Translate

Wednesday, September 4, 2013

ወያኔ የሚገነፍል ድስት ነዉ

ኤፍሬም ማዴቦ

Ephremስፖርት በጣም እወዳለሁ፤ ወቅታዊ ዜናና ጥናታዊ ፊልምም አዘወትራለሁ። ከሁለቱ ዉጭ ግን ኢትዮጵያ እያለሁም ሆነ ዛሬ በስደት ኑሮዬ ከቴሌቪዥን ጋር ብዙም አልዋደድም . . .  ግን አንዳንዴ እበድ ሲለኝ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንም ቴሌቪዥን ሆኖ ከመተኛቴ በፊት ኢቲቪ እየከፈትኩ አብዳለሁ።  አዎ . . . አብዳለሁ። ሆዴ ያመቀዉ ቁጣና ልቤ የተሸከመዉ የ22 አመት በደል ቀለል የሚለኝ ሳብድ ነዉና ኢቲቪ እየከፈትኩ አብዳለሁ። ምን ላድርግ ተሰድጄ ልበድ እንጂ በወያኔዋ ኢትዮጵያማ እነ በረከት ካልፈቀዱ ማበድም አይቻልምኮ!   አደራ እንግዲህ እንደኔ ጠንካራ ቆዳ የሌላችሁና በትንሹም በትልቁም እየተበሳጫችሁ ዕቃ የምትወረዉሩ ሰዎች ኢቲቪን ከመክፈታችሁ በፊት ባንካችሁ ዉስጥ ቴሌቪዥን መግዢያ ትርፍ ገንዘብ መኖሩን አረጋግጡ፤ አለዚያ እዉነትም ማበዳችሁ ነዉ።

ባለፉት ሃያ ሁለት አመታት የወያኔን ፀባይ በተከታታይ እንዳየሁት የወያኔ ፀባይ ከበቅሎ፤ ከድስት ወይም ከሁለቱም ጋር ተመሳስሎብኛል። በቅሎ የታሰረችበትን ገመድ በጠሰች ቢሉት “በራሷ አሳጠረች” ብሎ መለስ አሉ የበቅሎዋ ጌታ። በቅሎ መታሰሪያዋን በበጠሰች ቁጥር የምትጎዳዉ እራሷን ነዉ፤ ግን በቅሎ በጭራሽ ከስህተቷ አትማርምና ሁሌም ገመዷን እንደበጠሰች ነዉ። አምባገነኑ ወያኔም እንደዚሁ ነዉ።  ድስት ሁሉም ባይሆንም አንዳንዱ በጣዱት ቁጥር ይገነፍላል፤ የሚገነፍል ድስት ደግሞ የሚያበላሸዉ እራሱን ነዉ። ወያኔ ድስትም በቅሎም የሚሆነዉ ዕድሜዉን ለማራዘም ነዉ፤ ሆኖም ሲገነፍልም ሆነ ገመዱን ሲበጥስ እድሜዉ ያጥራል እንጂ አይረዝምም።
ከሰሞኑ ኢትዮጵያ ዉስጥ የሐይማኖቶች ጉባኤ ይካሄዳል ሲባል ሰምቼ ባለፉት ሁለት አመታት ካልጠፋ ነገር አገራችን የምትታመሰዉ በሐይማኖት ጉዳዮች ነዉና እስኪ ዜናዉን ከምንጩ ልስማ ብዬ ኢቲቪ ላይ አፈጠጥኩ። መቼም ኢቲቪ በብዙ ነገሮች ሊያበሳጫችሁ ይችላል ግን  ዛቻ፤ ዉሸትና፤ ዘራፊ ባለስልጣኖች ሲሞገሱ መስማት ከፈለጋችሁ ግን ሌላ ዬትም ቦታ መሄድ አያስፈልጋችሁም በዚህ ኢቲቪ የልባችሁን ያደርስላችኋል።
ወያኔ ስልጣን ይዞ በቆየባቸዉ አመታት ሁሉ ዛሬም ድረስ ኢትዮጵያ ጨንቋት ያላማጠችበትና ግራ ግብቷት ድረሱልኝ ያላለችበት አንድም ግዜ የለም። ወያኔ ባለፉት ሃያ አመታት ዉስጥ አገራችን ኢትዮጵያን እንዳልነበረች ለማድረግ ያልቆፈረዉ ጉድጓድና ያልሸረበዉ ደባ ባይኖርም ባለፉት ሁለት አመታት ይዞብን የመጣዉ ሸርና ተንኮል ግን የክርስቲያኑንና የሙስሊሙን ማህብረሰብ የአንድ ሺ አራት መቶ አመታት በሰላም አብሮ የመኖር ባህል የሚያደፈርስና አገራችንን አስከፊ የሐይማኖቶች ግጭት ዉስጥ የሚከት አደገኛ ሴራ ነዉ። ለወትሮዉ ፖለቲካዉን በዘር፤በቋንቋና በክልል ቋጥሮ ማዶ ለማዶ የለያየን ወያኔ ዘንድሮማ ጭራሽ የፓርቲ አባልነታችንን ብቻ ሳይሆን የምናመልክበትን የእምነት ቦታና አለም በቃኝ ብለን የምንመንንበትን ገዳም ጭምር አኔ ነኝ መርጬ የማድላችሁ ማለት ጀምሯል። በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ላይ ጳጳስ አዉርዶ ጳጳስ ሾሞባቸዋል፤ የወንጌላዉያን ቤ/ክርሲቲያኖችን ፓስተር አንዴ አስታራቂ አንዴ አማላጅ እያደረገ ቤ/መንግሰትና ቃሊቲ መሃል ተላላኪ አድርጎታል፤አሁን በቅርቡ ደግሞ ፊቱን ወደ ሙስሊሙ ማህበረሰብ በማዞር የራሱን መጅሊስ ሾሞባቸዋል።
