Translate

Thursday, September 14, 2017

ከወልቃይት ጠገዴና ጠለምት የአማራ ብሄር የማንነት ጉዳይ አስተባባሪ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ

ሸክሙን ሲፈሩ መደላድሉን!!

መስከረም 1 ቀን 2010ዓ/ም
Map of Gondar, Ethiopia
የገዥው ቡድን በኃይል አዳፍኖ ለመያዝ የሞከረው ድንገት እንደ እሣተ ገሞራ የፈነዳውና ከአንድ ዓመት በላይ በመላው ኢትዮጵያ በተለይም “የአማራ ክልል” በሚባለው ለገዥው ቡድን የእግር እሣት የሆነበትና ሀገሪቱ ለአንድ ዓመት ያህል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲታወጅ ያስገደደው አላስቀምጥ አላስተኛ ያለው እርስ በርሳቸው እንዳይተማመኑ በጥርጣሬ እንዲተያዩ ያደረገው፤ የአማራን ተጋድሎ የወለደው የወልቃይት ጠገዴና ጠለምት የአማራ ብሔር የማንነት ጉዳይ አስተባባሪ ኮሚቴ ራሳቸው በጻፉት ሕገ- መንግሥቱ በሚፈቅደው መሠረት አንቀጽ 39 ንኡስ አንቀጽ 5ን መሠረት በማድረግ ያቀረቡትን ሕጋዊና ሕገ መንግሥታዊ የመብት ጥያቄ እንደ ሆነ የአደባባይ ምሥጢር ነው።

ይሁን እንጅ ለዚህ ፍትሃዊና ሕጋዊ ጥያቄ ገዥው የወያኔ ቡድን በቀጥታ መልሱን መስጠት ሲገባው በሕዝብ የተወከሉና የተመረጡ ኮሚቴዎችን የአማራነት መብታችን ይከበር በማለታቸው በሌሊት በማፈን በማሰር፤ በመግደልና የሚሰደደውንም አሰድዶ አሁንም አካባቢውን በኃይል እንደያዘ ይገኛል። ይህ የህወሃት ወራሪና ኃላፊነት የጎደለው ቡድን አሁንም ላለፉት 26ና ከዚያም በላይ ረጅም ዓመታት ያስቆጠረ ጊዜ ውስጥ የብዙ አርሶ አደሮችን ሕይወት የቀጠፈ፤ ብዙዎች የታሰሩበትና የተሰደዱበት በራሳቸው ርስት ተወልደው ባደጉበት ቀያቸው መኖር እንዳይችሉ ተደርጎ የተፈናቀሉበት፤ አንድ ጠገዴን በ“ጠ” እና በ“ጸ” በመክፈል ለሙንና ውሃ ገቡን ወደ ትግራይ በመከለል ሕዝብን አለያይቶ አንዱን በአንዱ በማናከስና በማናቆር ፍጅት እንዲፈጠር በማድረግ የሕዝቡን መሬት ለመውረርና ሰፊ ቆዳ ያለው መሬት ባለቤት በመሆን የታላቋን ትግራይ ሪፐብሊክ የመመሥረት ቅጀት እውን ለማድረግ የታለመ መሆኑን የምናውቀው ጉዳይ ነው።
ይህ በዚህ እንዳለ አሁንም ለዘመናት ተዋልዶና ተዋህዶ አንድ አምሳል አንድ አካል ሆነው የኖሩትን አማራና ቅማንት ሕዝብ ለመለያየትና ወደ የማያባራ የርስ በርስ ጦርነት ውስጥ ለመክተት ያለ ሕዝቡ ፍላጎት የመንግሥት በጀት በመመደብ የተለመደ የመከፋፈል ሤራውን ቀጥሎበታል። አሁንም ይህ ወራሪና ተስፋፊ ቡድን በአማራው ሕዝብ ላይ ንቀትና አማራውን ሳያጠፋ የማይተኛ ለመሆኑ ይህ እኩይና ጠብ አጫሪ ተግባሩ ፍንትው አድርጎ ያሳያል። ይህ እየተደረገ ያለ የዘር ማጥፋት ዘር ማጽዳትና የመሬት ወረራ ለወደፊቱ ለሁለቱ ማለትም ለትግራይ ሕዝብና ለአማራው እንደማይጠቅምና ጉዳዩ በሁለቱም ተከባብረውና ተፈቃቅረው ለዘመናት በኖሩ ሕዝቦች መካከል የማይሽር ጠባሳና አደገኛ ሁኔታ በከፋ መልኩ ሊከሰት እንደሚችል መገመት የሚያዳግት አይመስለንም።
ስለሆነም ጉዳዩ አማራውን ብቻ የሚመለከት እስካልሆነ ድረስ ሌላውም ከእንቅልፉ ይነቃ ዘንድ አጥብቀን እንጠይቃለን። በተለይም በግልጽ ማስቀመጥና ማስገንዘብ የምንወደው የአማራው ሕዝብ፤ ባጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ ታሪካዊ ጠላቶች የትግራይ አምባገነን ገዥዎች ወያኔ (ህወሃት) እና ግብረአበሮቻቸው እንደሆኑ ብቻ ነው። የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት የአማራ ብሄርተኝነት የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ በጠገዴ እየተደረገ ያለው ሕዝብ ያልደገፈውና ያልተሳተፈበት የማካለል ሥራና ቅማንትና አማራ እያሉ አንድን ሕዝብ ለመለያየት እየተደረገ ያለው በአገር በቀል ቅኝ ገዥዎቻችን የተቀነባበረን የድምፅ ውሳኔ ሤራ አጥብቀን እንቃወማለን። ወያኔ (ህወሃት) ለሕዝብ የሚቆረቆር ድርጅት ቢሆን ኖሮማ መጀመርያ የወልቃይትን ጥያቄ በመለሰ ነበር።ለዚህ የታደለ አእምሮ ከአንድ የባንዳ ትውልድ መጠበቅ የዋህነት ስለሆነ ሁላችንም ተባብረን የተሳለብንን ስለት የሚሳብንን ቃታና ዘር ለማጥፋት የዘመተብንን የጠላት ርምጃ ለማምከን እንድንነሳ ኮሚቴው ያሳስባል።
የተወሰዱት ታሪካዊ ቦታዎች ወልቃይት ጠገዴ ጠለምት እንዲሁም ሌሎች ወደ ጥንት ቦታቸው ይመለሱ!!
የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት ሕዝብ አማራ ነው!!
በአፋኝ ቡድን በጨለማ ተይዘው በግፍ የታሰሩ የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት ኮሚቴ አባላት በአስቸኳይ ይፈቱ!!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!

No comments:

Post a Comment