Translate

Wednesday, September 25, 2013

ሰማያዊ ፓርቲ ሕገ-መንግስት አረቀቀ

በረቂቅ ሕገ-መንግስቱ ላይ የውይይት መድረክ ለማዘጋጀት አቅዷል

semayawi 12


በቅርቡ የተመሰረተው የሰማያዊ ፓርቲ ‘‘የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ ለዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ’’ በሚል መርህ ወደፊት የፖለቲካ ሥልጣን ሲይዝ የሚመራበትን አዲስ ህገመንግስት ማርቀቁን አስታወቀ። ረቂቅ ሰነዱ ላይ ምሁራንና ባለሙያዎች ውይይት ካደረጉ በኋላ ለሕዝብ እንደሚቀርብ ፓርቲው አስታውቋል።

የፓርቲው ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት በተለይ ለሰንደቅ ጋዜጣ እንደገለፁት በአዲሱ ረቂቅ ሕገ-መንግስት ላይ አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ውይይት እንደሚደረግ አስታውቀዋል። በውይይቱ ላይ ከዚህ በፊት የነበሩ ሦስት ህገ-መንግስቶች ድክመትና ጥንካሬ ምንድን ነው? አዲስ በሚረቀቀው ህገ-መንግስት ምሰሶዎች ምን ይሆናሉ፣ ስልጣንና ሕዝብን እንዴት ማገናኘት ይቻላል በሚሉ ወሳኝ ንድፈ ኀሳቦች ላይ የጠለቀ ውይይት እንደሚደረግ አስታውቀዋል።
‘‘የአሁኑ ሕገ-መንግስት የኢህአዴግ ፕሮግራም ቅጂ ነው’’ ያሉት ኢንጂነር ይልቃል እያረቀቁ ያሉት ሕገመንግሥት የሰነድ ዝግጅቱም ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁንና ምሁራን በሚያደርጉት ውይይት ከዳበረ በኋላ ለሕዝቡ ውይይት ቀርቦ ለባለሙያዎች ተመርቶ ዝርዝር ህጎች እንዲፃፉ ይደረጋል ብለዋል።
ፓርቲው ሰላማዊ ሰልፍ የሚያካሂደው ሕዝቡን ለማነቃቃትና ለማስተማር አባላትንም ለመመልመል ቢሆንም በተጓዳኝ ፓርቲውን ለማጠናከርና ምን አይነት ስርዓት እንገነባለን የሚለውንም ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑንም ኢንጂነር ይልቃል ገልፀዋል።
ሰማያዊ ፓርቲ ሕገ-መንግስት ባለበት ሀገር ሌላ ሕገ-መንግስት ከማውጣት የሚያግደው ነገር እንደሌለ የጠቀሱት ኢንጂነር ይልቃል፤ ፓርቲው እያካሄደ ያለው ትግል በሕገ-መንግስት የማይመራን አገዛዝ በዲሞክራሲያዊ ስርዓት የመተካት ስለሆነ አዲስ ህገ-መንግስት ማስፈለጉ የግድ ነው ብለዋል።
የፓርቲው ዋና አላማ በሀገሪቱ ሕጋዊ ስርዓትን መትከል በመሆኑ አሁኑ ባለው ሕግ-መንግስት በሚደረግ ምርጫ አብላጫ ወንበር ማግኘቱን ሲያረጋግጥ አዲሱን ሕገ-መንግስት ተግባራዊ ያደርጋል ብለዋል። በዚህ ሀገር ምርጫ ከተካሄደም ሰማያዊ ፓርቲ 99.6 በመቶ አብላጫ ወንበር ለማግኘት የሚያግደው ነገር እንደሌለም እርግጠኞች ነን ሲሉ አያይዘው ገልፀዋል።
ፓርቲው ከፖለቲካና ኢኮኖሚ አማራጭ ፕሮግራም በዘለለ አዲስ ህገ-መንግስት ማርቀቁ ቀዳሚ ተግባር መሆኑን የጠቀሱት ኢንጂነር ይልቃል፤ የፓርቲው አማራጭ ፕሮግራም የሚመነጨው ከረቀቀው ሕገ-መንግስት ነው ብለዋል። አዲሱ ህገ-መንግስት በሀገሪቱ ስለሚኖረው አጠቃላይ ስርዓትና መንግስታዊ አወቃቀር፣ የኢኮኖሚ ፖሊሲ፣ የገበያ ስርዓት፣ ዓለም አቀፍ ግንኙነት፣ የመሬት ፖሊሲ፣ ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ ገዥ ኀሳቦች የሚመነጩት ከህገ-መንግስት እንደሆነ ገልፀዋል። የፓርቲው ፕሮግራም ከህገ-መንግስቱ የሚመነጩ ዝርዝርና ስትራቴጂካዊ አቅጣጫ በመሆኑ ቀዳሚውና ምሰሶው ሕገመንግስት ነው ብለዋል።
‘‘የኢትዮጵያ ችግር መጠነኛ ችግር ሳይሆን አጠቃላይ ሕጋዊ ስርዓት የመትከልና፤ የሁሉም የኢትዮጵያ ዜጎችን መብት፣ ባህል፣ ታሪክን ግምት ውስጥ ያስገባ ስርዓት የማቋቋም ጉዳይ ነው’’ ያሉት ኢንጂነሩ አሁን ካለው ህገ-መንግስት ሊካተቱ የሚችሉት የሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ ድንጋጌዎች እና ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ የፈረመቻቸውን ድንጋጌዎች እንደሆኑም አስገንዝበዋል። ኢህአዴግ ለሀገር ደህንነትና ለህዝብ ጥቅም ሽፋን ከሕዝብ ነጥቆ የወሰዳቸው መብቶች በአዲሱ ህገ-መንግስት እንደሚካተቱ አመልክተዋል። ከኢህአዴግ መሠረታዊ ባህሪ ጋር ተመሳሳይ የሆኑ የሕዝብን አንድነት የሚነኩ፣ የተዛባውን የፌዴራሊዝም ጉዳዮች እንደገና የሚታዩ መሆኑንም ጠቁመዋል።
አዲሱ ህገ-መንግስት በማርቀቅ ሂደት ላይ ታላላቅ ምሁራን የተሳተፉበት መሆኑን ያስረዱት ኢንጂነሩ ውይይቱ በቅርቡ የትና መቼ እንደሚደረግ ፓርቲው ያሳውቃል ብለዋል።
በተያያዘ ባለፈው ዕሁድ ፓርቲው የጠራው ሰልፍ አለመካሄዱን በተመለከተ ኢንጂነር ይልቃል ተጠይቀው ሕጋዊው ስርዓት የውሸት እንደሆነ፣ ኢህአዴግ ትልቅ የህዝብ ፍርሃት እንዳለበትና ሕዝባዊ ተቀባይነቱ ባዶ እንደሆነ የተገነዘብንበት አጋጣሚ ነበር ሲሉ መልሰዋል።
ባለፈው እሁድ መስከረም 12 ቀን 2006 ዓ.ም ፓርቲው የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በመንግስት በኩል ጃንሜዳ ማካሄድ እንደሚችሉ በመግለፅ በአንፃሩ ሰማያዊ ፓርቲ ሰልፉን ለማካሄድ የጠየኩት መስቀል አደባባይ ነው በማለቱ ሰላማዊ ሰልፉ ከፓርቲው ጽ/ቤት በግምት አንድ መቶ ሜትር ከተካሄደ በኋላ ግንፍሌ ድልድይ ላይ በፖሊስ እንዲቋረጥ መደረጉ አይዘነጋም፡፡ (ሰንደቅ)

No comments:

Post a Comment