Translate

Friday, September 20, 2013

ወግ ነው ሲዳሩ ማልቀስ ይባል ነበር ዱሮ ወግ ነው ምርጫ ማሸነፍ ሆነ ዘንድሮ! አስተሳሰብና ጉልበት (ሕገ አራዊት)

ሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም
በረከትን በደንብ የሚያውቀው ያሬድ ጥበቡ ሙልጭ አድርጎ ነግሮታል፤ ያሬድ ከዚህ በፊትም ስለበረከት ጽፎ ነበር፤ አሁን ከጻፈው ጋር ሳስተያየው አንድ ግጥም ትዝ ይለኛል፤ አንዲት የቸገራት ሴትዮ ያንጎራጎረችው ይመስለኛል፡-
mnnnወደድኩህ ወደድከኝ፤ ጠላሁህ፤ ጠላኸኝ፤
እንደሚጣራ ጠጅ እየጣልክ አታንሣኝ!
ያሬድ ስለበረከት በሚጽፈው ሁሉ እያነሣ የመጣልና እየጣለ የማንሣት ዝንባሌን ያሳያል፤ እስከዛሬ በናፍቆት የሚጠብቀውን ወዳጁን ሸፍጥንና የአእምሮ ሕመምን ሲያለብሰው ማንኛቸው መቼ እንደተለወጡ ለመረዳት ያስቸግራል፤ ለማናቸውም የዲክንስን መጽሐፍ ያሬድ እንደሚለው በረከት ከመጀመሪያው ገጽ በላይ አነበበም አላነበበ እንግሊዝኛው ትርጉም መሆኑን የተረዳሁት ከያሬድ ነው፤ ለምን ወደ እንግሊዝኛ እንደተሄደም አልገባኝም፡፡

