Translate

Friday, September 15, 2017

የትግራይ ህዝብ ሆይ አገርና ህዝብ እያጠፉ ላሉት ልጆችህ መሸሸጊያ ዋሻነትህ ይብቃ



No automatic alt text available.
መስከረም 5 ቀን 2010 ዓ• ም
ወልቃይት፣ አማራ
ኢትዮጵያ
********
የተከበርከውና ኢትዮጵያን ከሌሎች ወንድሞችህ ጋር በመሆን ለዘመናት ከወራሪ በመጠበቅ ታላቅ ውለታ የሰራኸው የትግራይ ህዝብ ሆይ ስማኝ፣ ልጆችህ ክደውሃል፣ ልጆችህ ለዘመናት በሰላምና በፍቅር ከኖርክበት ኢትዮጵያዊ ማንነትህ አፋተውሃል፣ ልጆችህ አባቶችህ ያቆዩልህን የባህር በር አሳጥተውሃል፣ ልጆችህ በመላዋ ኢትዮጵያ በነፃነትና በፍቅር ተዘዋውረህ የምትኖርበትን የነገ የከበረ ኢትዮጵያዊ አንድነት ንደው አንተን ከኢትዮጵያዊ ከፍታ አውርደው በትግራይ ምድረ በዳ የዘር ቡትቶ አልብሰው ያንከራትቱሃል፣ ልጆችህ በደምና በክህደት በተጨማለቀ ማንነት የመንግስተ ሰማያት ኑሮ ሲኖሩ አንተ ነገ ምን ይዞ ይመጣ ይሆን በሚል ፍርሃት ታስረህ ትሰቃያለህ፣
ልጆችህ ከኦሮሞው ከአማራው፣ ከሶማሌው፣ ከአፋሩ፣ ከደቡቡ፣ ከጋምቤላውና ከቤንሻንጉል ጉምዙ ኢትዮጵያዊ ወንድምህ ጋር ደም አቃብተውሃል፣ አሁንም ያንን ስራ እየሰሩ ነው። ልጆችህ ለዘመናት ከአማራ ህዝብ ጋር በመከባበርና በመረዳዳት የኖርክበትን የመልካም ጉርብትና ሰንሰለት በጥሰውብሃል፣ ለራሳቸው ዘረፋ ይመቻቸው ዘንድ ያንተ ያልሆነውን ርስት ከተከዜ ተሻግረህ እንድትናፍቅና ከወንድምህ ከአማራ ህዝብ ጋር በጠላትነት እንድትተያይ አድርገውሃል።
የተከበርከው የትግራይ ህዝብ ሆይ ስማኝ፣ ከአብራክህ ስለወጡ ብቻ ውሸቱን እውነት አድርገህ ተቀብለህ ኖረሃል፣ ክህደታቸውን ታማኝነት አስመስለው እንድታምናቸው ተደርገሃል፣ በባድመጦርነት ወቅት የ70,000 ንፁህ ኢትዮጵያዊያንን ደም ካፈሰሱ በኋላ ለኤርትራ እንደ ተራ ነገር ሰጥተውብሃል፣ ዛሬ አማራው መጣብህ፣ ኦሮሞው ተነሳብህ፣ ጋምቤላው አመፀብህ እያሉ አንተን ከከበረው ኢትዮጵያዊ ማንነትህ ለመነጠል ቀንና ሌሊት ይደክማሉ። አንተ ግን ኢትዮጵያዊነት ክብር ነውና አይቅለልብህ፣ አንድነት ጌጥ ነውና አትጥላው፣ የሰውን መውሰድ ሌብነት ነውና እምቢ በላቸው፣ ነገ ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ወንድሞችህ ጋር የምትኖረው አንተ ነህና ዛሬ የነገ አብሮነትህን እያበላሹ ያሉትን እኩይ ልጆችህ በቃ በላቸው። ሀዘንም ቢሆን ደስታ ከሌላው ኢትዮጵያዊ ወንድምህ ጋር በመሆን ተካፈል። ታላቁ መፅሐፍ መፅሐፍ ቅዱስ "ሰው የዘራውን ያጭዳል፣ በሰፈረበት መስፈሪያም ተትረፍርፎ ይሰፈርለታል" ይላል። ይህ መለኮታዊ ህግ አይቀየርም፣ ሁሌም እውነት ነው፣ ለዘላለም ይሰራል። ታዲያ አንተ ልጆችህ እየዘሩ ያሉትን ጥላቻ ለምን ታጭዳለህ? ዘረኝነትንስ ለምን ትቃርማለህ? ልጆችህ በሰፈሩበት የግፍና የመከራ መስፈሪያስ ለምን ተትረፍርፎ ነገ እንዲሰፈርልህ ዘመን ትጠብቃለህ? አሁን የልጆችህን ክፋት በቃ ልትል ይገባል፣ ነገ በታሪክ ተጠያቂ የሚያደርግህን ስራ ዛሬ ከወያኔ ጋር በመሆን መስራትህን አቁም።
ዛሬ ከአብራክህ የወጡ ከሃዲ ልጆችህ በትግራይ ውስጥ ያሉ የኩናማ፣ የኢሮብ፣ የአገው፣ የአፋርና የአማራ ማንነት መብት ሳያከብሩ የአማራን ህዝብ ለመከፋፈል ቅማንት፣ ኦሮሞ፣ አገው፣ እያሉ ህዝብን ከህዝብ ጋር ደም የሚያቃቡትን እኩይ ሰይጣናዊ ስራ ቸል ብትል ነገ ይህ የደም ዋጋ አንተ እንድትከፍል የማትጠየቅበት ምንም ምክንያት የለም።
በመሆኑም መላው የትግራይ ህዝብ ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ወንድሞቹ ጎን በመሰለፍ እነዚህን የሻቢያ፣ የአረብ አገራት፣ የኢጣሊያንና የምዕራባዊያን ተላላኪና ጉዳይ ፈፃሜ የሆኑ ልጆችህን አሳልፈህ በመስጠት ለፍርድ እንዲቀርቡ በማድረግ ኢትዮጵያዊነትህን በተግባር እንድታሳይ በኢትዮጵያ አምላክ እንጠይቅሃለን። ነገር ግን ዛሬ የሚፈሰውን የአማራ ልጆች ደም፣ የኦሮሞ ልጆች ደም፣ የሶማሌ ልጆች ደም፣ የአፋር ልጆች ደም፣ የጋምቤላ ልጆች ደም፣ የደቡብ ልጆች ደምና የቤንሻንጉል ጉምዝ ልጆች ደም ሰምተህ እንዳልሰማህ፣ አይተህ እንዳለየህ ዝም ብትል ታሪክ እራሱን ይደግማልና ይህ የንፁሃን ደም ዳግም በትግራይ ምድር የማይፈስበት ምንም ዋስትና የለም። ስለዚህ የትግራይ ህዝብ ሆይ ዛሬ ቀን ሳለ ከእውነት ጋር ተስማማ፣ ከወገንህ ጋር ተስማማ፣ ከአገርህ ጋር ተስማማ፣ ከፈጣሪህ ጋር ተስማማ። ደስ አያሰኙም የምትላቸው ቀኖች ሳይመጡ፣ ቀኑ ሳይጨልም፣ ፀሐይም ሳትጠልቅ፣ ደመናውም ሳይከብድ አብሮህ ከኖረውና ከኖርክበት ህዝብህ ጋር አዲስ ቃል ኪዳን ግባ፣ እርቀ ሰላምም አውርድ፣ የበደልከውን የኢትዮጵያ ህዝብ፣ ሰማይና ምድር ይቅርታ ጠይቅ። ይህን ስታደርግ ዛሬ ወያኔ በውሸት አደረግሁልህ ከሚልህ በላይ ይደረግልሃል፣ ታላቅነትህ ይዘመርልሃል፣ ታሪክህም በወርቃማው የኢትዮጵያዊነት ፋይል ይፃፍልሃል።
