Translate

Wednesday, February 26, 2014

ሰሞነኛ ጉዳዮችን በወፍ በረር አንቀጾች ስንቃኛቸው

ሰሞነኛ ጉዳዮችን በወፍ በረር አንቀጾች ስንቃኛቸው
ይሄይስ አእምሮ (ከአዲስ አበባ)
(yiheyisaemro@gmail.com)
መግቢያ
“እግዚአብሔር የሚጠላቸው ስድስት ነገሮች አሉ፤ እንዲያውም እርሱ የሚጸየፋቸው ሰባት ናቸው፤ እነርሱም፡- ‹በንቀት የሚመለከት ዐይን፤ ሐሰት የሚናገር ምላስ፤ ንጹሖች ሰዎችን የሚገድሉ እጆች፤ ክፉ አሳብ የሚያፈልቅ አእምሮ፤ ወደ ክፋት ለመሮጥ የሚቸኩሉ እግሮች፤ በውሸት ላይ ውሸት እየጨመረ የሚናገር ምሥክር፤ በወዳጆች መካከል ጠብ የሚያነሣሣ ሰው› ናቸው፡፡” ምሳሌ 6፣ 16 – 19

ከአፍ ከወጣ አፋፍ ነው
አለምነው መኮነን የተባለው የወያኔ እንደራሴ በአማሮቹ ሀገር እምብርት ዋና ከተማ ባሕር ዳር ላይ በዝግ ስብሰባ ተቀምጦ በወሻከተው ነገርና መዘዙ ሳቢያ ብዙ እየሰማን ነው፡፡ ሰውዬው ጅል መሆን አለበት – አለዚያም ወፈፌ፤ ከአፍ የወጣ ነገር የትም ሊደርስ እንደሚችል ካጣው እውነተኛ በሽተኛ ነው፤ ከተራበ ለጠገበ አዝናለሁ መባሉ ይህን ዓይነት ዕብሪት ለመግለጥ ነው፡፡ ወያኔዎች ሊታወሱም ሆነ ሊረሱ የማይፈልጉ ዕንቆቅልሾች መሆናቸውን በሰሞኑ ድርጊታቸው መገንዘብ ይቻላል፡፡ በአሁኑ ኢትዮጵያዊ መቼት አማራን መሳደብ ትርጉም የሌለውና የደረቀ ወንዝን እንደመሻገር የሞተ ፈረስን እንደመጋለብ ያለ ዶንኪሾታዊ የጀብደኝነት ፉከራና ሽለላ  ነው፤ ስንትና ስንት ወቅታዊ ጠላት እያለ አርፎ የተቀመጠን ምሥኪን ወገን በጠላትነት ፈርጆ በተደጋጋሚ ኅሊናን ለማቁሰል መጣደፍ የዕድሜ ማራዘሚያ ክኒንን በከንቱ ውጦ እንደመጨረስ ያለ ሞኝነት ይመስለኛል፤ ወያኔዎች ሆይ! ያደርሳችኋል ግዴላችሁም – በኔ ይሁንባችሁ – እስከዚህን ቅጥ አምባራችሁ አይጥፋ፤ ጥጋባችሁን እንደምንም ቻል ለማድረግ ሞክሩ – የዱባ ጥጋብ ካለስንቅ እንደሚያዘምት እናንተም ይህች በሸፍጠኝነትና በሁለገብ ዓለማቀፋዊ ሻጥር የያዛችኋት አዱኛና የመንግሥት ሥልጣን ናላችሁን አዙራችሁ የምትሆኑትን አጥታችኋልና ፈጣሪ የምትቋምጡለትን ዕብሪት አስተንፋሽ እስኪልክላችሁ ባልተቆጠበ ትግስት ተጠባበቁ፤ ፈጣሪ “የነገሩትን የማይረሳ፣ የለመኑትን የማይነሳ” ቸር አምላክ ነውና የምትፈልጉትን የጦር ድግስ ይነፍገናል ብላችሁ ሃሳብ አይግባችሁ፡፡ የዱሮ ጦር ሠራዊት እንደናንተ ጥጋብ ሲወጥረው  