ወያኔ ጥንታዊቷን የኦርቶዶክስ ቤ/ክርሰቲያናችንን የአገር ዉስጥና የአገር ዉጭ ሲኖዶስ በሚል በመከፋፈል ወንጌላዉያኑን አብያተ ክርስቲያናት ደግሞ እኔ ነኝ የማምለክ ነጻነት የሰጠኋችሁ እያለ በማስፈራራት የክርስቲያኑን ህብረተሰብ ለግዜዉም ቢሆን ጭጭ አሰኝቶ እንዳሰኘዉ መቆጣጠር ችሏል። በድርጅታዊ ጥንካሬዉ፤ በምዕመኑ መካከል በገነባቸዉ የግንኙነት መስመሮችና  በእምነት ቀናኢነቱ ከክርስቲያኑ እጅግ በጣም በተሻለ ደረጃ ላይ የሚገኘዉ የሙስሊሙ ህብረተሰብ ግን  የወያኔን ፈላጭ ቆራጭነት አልቀበልም ብሎ ወያኔንና ዘረኝነቱን ፊለፊት በመጋፈጥ ላይ ይገኛል። ሰለሆነም ዛሬ አገራችን ኢትዮጵያ  ሐይማኖቴን አትንካብኝ በሚለዉ በሙስሊሙ ህብረተሰብና አጎንብሰህ ተገዛ በሚለዉ ወያኔ መካከል በተፈጠረዉ የፖለቲካ አለመረጋጋት በመታመስ ላይ ትገኛለች። እኔም ሞኝ ይመስል ኢቲቪ ላይ ያፈጠጥኩት ይካሄዳል የተባለዉ የሐይማኖት ጉባኤ ይህንን አገራችን ላይ የተደቀነዉን አደጋ ተመልክቶ የመፍትሄ ሃሳብ ያቀርባል ብዬ ነበር። ግን የወያኔ ነገር ሁሌም ታጥቦ ጭቃ ነዉና የሐይማኖት ጉባኤ ተብሎ የቀረበዉ ጉድ እንደ አኬልዳማና ጂሃዳዊ ሐረካት ሆን ተብሎ  ህዝብን ለማደናገር የተሰራ ድራማ ነዉ እንጂ በችግሮች ላይ ተወያይቶ የመፍትሄ ሃሳብ የሚያቀርብ ጉባኤ አይደለም። በአኬልዳማ ድራማና ሰሞኑን በተካሄደዉ የሐይማኖቶች ጉባኤ መካከል ልዩነት ቢኖር አንዱ የቴሌቪዥን ድራማ ሌላዉ ደግሞ የመድረክ ላይ ድራማ መሆናቸዉ ብቻ ነዉ።
በዚህ የሐይማኖቶች ጉባኤ ተብዬዉ የአዳራሽ ውስጥ ድራማ ላይ የተገኙት አብዛኛዎቹ ተዋንያን የዚያ “የድንጋይ ማምረቻ” ተቋም ዉጤቶች የሆኑ የወያኔ ካድሬዎች፤ የወያኔ ባለስልጣኖችና ኤሳዉ ታላቅነቱን ለምግብ እንደሸጠ የሐይማኖት አባትነታቸዉን ለጥቅም የሸጡ ካህናት ለመሆናቸዉ ምስክር የሚያሻ አይመስለኝም፤ ቴሌቪዥኑ መስኮት ዉስጥ አንደተከበበ አዉሬ የሚቁለጨለጨዉ አይናቸዉ ምስክር ነዉ።  ድራማዉን በኢቲቪ ስመለከት ተጠያቂነት የሚባል ነገር የማያዉቁ የወያኔ ባለስልጣኖች እንዳሰኛቸዉ እንደሚናገሩ ስለማዉቅ እነሱ ተናገሩም አልተናሩ ከነሱ ብዙም የምጠብቀዉ ነገር አልነበርም። ይልቁን ጉባኤዉን ስከታተል እጅግ በጣም የገረመኝና የራሴኑ ጆሮ ማመን ያቃተኝ አንድ በሰማይም በምድርም ተጠያቂነት ያለባቸዉ የሐይማኖት አባትና በዋሸ ቁጥር ኩራት የሚሰማዉ በረከት ስምኦን ያደረጉት እንደ ብርሀንና ጨለማ የተቃረነ ንግግር ነዉ። መቼም እርግጠኛ ነኝ የበረከትንና የአባዉን   ፊት ሳያይ ንግግራቸዉን ብቻ ያዳመጠ ሰዉ የቱ ነዉ በረከት የትኛዉ ናቸዉ የሀይማኖት አበት ብሎ መጠየቁ አይቀርም። ለሁሉም እኚያ የሐይማኖት አባትና በረከት እንዲህ ነበር ያሉት
የሐይማኖት አባት                        መንግስት ትዕግስቱን አብዝቶታል  . . . . እርምጃ ይዉስድ