በዚህ ዓመት ታላላቅ የአገር መሪዎች የሚያስተምሩን ነገር ባይኖራቸውም ‹‹የታሪክ››መጽሐፍት የሚሉትን አሳትመዋል፤ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምና አቶ በረከት ስምዖን፤ ሁለቱ ሰዎች በብዙ ነገር የሚመሳሰሉ ቢመስሉም እውነትን በመናቅና በመጥላት አንድ ናቸው፤ ዛሬ እኔ ላነሣ የፈለግሁት ግን በአስተሳሰብ ግድፈት ላይ የሚያተኩር ነው፡፡
በ1997 የፖለቲካ ክርክር ላይ ከሕገ መንግሥቱ አንቀጾች ሠላሳ በመቶ የሚሆነው ስለሰብዓዊ መብቶች የሚናገር ስለሆነ ይህ ቀረው የሚባል አይደለም፤ ችግሩ በተግባር የምናየው ሕገ አራዊት መሆኑ ነው ብዬ የተናገርሁትን ጉልበተኛው በረከት ወዲያው ቀለብ አድርጎ ‹‹ሕገ መንግሥቱን ሕገ አራዊት ነው አለ፤›› ብሎ ወነጀለኝ፤ ለጉልበተኛው ሕገ ኀልዮትም ሆነ ሕገ መንፈስ ቅዱስ ገንዘቡ አይደሉም፤ ዛሬ ረዳቱ የሆነውም ጠበቃው የገዛ ጆሮውን ከድቶ በጉልበተኛው የተነገረውን እያስፋፋ በፍርድ ቤቱ አስተጋባ፤ ዳኞቹም ጠበቃውን ሰምተው ፈረዱ፤ ዛሬ እነሱ አንገታቸውን አጎንብሰው ይሄዳሉ፡፡
ዛሬም ያው አስተሳሰብ (አስተሳሰብ ካልነው) እንደተለመደው ቃላትን እየዘለዘለ ለውንጀላ ያቀርባል፤ አንዱዓለም አራጌ ‹‹የአምባ ገነን አገዛዝ ባለበት የጀግና ቤቱ እስር ቤት ነው፤›› አለ ይባላል፤ ጉልበተኛው እንደለመደው መጀመሪያ የተባለውን ቀንጭቦ ኪሱ ከተተና (!)አንዱ ዓለም ‹‹የጀግና ቤቱ እስር ቤት ነው›› አለ ብሎ ለውንጀላ ያመቻቸዋል፤ የአንዱ ዓለም መታሰር እሱ ራሱ ያለውን ያረጋግጣል? ወይስ አለ የተባለውን ያረጋግጣል? ወይስ ሁለቱንም ያረጋግጣል? በመሠረቱ አንዱ ዓለም ያለው ሙሉ ቃልና ጎዶሎው ልዩነት የላቸውም፤ የጉልበት አገዛዝ ባለበት የጀግና ቤቱ እስር ቤት ነው፤ የሚለውና ያለመነሻ የጀግና ቤቱ እስር ቤት ነው፤ የሚለው በአንድ ነገር ይመሳሰላሉ፤ ጀግናን የጥቃት ኢላማ በማድረግ ይስማማሉ፤ ከዚያም አልፎ ጀግንነትን መጠቃት አድርገው የሚያቀርቡት ይመሳሰላሉ፤ የተዛባ አስተሳሰብ!
ቀጥዬ የምጠቅሰው ምሳሌ ከላይ ከተጠቀሱት የባሰ የአስተሳሰብ ግድፈትን የሚያመለክት ነው፤ አቶ መለስ ‹‹የተሃድሶ እንቅስቃሴያችንን በከፍተኛ ፍጥነት ከሚወርድና በየደቂቃው ፍጥነት እየጨመረ ከሚጓዝ ናዳ አምልጦ ወደ ጠንካራ ከለላ ለመግባት ከሚሮጥ ሰው ጋር ማመሳሰል ይቻላል፡፡›› ሲል ለስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ባቀረበው ሪፖርት ውስጥ ተናግሮአል፤ በ1997 ምርጫ አቶ መለስ ብዙ አጃቢዎቹ (አቶ በረከትን ጨምሮ) ስለዌደቁበት የናዳውን ኃይል በትክክል ገምቶ የተናገረ ይመስለኛል፤ መለስ የተናገረው ወደበረከት ስምዖን ጆሮ ሲደርስ ግን ሌላ ሆኖ ነበር፤- ናዳን የገታ አገራዊ ሩጫ! መለስ ወደፊት ሂድ! ሲል በረከት ስምዖን ቀኝ-ኋላ ዙር! ይላል፤ ወደፊት አልሮጥም የማለት መብት አለው፤ ጥያቄው ይህ አይደለም፤ የአስተሳሰብ ግድፈቱ ወደፊት ሂድ ማለትና ቀኝ-ኋላ ዙር ማለትን አንድ ማድርጉ ላይ ነው፤ በወያኔ/ኢህአዴግ ዘመን የመጣ የአፈፃፀም ጉድለት የሚባለው ነገር ምንጩ እንዲህ ያለ የግንዛቤ መዛባት መሆኑ ነው፡፡