ጦር አምጪ እያለ መሬትን ይደበድብ ነበር አሉ፡፡ በምታምኑበት ይሁንባችሁና አማራውን ተውት – ብሶቱን በእህህኣዊ ዕንባው ወደላይና ወደሚመለከተው አካል ያስተላልፍ፡፡ ጓድ አለምነው መኮንን ስማኝ- ቴፕ ሪከርደር እንኳን  የሰጡትን ላለመቀበል አንዳንዴ ያንገራግራል – ችንጊያው ሲጎትት፣ አልማዙ ሲበላ ወይንም ባትሪው ሲያልቅ፡፡ አንተ ግን በአማራው መሀል ተቀምጠህ በጌታዋ እንደተማመነችዋ በግ ቀን በጣለው ሕዝብ ላይ እንዳንዳች የሚቀረና ቅርሻትህን ለቀቅኽው፡፡ ግዴለም፡፡ ግፍን ያላሳለፈ፣ ጡርን ያልሰማ ወደ ደህና ቀን አይወጣምና ይህም ለበጎ ነው፡፡ ለአንተ ግን “መጥኖ መደቆስ ቀድሞ ነበር” ማለትን እወዳለሁ፡፡ አሁን ማጣፊያው ሲያጥርብህና ንግግርህን በማሳመር ሰውን ለማስገልፈጥ እንደዋዛ በወረወርከው ስድብ ሕዝባዊ የተቃውሞ ውርጅብኝ ሲበራከትብህ “የአራት ቀናት ንግግር በኮምፒውተር ተቆርጦ ተቀጥሎ ነው እንጂ የወጣሁበትን ሕዝብ እንዴት ልሳደብ እችላለሁ?” ብለህ በዐይኔን ግምባር ያ’ርገው መሃላ ብትሸመጥጥ የእናቴ መቀነት አሰናከለኝ ዓይነት የተበላ ዕቁብ መሆኑን ልትዘነጋ አይገባም፡፡ አንተ አማራን የተሳደብከው የተማመንከውን ተማምነህ ምናልባትም በተማመከው ኃይል ታዝዘህ ነው ብንል አንሳሳትም፤ የወደፊቱን እንጃህ እንጂ ለአሁኑ ከሽልማት በስተቀር የሚገጥምህ ክፉ ነገር እንደሌለ በደኖንና ዐርባጉጉን በማስታወስ ብቻ በሚገባ እንረዳለን፡፡ ዱባ ካላበደ መቼም ቅል አይጥልም፡፡ አማራ ነኝ የምትለው አለምነውም ሆንክ የሌላ ብሔር አባል ወይም ነጭም ይሁን ጥቁር የማንኛውም የሌላ ሀገር ዜጋ  አንድን ሕዝብ ለመሳደብ ምንም ዓይነት አመክንዮ የለውም፡፡ ቅጽሎች የተፈጠሩት ይህን ዓይነት አወዛጋቢ ሁኔታ ለማስወገድ ነው፡፡ አንተ የትግራይን ብሔር በጅምላ ተሳድበህ ቢሆን ኖሮ በአሁኑ ወቅት ሥጋህ ለጅብ ነፍህን ለጀሃነብ ሰጥተው፤ህ በሣምንታት ውስጥ ተረስተህ ነበር – ምሳሌ ነው – የትግራይ ሕዝብ እንደሕዝብ ባለመሰደቡ የሚቆጨው ሰው ካለ የሸንጎ ፍርድ የሚገባው የመጨረሻ ወንጀለኛ ሰው መሆኑን አጥቼው አይደለም፤ ሕዝብ በደግ እንጂ በክፉ ሊነሣ የሚገባው ኑባሬ አይደለም፤ አልተለመደምም፡፡ ነገር ግን ዘረኛው የወያኔ መንግሥት አማራውን ራሱ ተሳድቦ ስላላረካው ራሱ በሾመውና በአማራነት በፈረጀው ‹ባለሥልጣን› አማራን ሊያሰድበው ወደደ፡፡ ይህ ደግሞ የግፍ ግፍ ነው፡፡ ፈረንጆቹ “adding