በረከት ስምኦን                መንግስት ኃይሉ አለዉ ግን መታገሱ ጠቃሚ ነዉ
መቼም አንደህ አይነቱን ጉድ ከጉድም ጉድ የሚያዳምጡ ሰዎች ጆሯቸዉን ሲያማቸዉ፤ ሲበሳጩና አንጀታቸዉ ሲቃጠል ይታየኛል . . ደግሞስ ለምን አይበሳጩ ለምንስ አንጀታቸዉ አይረር?  ትዕግስት ምን አንደሆነች የማያዉቃት ወያኔ ለዛዉም በበረከት ስምኦን አፍ መታገሱ ጠቃሚ ነዉ ነዉ ብሎ ሲናገር የትዕግስት አባት የሆነዉን እግዚአብሄርን አገለግላለሁ ባዩ ቄስ “ትዕግስት በዛ እርምጃ ይወሰድ” ብለዉ መንግስትን የሚማጸኑበት ግዜ መጣ . . . ያዉም ስራዉ ዜጎችን መግደል የሆነዉን መንግስት!  እግዚኦ!  ለመሆኑ አንደ አገርና እንደ ህዝብ ስነምግባራችንና ሀይማኖታዊ እሴታችን እንደዚህ የዘቀጠበት ግዜ ኖሮን ያዉቃል? የወደፊቱን አገር ተረካቢ ትዉልድ በስነምግብርና በግብረገብ አንጾ የማሳደግ ኃላፊነት ያለባቸዉ የሐይማኖት አባት መንግስትን አሁንስ አበዛኸዉ ሂድና ግደል እንጂ የሚሉ ከሆነ ይህ እዉነት ሳይሰማ ያደገ ትዉልድ ስራዉ መግደል ብቻ ሊሆን ነዉኮ . . .   አረ እግዚኦ ማረን!  እባክህ ማረን!
ልጅ እያለሁ አንድ በኃይሉ እሼቴ የሚባል “መሆኑ ይገርማል የተገላበጦሽ አህያ ወደሊጥ ዉሻ ወደ ግጦሽ” ብሎ የዘፈነ አለግዜዉ የተፈጠረ ዘፋኝ ነበር  . . ያኔ የማይመስል አባባል ይመስለኝ ነበር፤  ይሄዉና ዘመን ቆጥሮ ደረሰ። በረከት ስምኦንን በተመለከተ ያንን ንግግር ከልቡ ይናገረዉ ወይ ለማሽሟጠጥ አላዉቅም ሆኖም በረከት ያዉ በረከት ነዉና ስለሱ ምንም የምለዉ የለኝም። እኚያ የሐይማኖት አባት ግን ይህንን አሳፋሪ ንግግር የተናገሩት ሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስ ያንን ለትዉልድ ሁሉ ኩራት የሆነዉን ታሪካዊ ንግግር በተናገሩበት ከተማ ዉስጥ ነዉና አሳቸዉ ያለ እፍረት አፋቸዉን እንደከፈቱ እኔም በድፍረት አፌን አከፍትባቸዋለሁ . . . ምን ላድርግ 1ኛ ሳሙኤል 2፡1 ላይ  “አፌ በጠላቶቼ ላይ ተከፈተ” ይላልኮ አባ እራሳቸዉ ያስተማሩኝ ቅዱስ መጽሐፍ።  ለሁሉም “እናቷን ምጥ አስተማረች” እንዳይሆንብኝ እንጂ  እኚያ ወያኔን “ምነዉ መንግስት ትዕግስት አበዛ” ብለዉ ያወገዙት አባት ተሸክመዉ የሚዞሩትን መ/ቅዱስ አንብበዉት ከሆነ እዚያ ቅዱስ መጽሐፍ ዉስጥ ትዕግስት የሚለዉ ቃል 33 ግዜ ተጠቅሷል። “አትግደል” የሚለዉ ትዕዛዝ ደግሞ ከአስርቱ ትዕዛዛት አንዱ ሲሆን ቅዱስ ታቦቱ ላይም የሰፈረ ቃል ነዉ። መጽሐፍ ቅዱስ ትዕግስትን አስመልክቶ  መጽሐፈ ምሳሌ ምዕራፍ 25፤15 ላይ “በትዕግስት ማግባባት ታላቅ ተቃወሞን ያበርዳል፤መሪዎችን ሳይቀር በሃሳብ እንዲስማሙ ያደርጋል” ይላልኮ! ለመሆኑ ትዕግስቱን ተትህ ግደል እንጂ ብለዉ ወያኔን የተማፀኑት የሐይማኖት አባት የኦርቶዶክስ አባ ናቸዉ፤ የካቶሊክ ካርዲናል፤ የፕሮቴስታንት ፓስተር ወይስ በሐይማኖት ስም የመጡ የወያኔ ካድሬ? ማናቸዉ እኚህ ታገሱ ፤ ትዕግስትን ገንዘባችሁ አድርጉ፤“መግደል” ኃጢያት ነዉና ሰዉ አትግደሉ ብለዉ ማስተማር ሲገባቸዉ የተገላቢጦሽ “ግደል” እያሉ የሚማጸኑ የሐይማኖት ሰዉ?