ለምራቂ አንድ ሌላ ግድፈት ላቅርብ፤ የመጽሐፉ ዋና ርዕስ ‹‹የሁለት ምርጫዎች ወግ›› ነው፤ ምን ማለት ነው? ወግ የሚለው ቃል ሁለት ትርጉም አለው፤ አንዱ ትርጉም ወሬ ነው፤ ሁለተኛው ትርጉም ሥርዓት ማለት ነው፤ ከሃምሳ ዓመታት በፊት በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ላይ በራስ ቢትወደድ እንዳልካቸው የተደረሰ ጨዋታ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ቲያትር ታይቶ ነበር፤ አቶ አሐዱ ሳቡሬ ሲተቹ ድራማ ብለውት ነበር፤ እኔ ግን ጨዋታ ነው ብዬ ‹‹አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም›› ለዚያ ለሞተ ጨዋታ ተስማሚ ስም ነው በማለት ጽፌ ነበር፤ እንዲሁም የሁለት ምርጫዎች ወግ በሁለቱም የወግ ትርጉሞች ተስማሚ ስም የተሰጠው ተረት ነው፤ እውነቱ ጸሐፊው በዚያ ምርጫ መውደቁ ነው፤ እውነቱ ጸሐፊው እንደገና በልዩ ዝግጅት ተመረጠ መባሉ ነው፤ ታሪክን፣ ያውም የቅርብ ታሪክን ወደተረት ለመለወጥ ለጉልበተኛም ቢሆን አስቸጋሪ ነው፤ ተዋንያኑ ሁሉ ገና በሕይወት አሉ፤ ጸሐፊው ልማድ ሆኖበት አላነበባቸውም እንጂ አንዳንዶቹም ስለምርጫው ከወግ ባለፈ ጽፈዋል፡፡
ስለ2002 ምርጫ በቅርቡ እንኳን በአሐዝ የተደገፈ ጥናት ወጥቷል፤ አንደኛ ከአጠቃላይ የየክልሉ ሕዝብ ቁጥር ውስጥ የመረጡትን ስናይ ምርጫው ወግ ብቻ እንደነበረ ገሀድ ይሆናል፤ ለምሳሌ ከየክልሉ የመረጡት በኦሮሚያ 31 ከመቶ፣ በአማራ 33 ከመቶ፣ በደቡብ 27 ከመቶ፣ በትግራይ 39 ከመቶ፣ በአዲስ አበባ 19 ከመቶ፣በአፋር 66 በመቶ፣ ከዚያ ደግሞ በድሬደዋ 57 ከመቶ ሲሆኑ በሐረርና በኦጋዴን ደግሞ ለወግም የማይመች በመሆኑ አልተገለጸም፤ ናዳው የምርጫውን ወግ እንኳን እንደደፈጠጠ በተለይ የአፋርና የድሬዳዋ የመራጮች አሐዝ ምስክር
ነው፤ እድሜያቸው የማይፈቅድላቸው ሁሉ ካልመረጡ በቀር፤ ወይም በእነዚህ ክልሎች አብዛኛው ሕዝብ በልዩ ተአምር እድሜው ከ18 ዓመት በላይ ካልሆነ በቀር ከላይ የተገለጸውን ያህል መራጭ ሊያገኙ አይችሉም፤ እንዲሁም በመረጡት ወንዶችና ሴቶች መሀከል በየክልሉ የሚታየው ድርሻ ወንድና ሴቱ እኩል እንዲሆን ተደርጎ የተደለደለ መሆኑ ይታያል፤ ይህንን ሁሉ የዘነጋ ከታሪክ ይልቅ ወደተረት ያዘነበለ ጨዋታ ነው፤ ተረቱ የሚጣፍጠው ከተገኘ!
ሁለተኛ አቶ ኡስማን አሊ የሚባል ሰው 368,211 ድምጽ፣ አቶ ሽመልስ ከማል ብርሃን የሚባል ደግሞ 19,647 ድምጽ ለወጉ አግኝተው ተመርጠዋል፤ ከተመራጮቹ 64 በመቶ ያህሉ ያገኙት ድምጽ ከ50,000 በታች ነው፤ መለስ ዜናዊ ያገኘው 40,302 ነው፤ በትግራይ ወይዘሮ አልማዝ የሚባሉ 87,185 ድምጽ ማግኘታቸው ቱባ ቱባ ባለስልጣኖቹ ካገኙት ጋር ሲወዳደር ሰማይ ያደርሳቸዋል ስለ2002 ምርጫ በአገቱኒ ውስጥ ዝርዝር መረጃ ቀርቦአል፡፡
መጽሐፍ ያውም የታሪክ መጽሐፍ ለመጻፍ ለእውነት ክብር መስጠትና ለእውነት ተገዢ መሆን ያስፈልጋል፤ አለዚያ ጉልበትና የአቶ አላሙዲንን ገንዘብ ማጥፋት ነው፡፡

No comments:

Post a Comment