Translate

Sunday, November 12, 2017

የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚያስከትል አዲስ የጸጥታ እና የደህንነት ዕቅድ ይፋ ተደረገ

በሰብዓዊ መብት ላይ ከፍተኛ ወንጀል የሚፈጽም አዲስ ዕቅድ ይፋ ተደረገ፡፡ ዕቅዱ የብሔራዊ እና የክልል ደህንነት ጸጥታ ምክር ቤቶች የጋራ ዕቅድ የሚባል ሲሆን፣ ይህን ለማስፈጸምም ራሱን የቻለ አንድ ግብር ኃይል አለው፡፡ በውጭ ዲፕሎማቶች እና በእርዳታ ሰጪ ሀገራት ጫና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማንሳት ተገዶ የነበረው ገዥው ፓርቲ፣ አሁን ደግሞ ቆዳውን ገልብጦ ሌላ ጸረ ህዝብ አዋጅ ይዞ ብቅ ማለቱም ተነግሯል፡፡
ትላንት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት በተደረገው ስበሰባ ላይ የፌደራል እና የከልል የደህንነት አባላት፣ የመከላከያ አዛዦች እና በጸትታ ጉዳይ ላይ የሚሰሩ የገዥው ቡድን ሰዎች ተገኝተው ነበር፡፡ የመከላከያ ሚኒስትሩ እና የብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ ሲራጅ ፈጌሳ፣ በውይይቱ ላይ እንደገለጹት፣ አዲስ የወጣው ዕቅድ ለቀጣይ አንድ ዓመት ይቆያል፡፡ ዕቅዱ በፌደራል እና በክልሎች የተቀናጀ ተሳትፎ እንደሚተገበር የገለጹት አቶ ሲራጅ፣ ዕቅዱም ከፌደራል እስከ ቀበሌ ድረስ እንደሚተገበር ተናግረዋል፡፡

በህዝባዊ ተቃውሞ ከፍተኛ ጭንቅት ላይ የሚገኘው አገዛዙ አንዴ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ የብሔራዊ እና የክልል ደህንነት ጸጥታ ምክር ቤት የጋራ ዕቅድ በማለት የህዝብን ተቃውሞ ለማፈን እየሞከረ እንደሚገኝ ታዛቢዎች ይገልጻሉ፡፡ ሀገሪቱ ተረጋግታለች በማለት በጫና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አንስቶ የነበረው አገዛዙ፣ አሁን ላይ በድጋሚ አዋጁን መመለስ መሳቂያ መሳለቂያ እንደሚያደርገው አምኗል የሚሉ ታዛቢዎች፣ በዚህም የተነሳ የስም ለውጥ በማድረግ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የሚተካ አዲስ ህግ ማውጣቱንም ታዛቢዎቹ ያክላሉ፡፡
በኢትዮጵያ ህዝብ እየተካሔደ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ የስልጣን መናጋት የፈጠረበት አገዛዙ፣ አዲሱን የደህንነት ዕቅድ የተቃውሞ ማብረጃ ለማድረግ እንዳቀደም ታውቋል፡፡ የብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት የተባለው ግብረ ኃይል ውስጥ የመከላከያ፣ የደህንነት፣ የፌደራል እና የክልል የደህንነት አዛዦች የተካተቱበት ሲሆን፣ ግብረ ኃይሉም ህዝባዊ ተቃውሞ በተነሳበት ሰዓት ሁሉ ወታደሮችን እና ፖሊሶችን የማዘዝ ስልጣን አለው፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በስራ ላይ በነበረበት ሰዓት እስከ 60 ሺህ የሚደርሱ ሰዎች መታሰራቸው እና በርካቶችም መገደላቸው ይታወሳል፡፡ አዲሱ ዕቅድም ተመሳሳይ ዓለማ እንዳለው ለመረዳት ተችሏል፡፡

No comments:

Post a Comment