ኢትዮጵያዉያን የእስልምና እምነት ተከታዮች ያነሱትን የመብትና የነጻነት ጥያቄ በተመለከተ ፖለቲካና ሐይማኖት፤ካድሬነትና ቅስና ተቀላቅሎባቸዉ ግራ ተጋብተዉ ህዝብን ግራ ከሚያጋቡ ሰዎች አንዱ ጠ/ሚ ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ነዉ። ኃ/ማሪያም ደሳለኝ እንደ መለስ ዜናዊ ምላስ እንቆርጣለን ብሎ እንዳይዝት እንኳን ምላስ ለመቁረጥ ቤ/መንግስት ከመግባቱ በፊት በነጻነት ያመልከዉ የነበረዉን አምላኩን ለማምለክም የወያኔ ፈቃድ ያስፈልገዋል። ደሞ ምንም ቢሆን ሰዉዬዉ የአገር መሪ ነዉና ችግሮችን እፈታለሁ በሚል ሚዛናዊ እርምጃ ልዉስድ ቢል እሱ እራሱ በስልክ እየታዘዘ የሚሰራ ሰዉ ነዉ። መቼም በወያኔዋ ኢትዮጵያ እንዲህ አይነቱ ነገር አይታሰብም እንጂ ኃ/ማሪያም ዳሳለኝ የሙስሊሙ ህብረተሰብ ያነሳዉን ጥያቄ ከሐይማኖት፤ከባህልና ከስነምግባር አንጻር አይቶ ትክክለኛ ጥያቄ ነዉ ብሎ ጥያቄዉን ለመመለስ ቢሞክር እንኳን ብዙም ሳይቆይ “እንደወጣች ቀረች” ተብሎ ይተረትበታል አንጂ ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ህዝባዊ ጥያቄዎችን መመለስ ቀርቶ እሱ እራሱ ያሻዉን ጥያቄ መጠየቅም አይችልም ። እንግዲህ ይህ እራሱን መሆን የተሳነዉና ሦስት ቅርቃሮች ዉስጥ ገብቶ የተቀረቀረዉ ኃ/ማሪያም ነዉ አንዴ ተጨማሪ የኃይል እርምጃ እንወስዳለን፤ አንዴ የሙስሊሙ ጥያቄ የሸሪአ ጥያቄ ነዉ፤ ይባስ ሲለዉ ደግሞ ከሙስሊሙ ትግል ጋር የተባበረ ሁሉ ሽብርተኛ ነዉ እያለ ያልተጻፈ መጽሐፍ የሚያነብበዉ። ለመሆኑ ይህ ጧትና ማታ የጓድ መለስን ራዕይ ተግባራዊ እናደርገለን እያለ የሚዘምረዉ ኃ/ማሪያም  “ተጨማሪ የኃይል እርምጃ እንወስዳለን” ሲል የጌታዉን ራዕይ ተግባራዊ ማድረጉ ይሆን?