an insult to injury” እንደሚሉት ነው፡፡ ስብሃት ነጋ፣ ሣሞራ(ሙሃመድ) የኑስና መለስ ዜናዊ አማራን በመሳደብ የሚወዳደራቸው የለም – እስኪሰለቻቸው እየሰደቡ አሰድበውታል፤ ግን ስድብ አይጣበቅ ሆኖ ተቸገሩ፡፡ እንግዲህ የነሱ ስድብና የነሱ የዘመናት ጭፍጨፋ ሊያረካቸው አልቻለም ማለት ነው፡፡ ያሳዝኑኛል፡፡ አንድን ጠላቴ ነው የምትለውን ሰው አንተው ራስህ በጥፍርህም፣ በጥርስህም፣ በጠበንጃህም፣ … በቻልከው ሁሉ ቦጫጭቀኸው እየተንጠራወዘ አልሞትልህ ሲል በከፊልም ይሁን በሙሉ በ“ደም” ይዛመደዋል የምትለውን ሰው ፈልገህ በእጅ አዙር ለማጥቃት መሞከር ከሰይጣናዊነት ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡
ስም ይቀድሞ ለነገር
ኃይለመድኅን አበራ ተገኝ ታሪካዊ ሥራ ሠራ፡፡ ወርቃማ ሥራ ሺህ ጊዜ በማንም ቢደጋገም ሊሰለች አይገባም፡፡ እናም እኔም እላለሁ – ይህ ወጣት ብዙ ክፍለ ጦሮች ሊሠሩት የሚከብዳቸውን ታላቅ ጀብድ ሠርቷል – ልክ እንዳገሩ ልጅ እንደአበበ ገላው (‹ሽጉጥ አልታጠቀ መትረየስ የለው፤ ባንደበቱ ገዳይ አበበ ገላው› ተብሎ የተገጠመውም እዚያችው ሥርፋ ለበቀለው ብርቅዬ ኢትዮጵያዊ ነው፡፡) የዚህ ረዳት አብራሪ ስም ራሱ ተናጋሪ ነው፡፡ “የመድሓኒት ኃይል የነጻነትን ቀንዲል ሊያበራልን ተገኘ” እንደማለት ነው – የት ተገኘ? ከዚያችው ጉደኛ ባህር ዳር ከተማ፡፡  ባህር ዳር መድሓኒትም መርዝም የሚበቅልባት ቦታ ሆነች፡፡ መርዝ ያልኩት አለምነውን የመሰለ ሰው እዚያችው ከተማ ውስጥ የተናገረውን ስለተናገረ ነው – እዚያው እከተማው መሀል ይሁን ዳር ላይ ተጎልቶ በማን አለብኝነት አማራን ዘለፈ፤ የምን መዝለፍ ብቻ በጋብቻ ከልክል ስድብ ዶቃ ማሰሪያው ድረስ አስታጠቀው እንጂ! አሁን በሞቴ ከሰደበኝ ስድቤን አምጥቶ የነገረኝ እንዳትሉኝ እንጂ የ“ልጋጋምንና የለሃጫምን ልጅ ማን ያገባል? ከሰባቱ ልጆቼ አራቱ ጉድ ፈላባቸው! ሦስቱስ አለምነውን ቀድመው በማግባታቸው ተገልግለዋል፡፡ ለነገሩ አለምነው ብቻ አይደለም አማሮችን ለማዋረድ ወያዎች መቀመጫ ውስጥ ሄዶ የተወተፈ፤ እነገነት ዘውዴን፣ እነክፍሌ ወዳጆንና ሌሎች ሆዳሞችን በአለምነው ቅርጫት ልንከታቸው እንችላለን፡፡ የእናት ሆድ ዥንጉርጉር ነው፡፡ [“ትልቅ ነበርን ፤ ትልቅም እንሆናለን” - አሁን ከሬዲዮ ሰማኋት፤ ደስ የምትለኝ አባባል!]
ፆመ ኹዳዴ ተጀመረ!
