደረጃ ላለማየት ለምን እንደፈለገ አይገባኝም፤ ሁለቱ ሀገሮች ጦርነት ቢገጥሙ እንኳን ይህን ያህል ሰው በአንድ ቀን የሚሞት አይመስለኝም፡፡ ኢህአዴግ ደ.ሱዳንንም በለመደ የብሄር-ብሄረሰብ መነጽሩ ካልተመለከታት በስተቀር፣ ይህ ወንጀል የደ.ሱዳንን መንግስትንም ያስጠይቃል፡፡
.
በምን ሚዛን ነው አንድ መንግስት የሚያስተዳድረው ህዝብ እንዲህ አይነት ውንብድና ሲፈጽም፣ ከወንጀሉ ነጻ የሚሆነው? የኢትዮጵያ መንግስት በርግጥ ድንበር አቋርጦ 60 ሰው መግደሉን ይፋ አድርጓል፤ ይህ ግን መፍትሄ አይደለም፡፡ ይህ ጥቃት በአካባቢው በተደጋጋሚ እንደሚፈጸም፣ ይህንን ከቀደሙት የሚለየው ብዙ ወገኖቻችን የተጨፈጨፉበት መሆኑ እንደሆነ የውጭ የዜና አውታሮች እየገለጹ ነው፡፡ እና መንግስታችን ለምን እስካሁን እንደልሰማና እንዳላየ ዝም አለ?
.
ሌላው ጥያቄዬ ለክቡር ጠቅላይ ሚንስትራችን ነው፤ ባህር ዳር ጣና ፎረም ስብሰባ ላይ እንዳሉ አውቃለሁ፡፡ አብሮት የተሰበሰበው የሙኒክ ሴኩሪቲ ኮንፍረንስ ሰብሳቢ አንባሳደር ዎልፍ ጋንግ ኢስቺንገር፣ ለረዥም ጊዜ ጀርመንን ያገለገሉና በጡረታ ላይ የሚገኙ ሰው በመሞታቸው ስብሰባውን አቋርጠው ሲሄዱ ተመልክተዋል፤ ለቀብር፡፡ የሁለት መቶ ሰው መሞት ለእርስዎ ስብሰባ ለማቋረጥ በቂ አይደለም? በኦሮምያ አመጽ (በሚዲያ አጣራር ሽብር) ልማቱ ሲደናቀፍ፣ ንብረት ሲወድም ካንዴም ሁለቴ ጋዜጠኛ ሰብስበው መግለጫ ሰጥተዋል፤ የስንት ዜጎቻችን ህይወት ነው ከልማቱ እኩል ዋጋ የሚኖረው? በዚሁ ስብሰባ ላይ ለቀድሞው ጠ.ሚንስትር ክቡር መለስ ዜናዊ የህሊና ጸሎት ተደርጓል፤ እነዚህ ወገኖቻችንስ የህሊና ጸሎት አያሽፈልጋቻም ነበር?

No comments:

Post a Comment