ባለፉት ሦስት ሳምንታት በተለይ ባለፈዉ ቅዳሜ በወያኔ ጌቶቹ እየተመራ ኃ/ማሪያም ደሳለኝ የወሰዳቸዉ ፀረ ህዝብና ፀረ አገር እርምጃዎች ለኢትዮጵያ ህዝብም ሆነ ኢትዮጵያ ዉስጥ በመካሄድ ላይ ያለዉን ህዝባዊ እንቅስቃሴ ለሚከታተሉ አገሮች ያረጋገጠዉ ነገር ቢኖር የኢትዮጵያ ህዝብ የወያኔን ዘረኛ ስርዐት ለማስወገድ የሚከተለዉን እስትራቴጂ በጥልቀትና በስፋት መመርመር እንዳለበት ነዉ። እስካዛሬ እንዳየነዉ ወያኔ በልመናም፤ በሰላማዊ ትግልም፤ በአመጽም ሆነ በሌላ በምንም አይነት መንገድ እንድንታገለዉ የማይፈልግና እኔ ብቻ ዝንተ አለም እንደገዛኋችሁ ልኑር የሚል ልቡ ያበጠ አምባገነን ነዉ። ህዝባዊ ተሳትፎን በተመለከተ የወያኔ ፍላጎት አንድ ብቻ ነዉ፤ እሱም በዚያ እሱ እንደ ቤቱ ጓዳ በሚቆጣጠረዉና በየአምስት አመቱ በሚደረገዉ ምርጫ እንድናጅበዉ ብቻ ነዉ። ከዚህ ዉጭ ዲሞክራሲና መብት የሚባል ቃል ስሙን ያነሳ ሰዉ ወይ ይታሰራል፤ ይደበደባል፤ከአገር ይሰደዳል አለዚያም ይገደላል። የወያኔና የእኛ ሠላማዊ ትግል በይዘትም በቅርጽም እጅግ በጣም የሚለያይ ይመስለኛል። የወያኔ ሠላማዊ ትግል እኔን ብቻ ስሙኝ ወይም በየአምስት አመቱ በምርጫ አጅቡኝ ነዉ። እኛ ሠላማዊ ትግል የምንለዉ ደግሞ መብታችን ይከበር ብለን ባሰኘን ግዜና ቦታ የተቃዉሞ ሠልፍ ማድረግ፤ የስራ ማቆም አድማ ማድረግና ወያኔ ህገመንግስቱን የሚጻረር መመሪያና ህግ ሲያወጣ በፍጹም አንቀበልም ብለን በህዝባዊ እምቢተኝነት ማመጽ ነዉ። ይህንን አድርገን ቢሆን ኖሮ ዛሬ እስክንድርን፤ አንዱአለምን፤ ርዕዮትንና ሌሎች በሺዎች የሚቆጠሩ ሠላማዊ ዜጎችን ቃሊቲ የወረወረዉ ህግ አይኖርም ነበር። ሠላማዊ ትግል የሚባለዉ እንደዚህ አይነቱ ትግል ነዉና ወያኔን ማፋጠጥ ያለብን በዚህ አይነቱ ትግል ነዉ፤ ካለዚያ የትግላችንን እስትራቴጅ ፈትሸን ለግዜዉ የወያኔን ጥቃት ባይመጥንም ወያኔ ጥቃት ከመሰንዘሩ በፊት ሁለቴ እንዲያስብ የሚያደርግ የትግል እስትራቴጅ መንደፍ አለብን። ከዚህ በተጨማሪ ወያኔን በመሳሪያ ለመፋለም የቆረጡ ኃይሎችን ቢቻል መደገፍ አለዚያም ጣታችንን እነሱ ላይ መጠንቆሉን ማቆም አለብን።
ከሰዐት በኋላ ረፋዱ ላይ ከስራ ወጥቼ ቴሌቪዥኑ ፊት ስደቀን የአገሬ የኢትዮጵያ ነገር አይኔ ላይ ይመጣና አንዳንዴ ግርም ይለኛል፤ አንዳንዴ ይጨንቀኛል፤ አንዳንዴም ይነድደኛል። የከሰሞኑ ግን አታምጣ ነዉ።  አግራሞቱም፤ ጭንቀቱም፤ ንዴቱም እንደ ክፉ መንፈስ በአንዴ ተከመሩብኝ። መቼም የኢትዮጵያ ነገር የማይገርመዉ ኢትዮጵያዊም ሆነ የዉጭ አገር ሰዉ ያለ አይመስለኝም፤ ደግሞስ የኢትዮጵያ ነገር ለምን አይገርምም?  መንግስት ተብዬዉና አገር እመራለሁ ባዩ ወያኔ የምትወደዉ እንድዬ ልጇ እንደሞተባት አሮጊት አመት ጠብቆ ተዝካር ሲያወጣ . . . .  ጎበዝ ለመሆኑ ተዝካር የሚያወጣ መንግስት አይታችሁ ወይም ሰምታችሁ ታዉቃላችሁ? አኔ እንኳን መስማት አስቤዉም አላዉቅም። የሚገርመዉ ወያኔ ያንን የፈረደበትንና የዛሬ አመት እያስፈራራ በጉልበት ያስለቀሰዉን ህዝብ ብቻ ሰብስቦ የጌታዬን ተዝካር አዉጡልኝ ቢል ኖሮ ነገሩ እኛዉ በእኛ ነዉና ስቀን ዝም እንል ነበር፤ ግን ጉደኛዉ ወያኔ ተዝካር ድረሱልኝ ብሎ የጠራዉኮ የጎረቤት አገር መሪዎችን ጭምር ነዉ። የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ ነኝና ተዝካር ለሟቹም ለቋሚዉም አይጠቅምም ብዬ አምናለሁ፤ ሆኖም ተዝካር ትክክለኛ ነገር ነዉና መዘከር አለበት የሚሉ ወገኖች ተዝካር የማዉጣት መብታቸዉ እንዲከበር ሽንጤን ገትሬ የምታገል ሰዉ ነኝ። ግን የኢትዮጵያ መንግስት ሲባል የኦርቶዶክሱ፤ የሙስሊሙ፤ የጴንጤዉ፤ የካቶሊኩና የሌሎቹም የዬትኛዉም አይነት እምነት ተከታዮችና ስለሐይማኖት ግድ የሌላቸዉም ሰዎች መንግስት ስለሆነ ተዝካር ማዉጣጥ ቀርቶ ስለተዝካር መልካምነትም ሆነ መጥፎነት መናገርም የለበትም የሚል የፀና እምነት አለኝ። በረከት ስምኦንና ሽመልስ ከማል አይገባቸዉም አንጂ የሚገባቸዉ ቢሆን ኖሮ ሐይማኖትና መንግስት ተቀላቀሉ የሚባለዉ እንደዚህ መንግስት በአገር አቀፍ ደረጃ ተዝካር ሲያወጣ ነዉ አንጂ ሐይማኖትና ፖለቲካ ሲነካኩ አይደለም፤ እነሱማ መነካካት አለባቸዉ፤ የአገሪቱ ህገመንግስትም ይህንን አይከለክልም።
ሌላዉ ከሰሞኑ ያየሁት የወያኔ ጉድ  . . . ማንን እንደሚቃወም ባላዉቅም ወያኔ ሠላማዊ ሠልፍ የሚወጣ ብቸኛዉ የአለማችን መንግስት  ነዉ። ወገኖቼ ይህ ጉድ ካልገረመን፤ ካልጨነቀንና ካልነደደን ሌላ ምን. . . ምን . . . .  ምን! ደግሞኮ የ39 አመቱ ጎልማሳ ወያኔ ሠላማዊ ሠልፍ የጠራዉ ገና በእግሩ መሄድ ካልጀመረዉ ከሠማያዊ ፓርቲ ገር ሽሚያ ገብቶ ነዉ። ኢትዮጵያ ዉስጥ መንግስት በአስቸኳይ ግዜ አዋጅ ለአገሪቱ ደህንነት ሲባል ካላገደ በቀር ሠላማዊ ሠልፍ ማድረግ ህገመንግስታዊ መብት ነዉ፤ወይም  ዜጎች ሠላማዊ ሠልፍ ለመዉጣት ማሳወቅ እንጂ ፈቃድ መጠየቅ አያሻቸዉም። ወያኔ ሠማያዊ ፓርቲ የጠራዉን ሠልፍ ለጸጥታ ወይም ለሌላም ጉዳይ ብሎ እንዳይካሄድ ቢፈልግ ኖሮ ብቸኛዉ አማራጭ ወይ ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር መደራደር አለዚያም ፍርድ ቤቶች የራሱ ንበረቶች ቢሆኑም ለይስሙላም ቢሆን እዚያ መሄድና ፍርድ ቤቱን ማሳመን ነበረበት እንጂ ልቡ እንዳበጠ የመንደር ዉስጥ ወጠጤ በተራ ዝርፊያና ድብደባ ላይ አይሰማራም። መንግስት ማለት ያሰኘዉን ነገር ሁሉ የሚያደርግ ተቋም አለመሆኑን ወያኔም ሆነ ወያኔ በተተቸ ቁጥር ምጣድ ላይ እንደቆየ ተልባ የሚንጣጡት ደጋፊዎቹ ሊረዱት ይገባል።
ባለፈዉ ቅዳሜ ወያኔ ከሠማያዊ ፓርቲ ጋር ሠልፍ ልዉጣ አትወጣም በሚል በገባዉ እሰጥ አገባ በህግም በሃሳብም በሠማያዊ ፓርቲ በመሸነፉ የተሸናፊዎች ብቸኛ መሳሪያ የሆነዉን ጉልበትና በህግ ያልተገደበ ኃይል በመጠቀም የሠማያዊ ፓርቲ መሪዎችን በቆመጥና በሰደፍ ሲደበድብ ዉሏል፤ የፓርቲዉን ጽ/ቤት ሰብሮ በመግባት ንብረት ሰርቋል እንዱሁም ፓርቲዉ በህጋዊ መንገድ የተከራየዉን ጽ/ቤት ከብቦ አካባቢዉን የጦርነት ወረዳ አስመስሎታል። መስበር፤ መዝረፍ፤ ሠላማዊ ዜጎችን መደብደብና የአካባቢን ጸጥታ መንሳት . . . . ለመሆኑ ማነዉ ሽብርተኛዉ?  አገራችን ኢትዮጵያን ጨምሮ አለማችን ብዙ አምባገነን መሪዎችን አስተናግዳለች፤ እንደ ወያኔ አይነቱ ተራ ዱሪዬና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ንፍጣቸዉን የተናፈጡበትን መሀረብ ጭምር የሚሰርቅ ተራ ሌባ የሆነ ስርዐት ግን ዬትም አገር ዉስጥ ታይቶ አይታወቅም። ይህ ስርዐተ አልበኛ የሆነ የወንበዴ አገዛዝ ከአሁን በኋላ የሚወስደዉ እርምጃ ለሁላችንም ግልጽ የሆነ ይመስለኛል፤ ትናንት በአንዱ አለም አራጌ፤ በእስክንድር ነጋ፤ በበቀለ ገርባና ኦብላና ሌሊሳ ላይ የተመሰረተዉ የግፍ ከስ ዛሬ በሠላማዊ ፓርቲ መሪዎች ላይ መመስረቱ አይቀርም፤ የሚያሳዝነዉ በሠማያዊ ፓርቲ መሪዎች ላይ መረጃ ሆነዉ የሚቀርቡት እነዚሁ ባለፈዉ ቅዳሜ ከፓርቲዉ ጽ/ቤት የተዘረፉት የፓርቲዉ ህጋዊ ሰነዶች ናቸዉ። እንገዲህ ያታያችሁ . . .  