ኹዳዴን የምትፆሙ በተለይ የኦርቶዶክስና የካቶሊክ እምነት ተከታዮች እንኳን ለፆም መያዣው አደረሳችሁ (አብዛኞቹ ካቶሊካውያን የሚፆሙት ክርስቶስ የፆማቸውን ዐርባ ቀናት በመሆኑ የነሱ ፆም መያዣ ገና አልገባም፤ ብሎም ቢሆን እንደባህል ወስደው የኦርቶዶክስን የፆም ይትበሃል የሚከተሉም አሉ – 55 ቀናትን የሚፆሙ – ለቀድሞ የእሥራኤል ንጉሥ  ኃጢኣት ጭምር መሆኑ ነው)፡፡ ፆሙን በሰላም አጠናቅቃችሁ የጌታችንን የመድሓኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ብርሃነ ትንሣኤ ለማየት እንዲያበቃችሁ የኅያው እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ ይሁንልን፡፡ ፆምን መፆም ጥሩ ነው፡፡ ጸሎት መጸለይም ጥሩ ነው፡፡ መመጽወት ጥሩ ነው፡፡ መቀደስና እግዚአብሔርን በከበሮና በጸናጽል፣ በእምቢል፣ በበገናና በማሲንቆ ማወደስም ጥሩ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናትን ማነጽና ማሳነጽ ጥሩ ነው፤ እነዚህና መሰል ደጋግ ሃይማኖታዊ ተግባራት ከፈጣሪ ያገናኛሉ – የፋክስ መስመሮች ናቸው፤ እንዴት መከናወን እንደሚገባቸው መረዳት ግን ይገባል፡፡ አለበለዚያ ለቅጽፈት ይዳርጋሉ ብሎ ማስፈራራቱ ከዘመኑ ሃይማኖታዊ ዕውቀት አንጻር ተጠየቃዊ መከራከሪያ ባይሆንም በግንጥል ጌጥነታቸው ግን ነውረኝነታቸውን መጥቀስ ይቻላል፤ ግንጥል ጌጥ አሣፋሪ ነው፡፡ ለሁለት ጌቶች መገዛትም እንዲሁ፡፡ የሚታየኝን እናገራለሁና ለመቆጣት ያቆበቆባችሁ አደብ ግዙ፡፡ ደግሞም እውነትን ተጋፍታችሁ የትም አትደርሱም፡፡ ይህ ጉዳይ ሁለት አንቀጾች ሊሆንብኝ ነው መሰለኝ፡፡
ከገዳይና ዘራፊ መንግሥት ጋር መቀመጫዋን ገጥማ (ወንበር ለማለት አይደለም) አብራና ተባብራ ሕዝቧን የምታስፈጅ ቤተ ክርስቲያን ጸሎትና ምህላዋ ከዳመና በላይ ይቅርና ከዛፍና ከቤት ጣሪያ በላይም አልፎ አይሄድም – ይህን ለማለት ጉዝጓዜ መጽሐፍ ቅዱሱ ስለሆነ ማንም ያንብበውና ይረዳው፤ የጊዜውን መድረስም በእግረ መንገድ ይገንዘብ፡፡ ቀን ከእግዚአብሔር መንገድ ወጥቶ እንደልቡ ሲፏንንና በየእንትን ቤቱ ሲፋልል የሚውል ካህንና ደብተራ ሌሊት በቤተ መቅደስና በቅኔ ማኅሌት በያሬዳዊ ዜማና ወረብ ቃለ እግዚአብሔርን ማሽር ሲያቀልጥ ቢያድር የክርስቶስን አነጋገር ልዋስና – እውነት እውነት እላችኋለሁ አንድም ጽድቅ የለም፤ ልፋታቸው “የከንቱ ከንቱና ንፋስንም እንደመከተል ነው”፡፡ እንዲያውም ካህናትና ጳጳሳት በእግዚአብሔር ላይ እንደሚያሳዩት አመፃና የትዕቢት ጉዞ ቢሆን ኖሮ እስካሁንም ሁላችንም አልቀን ነበር፤ አንዳችንም ባልተረፍን፡፡ ነገር ግን የሚቀልዱበት እግዚአብሔር ትግስቱና የቸርነቱ ብዛት ገደብ የሌለው በመሆኑ ይሄውና “እስካሁን በአማርኛ በመቀደሴ ይጸጽተኛል፤ ከኢሕአዴግ ጋር መጪው ዘመን ብሩኅ ነው፤ ጭቃ ሕዝብ፤ “shoot him!”