ሆኖም ግን ይህን የምልህን ወንድማዊ ምክር ቸል ብለህ ከገዳዮች፣ ከከሃዲዎች፣ ከሌቦች፣ ከወንጀለኞችና ከፀረ ኢትዮጵያ ልጆችህ ጎን ዛሬም እንደ ትናንቱ ብትሰለፍ ሰማይ ናስ ምድርም ብረት ትሆንብሃለች፣ ያገኘህ ሁሉ ያሳድድሃል፣ በቀሪ ዘመንህም ተቅበዝባዥና ኮብላይ ትሆናለህ፣ አይደለም ዛሬ ከተከዜ ማዶ የወሰድካቸውን መሬቶች ይቅርና ትናንት ለኖርክበት ቦታም ዋስትና አይኖርህም። ምክንያቱም እግዚአብሔር የእስራኤላውያንን የ430 ዓመት በፈርኦን ባርነት ቀንበር መሰቃየትና ጩኸት ካዬ በኋላ ከዙፋኑ ሲንቀሳቀስ፣ ከማደሪያው ሲወጣ በሙሴ እጅ በግብፃውያን ላይ የሆነውን ድንጋጤና ውርደት ታውቃለህ። ከተፈጥሮ ህግ በላይ አንበጣና ዝንብ ከእስራኤላውያን ጋር በመወገን በፈጣሪ ትዕዛዝ ተሰልፈው ግብፃዊያንን ተዋግተዋል። የፈርኦን ጦር፣ የፈርኦን ሰረገላዎች ግብፃውያንን አላዳኗቸውም፣ ነገም ባንተ የሚሆነው ይህ ነው። ዛሬ ልጆችህ ለክፉ ቀን ብለው በስርቆትና በዘረፋ ያከማቹት የጦር መሳሪያና ሃብት አያድንህም፣ አይታደግህም። ታዳጊህ የኢትዮጵያ አምላክና ህዝብ ነውና ወደ ህዝብህ ተመለስ፣ ዘረኞችን እምቢ በል።
ዛሬ እኔ ታናሹ ወንድምህ የምመክርህን ይህን የእውነት ቃል ብትሰማ በህይወት ትኖራለህ፣ ነገር ግን ይህን ንቀህ ልጆችህ በተጓዙበት የትዕቢት፣ የጥላቻ፣ የዘረኝነት፣ የፀረ ኢትዮጵያዊነት መንገድ ብትጓዝ እውነት እልሃለሁ የኢትዮጵያ አምላክ እስክትጠፋ ድረስ ያሳድድሃል፣ መታሰቢያም አይኖርህም። አሁን ምርጫው ያንተ ነው፣ ኢትዪጵያዉነትን ወይም ወያኔነትን መምረጥ፣ ሁለቱንም ምርጫዎችህን ይህ ታላቅ ህዝብ ያከብርልሃል፣ ነገር ግን ሁለቱም ምርጫዎች በየራሳቸው መንገድ የሚያሸልሙህ ወይም የሚያሰነቅፉህ ይሆናሉ። እንደ እኔ ግን የትግራይ ህዝብ ሆይ አገርና ህዝብ እያጠፉ ያሉ ከሃዲ ልጆችህን በመካድና በቃ በማለት ከኢትዮጵያ ህዝብ ጎን መሰለፍ መተኪያ የሌለው እውነተኛና ትክክለኛ ምርጫ ነው እላለሁ፣ መልሱንም ከአንተ በቅርቡ እጠብቃለሁ።
______________________________________________
ከብላቴናው ወንድምህ ንጉስ ካሌብ
መስከረም 5 ቀን በእለተ አቡነ አረጋዊ 2010 ዓ• ም ተፃፈ
ወልቃይት፣ ጎንደር፣ ኢትዮጵያ
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ፣ ዳርቻዋንም ያስፋ!!

No comments:

Post a Comment