Translate

Monday, July 11, 2016

በፈተና ስም ማህበራዊ ሚዲያው አፈና ተካሄደበት

Image result for social media
ሐምሌ ፬( አራት ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በመላ አገሪቱ የፌስ ቡክ፣ ትዊተር፣ ኢንስታግራም እና ቫይበር የመልክት መለዋወጫ ዘዴዎች የተዘጉ ሲሆን፣ ገዢው ፓርቲ እርምጃውን የወሰድኩት የአስራ ሁለተኛ ክፍል ተማሪዎች ተረጋግተው ፈተና እንዲፈተኑ ለማስቻል ነው ብሎአል። ይሁን እንጅ እርምጃው በአገሪቱ ውስጥ እየተባባሰ ከመጣው የፖለቲካ ቀውስ ጋር እየተያያዘ ነው። ገዢው ፓርቲ ለፈተና በሚል አለማቀፍ ገጽታውን አያበላሽም የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች፣ ምክንያቱ የማህበራዊ ሚዲያው እየፈጠረ ካለው ተጽኖና በአገሪቱ እየታዬ ካለው አለመረጋጋት ጋር የሚያያዝ ነው በማለት አስተያየት ይሰጣሉ። ተማሪዎች ፈተናውን ተረጋግተው እንዲወስዱ ለማድረግ እንዲሁም ካላስፈላጊ ውዥንብር እንዲድኑ በማሰብ የተወሰደው እርምጃ ጊዜያዊ ነው ሲሉ የመንግስት ቃል አቀባይ ጌታቸው ረዳ ተናግረዋል። ማህበራዊ ሚዲያ ተማሪዎችን የሚያዘናጋ መሆኑ ተረጋግጧል በማለት ቃል አቀባዩ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

ገዢው ፓርቲ ማህበራዊ ሚዲያውን ለመዝጋት የተገደደው ከዚህ ዘገባ በሁዋላ ሲሆን፣ ማህበራዊ ሚዲያው በኢትዮጵያ ውስጥ እየፈጠረ ያለው ተጽኖ ከፍተኛ እየሆነ መምጣቱንም የሚያመላክት ነው። ትምህርት ሚኒስቴር ፈተናው አልተሰረቀም በማለት የሰጠውን መግለጫ በቂ ሆኖ ባለማግኘቱ ማህበራዊ ሚዲያውን እስከመዝጋት ከደረሰ፣ ወጣቱ ትውልድ መንግስት የሚሰጠውን መግለጫ የማያምንበት ደረጃ መድረሱንና የመረጃ ምንጩንም ማህበራዊ ሚዲያውን ማድረጉን የሚያመለክት ነው በማለት አስተያየቶች እየቀረቡ ነው። በአለም ላይ የኢንተርኔት የመገናኛ ብዙሃንን የሚያፍኑ አገሮች አለማቀፍ ገጽታቸው ይበላሻል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኢንርኔትን ማፈንና መሰለል የሰብአዊ መብት ጥሰት መሆናቸውን ባለፈው ሳምንት ወስኗል፡፡ለአለማቀፍ ገጽታው በከፍተኛ ደረጃ የሚጨነቀው የኢህአዴግ መንግስት ሌላ የከፋ ችግር ካልገጠመው በስተቀር እንዲህ አይነቱን ከፍተኛ ዋጋ የሚያስከፍል እርምጃ ለተማሪዎች አስቦ አይወሰድም በማለት አስተያየቱን የሰጠን በኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖርና በማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚ የሆነ ስሙ እንዳይገለጽ የጠየቀ ጸሃፊ፣ ከፈተናው ይልቅ ገዢው ፓርቲ ፈተናውን ሰበብ አድርጎ በአደጋ ጊዜ ማህበራዊ ሚዲያውን ማፈን እንደሚችል ለማየት ያደረገው ሙከራ ነው ብሎአል። “ ፈተናን ለመቋቋም የተወሰደ እርምጃ ነው ቢባል አለማቀፍ ትችቱ ሊቀንስ ይችላል በሚል ስሌት በሌሎች አጋጣሚዎች ለመውሰድ ያልደፈረውን እርምጃ አሁን ለመውሰድ መሞከሩን እናያለን” የሚለው ጸሃፊው፣ የአሁኑ እርምጃ ከዚህ በፊት የኢንተርኔት አገልግሎትን እንደማያፍን ሲናገር የነበረውን የሚያፈርስ፣ ከአፈና ጋር በተያያዘ ሲቀርቡ የነበሩ ትችቶች ትክክለኛ መሆናቸውን ያረጋገጠ በመሆኑ፣ መንግስት ከእንግዲህ ኢንተርኔት አፍኜ አላውቅም በሚል አፉን ሞልቶ ለመናገር እንዳይችል አድርጎታል” ሲል አስተያየቱን አክሏል። እዮስያስ የተባለ አስተያየት ሰጪ በኢሜል ባደረሰን አስተያየት ደግሞ፣ “የገዢው ፓርቲ ውሳኔ የተቃዋሚው ሃይል በአገር ውስጥ ያለው ተቀባይነቱ እየጎለበተ መምጣቱን ማሳዬት ብቻ ሳይሆን፣ ገዢው ፓርቲ በራስ መተማመኑ እያለቀበት ወደ ጉልበት እርምጃ እየገባ መሆኑን ያሳያል” ብሎአል። ገዢው ፓርቲ ኢንተርኔት በማፈን ከፍተኛ የገንዘብና የፖለቲካ ኪሳራ ደረሰበት እንጅ አላተረፈም ሲል አክሏል። በአፍሪካ ውስጥ ኢንተርኔትንና የተቃዋሞ እና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን በማፈን በአፍሪካ ቀዳሚ ከሆኑ አገራት ተርታ እንደምትሰለፍ ቢቢሲ ዘግቧል። ቢቢሲ በኢትዮጵያ ማህበራዊ ሚዲያው በተደጋጋሚ የሚፈታፈን ቢሆንም፣ በመላው አገሪቱ በዚህ መጠን ሰታፈን ግን ለመጀመሪያ ጊዜ ነው ብሎአል። ለቢቢሲ አስተያየቱን የሰጠው ማንነቱ ያልተጠቀሰ ግለሰብ፣ ይህ ጅማሮ ነው፣ ከዚህ ይማሩና በሚቀጥለው ጊዜ ተቃውሞ ሲኖር በመላ አገሪቱ እገዳ ይጥላሉ” ብሎአል። ገዢው ፓርቲ እገዳውን መጣሉን ተከትሎ በአሁኑ ሰአት አገሪቱ ምን ያክል ገንዘብ እንደከሰረች ለማወቅ ባይቻልም፣ ደንበኞች ፌስቡክ፣ ሜሴንጀር፣ ፋይበርና የመሳሰሉትን ለመጠቀም የኢንተርኔት ግንኙነት የሚያስፈልጋቸው በመሆኑ፣ ቴሌኮሚኒኬሽን ከኢንተርኔት አገልግሎት ( Connection fee) የሚያገኘው ገቢ ይቀንስበታል።

No comments:

Post a Comment