ከሳሾቹ ሌቦች፤ ዳኞቹ ሌቦች ምስክሮቹ ሌቦች፤ ማስረጃዉም በሌብነት የተሰበሰበ ማስረጃ ነዉ . . .  “እዛዉ ሞላ እዛዉ ፈላ”  . . .  እንደዚህ ነዉ የወያኔ ነገር … ሁሉም ነገር በሌብነት!
ባለፈዉ ቅዳሜ ወያኔ ከብዕርና ከመጽሐፍ ዉጭ እጃቸዉ ሌላ ምንም ነገር ጨብጦ የማያዉቀዉን ነፃነትና ፍትህ ናፋቂ ወጣቶች ወራሪ ጠላትን ለማጥቃት በሰለጠኑ የልዩ ኮማንዶ ኃይሎች ሲደብድብ ዉሏል። ሴቶች እህቶቻችንን ባዕዳን አረቦች ከሚያድርሱባቸዉ የአካልና የሂሊና ጉዳት እጅግ በጣም በከፋ መልኩ ተድብድበዋል፤ ክብራቸዉንና ሰብእናቸዉን በሚያንቋሽሽ ስድብ ተሰድበዋል። ከሁሉም የሚያሳዝነዉ ወጣት ሴቶቻችን ልብሳቸዉን እንዲያወልቁ ተደርገዉ በዉስጥ ሱሪያቸዉ ብቻ ጭቃ ዉስጥ እንዲንከባሉ ተደርገዋል። በቀጥታ ከዲስ አበባ በደረሰኝ መረጃ መሠረት የወያኔ ደነዝ አግአዚ ቅልቦች በ1997ቱ ምርጫ ማግስት በግልጽ የነገሩንን ቃል አሁንም በማያሻማ መልኩ አስረዉ እየደበደቡ በሚያሰቃዩዋቸዉ የሠማያዊ ፓርቲ አባላት ፊት አንደዚህ ሲሉ ደግመዉታል -
እንገዛችኋለን . . .  መግዛት ብቻ ሳይሆን እንረግጣችኋለን!! ደማችንን አፍስሰንና አጥንታችንን ከስክሰን የያዝነዉን ስልጣን አሁንም እንሞትለታለን እንጂ በፍጹም አንለቅም። በሠላማዊ ትግል ስልጣን መያዝ ቀርቶ ከዛሬ በኋላ እኛ ሳንፈቅድላችሁ ከቤታችሁም አትወጡም። ስለህግ አታዉሩ ህግ ማለት እኛ ነን።
ዉድ ኢትዮጵያዉያን ለወያኔ ጅላጅሎችና ጋጠወጦች የማንገዛና የማንረገጥ መሆናችንን ብቻ ሳይሆን ታቦት ተሸክመዉ እባካችሁ ማሩን ብለዉ እስኪለምኑን ድረስ መርገጥ ማለት ምን ማለት መሆኑን ማሳየት የምንችል መሆናችንን በተግባር ማሳየት አለብን። ለአገራቸን ግድ ከሌላቸዉ፤ ታሪካችንን ከናቁና ለሰብዕናችንና በተለይም ለሴት እህቶቻችን ክብር ከሌላቸዉ እኛስ እነዚህን አዉሬዎች ለምን መታገስ አለብን፤ ለምን መሸከም አለብን ለምንስ እነሱ አድርጉ የሚሉንን ማድረግ አለብን? የታለ ያ ባርነትን የሚጸየፈዉ ኢትዮጵያዊታችን? የታለ ያ ጥቃትን በፍጹም የማይቀበለዉ ኢትዮጵያዊ ወኔያችን? የታለ ያ “እታለም” ስትደፈር ዱር ቤቴ ብሎ የሚሰደደዉ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን? የታለ ያ በ1970ዎቹ የትግል ጓዱ በደርግ ባንዳዎች እጅ እንዳይወድቅ ሲል ብቻ ፖታሲየም ሳይናይድ እየቃመ የሞትን ፅዋ የጨለጠዉ ኢትዮጵያዊ ጅግንነታችን. . .  የታለ?  . . .የታለ? . . .የታለ?  የወያኔ ዘረኞች ረግጠዉ ሊገዙን ሞተዋል፤ ዛሬም ይህ ረጋጭ ስርአታቸዉ እንዲቀጥል ለመሞት ቆርጠዋል? እኛስ ምነዉ ላለመረገጥ፤ ላለመገዛትና እህቶቻችንና ወንድሞቻችን በዘረኞች እንዳይገደሉ ስንል የማንሞተዉ ለምንድነዉ? ጎበዝ እኔ አልሞትም ብንልም በቁማችን ሞተናልኮ፤ አንዱኑ በክብር እንሙትና ለወገኖቻችንና ለአገራችን ቤዛ እንሁን አንጂ!
የኢትዮጵያ ህዝብ ህግ አክባሪ ህዝብ ነዉ፤ ሆኖም ወያኔ የራሱን ህገመንግስት ጥሶ በህግ ያልተገደበ ኃይል ሲጠቀም ወይም ህጉን የጻፈዉ አካል እራሱ ያላከበረዉን ህግ ማክበር ሞኝነትና እራስን ለጥቃት ማጋላጥ እንጂ ህግ አክባሪነት አይደለም። እኛ ኢትዮጵያዉያን ከበስተጀርባዉ የማስፈጸሚያ ኃይል የሌለዉ ህግ እንደማይጠቅመን ሁሉ ህግ የማይገዛዉ ልቅ የሆነ ኃይልም ይጎዳናል እንጂ በፍጹም አይጠቅመንም። ስለዚህ እንደ አገርና እንደ ህዝብ መቀጠል ከፈለግን በህግ ያልተገደበ ኃይል የጨበጡ የወያኔ ዘረኞችን ወይ ህግ እንዲገዛቸዉ ማስገደድ አለዚያም ማስወገድ አለብን። በህግ አክባሪነትና በስርአተልበኝነት መካከል ምንም አይነት ማመቻመች ወይም ድርድር ሊኖር አይገባም።
ከዉጭ ራቅ ብሎ ለተመለከተዉ የወያኔ አገዛዝ ሽብርተኝንትን ለማጥፋት ወይም ለመቆጣጠር ከአቅሙ በላይ ሽር ጉድ ሲል ይታያል፤ ነገሩ “ላም ባልዋለችበት ኩበት ለቀማ” ሆነ እንጂ ወያኔ ሽብርተኝነት ከኢትዮጵያ መጥፋቱን ለማረጋገጥ ከፈለገ ማድረግ ያለበት ነገር አንድ ብቻ ነዉ፤ እሱም ሳይዉል ሳይድር ዛሬዉኑ የኢትዮጵያን ህዝብ ማሸበሩን ማቆም ነዉ። ሽብር እየፈጠሩ የአገርን ሠላምና ጸጥታ አስከብራሁ ማለት የለየለት ምግባረብልሹነት የመሆኑን ያክል ህዝብን በመግደል የተካነ መንግስትን ምነዉ ዝም አልክ ግደል እንጂ ብሎ መማጸንም ምግባረብልሹነት ብቻ ሳይሆን አማኑኤል የሚያስኬድ የዕምሮ በሽታ ነዉ። በዚህ አጋጣሚ የሠማያዊ ፓርቲ መሪዎችን፤ አባላትንና ደጋፊዎችን ትክክለኛዉን ሠላማዊ ትግል አሳይታችሁኛልና ባርኔጣዬን አንስቼ ለእናንተ ያለኘን አድናቆት መግለጽ እወዳለሁ። የቆማችሁለትን የፍትህ፤ የነጻነት፤ የዲሞክራሲና የእኩልነት እሴቶች እንደ ጦር የሚፈሩ ጉግማንጉጎች በሚወስዱት የቀቢፀ ተስፋ እርምጃ ተደናግጣችሁ ከቆማችሁለት ትክክለኛ አላማ ወደ ኋላ እንደማትሉ እርግጠኛ ነኝ። እዉነትና የእትዮጳያ ህዝብ ከእናንተ ጋር ነዉና ማሸነፋችን የተረጋጋጠ ነዉ . . .  ኑ ተነሱ የወያኔን ሽብርተኝነት አብረን እንዋጋ!

No comments:

Post a Comment