፣ የህዳሴውን ግድብ ያልደገፈ ኢትዮጵያዊነቱን በራሱ ገፍፎ ጥሏል፤ …” የሚሉ “ብፁኣን”  አባቶችና የነሱን ስም በየቅዳሤው እያወሱ የሚቀድሱ ደናቁርት ቀሣውስት እያሉን በመቻያው ችሎናል፤ አስችሎንማል፡፡ አንድም የበቃ ካህንና የሃይማኖት መሪ በሌለን ሁኔታ ወጉ አይቀርም “ፆም ሊፆም” በቀደም ለት ተያዘ፡፡ ሊያውም ከፋሲካው በበለጠ የሚፆመውም የማይፆመውም ለነፍሱ ሳይሆን ለሥጋው በሚንሰፈሰፍበት የገበያ ግርግር፡፡ ሃይማኖታችን ለሆድና ስለሆድ ወደተለወጠባት የልማድ እምነት ስትቀየር እንደማየት መጥፎ አጋጣሚ የለም፡፡ በኪነ ጥበቡ ይቅር ይበለን፡፡ አንድ አጭር ማሳሰቢያ አለኝ፡- ጆሮ ያላችሁ የማንኛውም ሃይማኖት አባቶች አዳምጡኝ፤  ይበልጡን ለገንዘብና ለተደላደለ ቅንጦተኛ ሕይወት ስትሉ ከእውነቱ መንገድ ወጥታችሁ ለሥጋችሁ ማደራችሁን በግልጥ የምታሳዩበትና የምታሾፉበት ፈጣሪ በራሱ ጊዜ የሚፈልገውን የማስተካከያ እርምጃ መውሰዱ የሚጠበቅና የማይቀርም ሆኖ አሁን ለጊዜው ግን እንዲህ አድርጉ፡- አለሰዓት የምታስጮኹትን ዘመናዊ የድምፅ ማጉያ ነገ ዛሬ ሳትሉ ልጓም አብጁለት፡፡ የታመመ አለ፤ በሥራ የደከመ አለ፤ የአንድኛችሁን ጩኸት ሌላኛችሁ በማረፊያና መተኛ ሰዓት ይቅርና በመደነቋቆሪያው የቀኑ ጊዜም መስማት የማይፈልግ አለ፤ ልክ መሆን አለመሆኑ የራሱ ጉዳይ ሆኖ በምንም ነገር የማያምን ግን በቤቱ በሰላም ተኝቶ ማደር የሚገባው የአንዲት ሀገር እኩል ዜጋ አለ፤ በቤተ እምነቱ እንጂ ቤቱ ድረስ በሚመጣ ሰዓት ያልተገደበበት ረብሻና ሁከት በጸሎት ስም መታወክ የማይፈልግ አለ፡፡ ይህ ሁሉ ከጉዳይ መጣፍ አለበት፡፡ ሁሉም ነገር በሥርዓት መከናወን ይገባዋል፡፡ ባህልንና ሃይማኖትን ተመርኩዞ ዜጎችን ማስጨነቅ ተገቢ አይደለም፤ ፈጣሪም የሚወድላችሁ እንዳይመስላችሁ፡፡ ለርሱ እንዲያውም የአእዋፋትና የዕፅዋት የተፈጥሮ ድምፅና ውዝዋዜ፣ የነፋሳትና የደመናት ዳንኪራና ንፅውፅውታ ከእናንተ በተሻለ የውዳሤና አምልኮት መባዎች ናቸው፤ የነሱ ደረቅና የለበጣ አይደለም – እውነት ነው፡፡ ደግሞም መጽሐፉ “የቄሣርን ለቄሣር፣ የእግዜርን ለእግዜር” ስለሚል በደረቅ ሌሊት ከፍተኛ ድምፅ በሚያወጣ ማይክሮፎን ሀገርን ማናወጥ መብት አይደለም – እንደዚያ አስፈላጊ ከሆነ ከከተማዎች ውጪ በሚገኙ ገዳማትና አብያተ ክርስቲያን ሕዝብን በጥቅል ሳያውኩ ማከናወን ይቻላል፡፡ በዱሮ ጊዜ ቤተ ክርስቲያናት ሲሠሩ ከመኖሪያ አካባቢዎች ራቅ ይሉ ነበር፤ እንዲያም ሆኖ ኤሌክትሪካዊ ማጉሊያዎች ስላልነበሩ እንደዛሬው ሁከት አልነበረም፡፡ ስለጸሎት ምንነትና ርዝማኔም የክርስቶስን አስተምህሮዎች ደግማችሁ አጢኑ፡፡ እውነቴን ነው የምለው – አሁን አሁን በፉክክርና በደራ በየሽርንቁላው እንደጠላ ቤት በሚቀለሱ የእምነት ቤቶች ሕዝብ እየተረበሸ ነው፤ ብሶቱን ስለማይናገርና ስለሚያፍርም እንጂ ሕዝቡ በዚህም እየተማረረ ከመጣ ሰነባብቷል፤ ለስንቱስ ቀን ጠብቀንለት ይዘለቃል? ከቤተክርስቲያን ግድግዳ በጥቂት ሣንቲ ሜትሮች ወይም በጣት የሚቆጠሩ ሜትሮች ርቀት ላይ የወንደላጤዎች መኝታ ቤት ወይም የተከራይ ሴተኛ አዳሪዎች ክፍል ወይም የጭፈራ ቤት መኖሩን ታውቃላችሁ? ብርሃንና ጨለማ ምን ኅብረት አላቸው? ችግር አለ ምዕመናን፡፡ ብዙ ችግር አለ፡፡ የቋራው መይሳው ካሣ በዳግም ልደታዊ የሂንዱይዝም እምነት መሠረት ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ተብሎ እስኪመጣ አንጠብቅ፡፡ ተግባራችን መስታውታችን ይሁነንና ራሳችንን በመመርመር  እንደእግዚአብሔር ትዕዛዛት እንጂ እንደሰይጣን ደባ አንጓዝ፡፡ ልበ ወኩልያትን የሚመረምር የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፣ አንድ ካህን በሥውርም ይሁን በግልጥ ምን እየሠራ የእምነቱ ትውፊታዊ መገለጫ የሆነውን ጽላት ወይም ታቦት እንደሚሸከምና ቃለ ምዕዳን እንደሚሰጥ ፈጣሪ ሳያውቅ ይቀራል ብሎ የሚያስብ ጅላጅል ቄስ ካለ ከሕዝቡ ንቃተ ኅሊና በእጅጉ የወረደ የንቃት ደረጃ ላይ ይገኛል ማለት ነውና ሣይረፍድበት ራሱን ይፈትሽ – አብረን ስለምንኖር ሙሉ በሙሉ እንተዋወቃለንና … ፡፡ (“ውርድ ከራሴ፤ እኔ የለሁበትም…” እያለች የምትዘፍን ሴት አቀንቃኝ ከአንዱ ኤፍኤም በአሁኒቷ ቅጽበት ትሰማኛለች፡፡) ሕዝቡን አደንቁራ ያስቀረች ሃይማኖታችን መሠረቷን ሳትለቅ ልትታደስ ይገባታል፤ ይህ የሚሆነው ከትንሽ ጀምሮ ነውና እዚህ ላይ የጠቀስኩትን ሃሳብ ልብ የሚል ልብ ይበል፡፡ የተለመደ ቅጥልጣይ ሰው ላይ መለጠፍ የማይሠራባቸው ሁኔታዎች መኖራቸውንም ልብ እንበል፡፡ እውነት ብትመር ብትጎመዝዝም እንደምንም ማወራረድ ነው፡፡ አካሄዳችን የተበለሻሸ ነው፡፡ ይታረም፡፡ በዚያ ላይ “ባለቤቱን  ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ” እንዲሉ ሆኖ ከቄሶቹ ባልተናነሰ በፈጣሪ ላይ የሚዘብቱት ወያኔዎች የማይፈርድባቸው መስሏቸው ከመነሻቸው ጀምረው ሃይማኖትን ለማጥፋት ምን ምን እያደረጉ እንደመጡ የምናውቀው ነው፡፡ ይሄውና በነሱና በተባባሪ የሃይማኖት አባቶቻቸውና ጭፍሮቻቸው የበከተ ዲያብሎሣዊ አመራር የተነሣ ዛሬ ዛሬ በአሥር ሚሊዮን የሚቆጠሩ ምዕመናን ግራ እየገባቸውና መዳን በሃይኖማኖት መለዋወጥ እየመሰላቸው ወደሌሎች የሃይማኖት ዘርፎች እየነጎዱ ነው፡፡ ይንጎዱ፡፡ ሥራቸው ያወጣቸዋል፡፡ እዚያም ቤት እሳት መኖሩን ያላወቁ ማለትም ከሸሹበት ቤት የጠሉት እንከን ወይንም ገመና በሚሸሹበት ቤት የሌለ የሚመስላቸው የዋሃን በሚደርስባቸው ሥነ ልቦናዊና አእምሯዊ እንግልት ለጊዜው ማዘናችን ባይቀርም ሁሉም የሥራውን ማግኘቱ የነበረና ያለ ነውና በዚያ እንጽናናለን፡፡ የሃይማኖተኞች ጠርዝ የለቀቀ ውስልትናና ሃሳዊነት ከዓለማውያን ሶዶም ወገሞራዊ ብልግና ጋር ሲጋጠሙ ለሚፈጠረው አርማጌዴዎናዊ ትዕይንት ዝግጁ ሆነን እንድንጠብቅ  በዚህ አጋጣሚ የጋራ ግብዣ ማስተላለፍ እፈልጋለሁ፡፡ ግን ዛሬ ምን ነካኝ? የጤና ነው ብላችሁ ነው? አሃ፣ በቃ! እስከመቼ?
በሦስት ዓመታት ውስጥ ከ20 እስከ 38 ሚሊዮን ብር ወጪ
እውነተኞቹም ይሁኑ የተጋቦት ወያኔዎች ራሳቸው መርጠው፣ ራሳቸው ሾመውና ራሳቸው መርዘው ለህመም የዳረጉትን የአንድ ክልል ‹ፕሬዚዳንት› ለማሳከም ብዙ ሚሊዮን ብር ከዚህ ምስኪን ሕዝብ ደረቁቻ ካዝና መመዝበራቸውን ሰማን – በአነስተኛ ግምት 20 ሚሊዮን ብር – በከፍተኛ ግምት 38 ሚሊዮን ብር፡፡ የኢትዮጵያ ካዝና መቼም ለዜጎቹ አይሆንም እንጂ ለባለሥልጣናትና ባለሥልጣናት ለሚመሳጠሯቸው የውጭና የሀገር ውስጥ የሥራ ተቋራጮች የወርቅ ጎተራ ነው፡፡ የሀገሬ ባላገር በባዶ እግሩ እየሄደ፣ ጨርቁ አልቆ ራቁቱን በብርድ ቸነፈር እየተሰቃዬ አፍንጫውን ተይዞ ከሚከፍለው ግብር ሰባት ሚሊዮን ብር የሚገዛ መኪና ለባለሥልጣን የሚሰጥባት ሀገር ሆናለች አሉ – ኢትዮጵያ፤ በየመሥሪያ ቤቱ አላግባብ የሚባክነው ገንዘብ፣ ሥራው ከመጠናቀቁና ርክክብ ከመፈጸሙ በፊት የሚፍረከረከው የፈረደበት የመንግሥት መንገድና ሕንጻና በቀላል ብልሽት የሚጣለው ተሸከርካሪና ሌላ ንብረትማ አይነሣ፡፡ እንደመጥፎ ዕድል ሆኖ ሀገራችን ብዙ ታማሚ ባለሥልጣናትን በውድ ወጪ ሊያውም በውጪ ሀገራት በማስታመምም ትታወቃለች፡፡ ጥቂት አብነቶችን ለመጥቀስ ያህል- መለስ ዜናዊ፣ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፣ መሀመድ የኑስ፣ አለማየሁ አቶምሳ፣ ሙላቱ ተሸመ፣ ሥዩም መስፍን እና ሌሎችም ሙትና ቁስለኞች ሁሉ ሞሰብ ገልባጮች ናቸው፡፡ ባለሥልጣኖቻችን ኢትዮጵያቸውን በዕድገትና ሥልጣኔ ወደላይ ስላስፈነጠሯት ለራስ ምታትና ለጉንፋንም ሳይቀር አውሮፕላናቸውን እያስነሱ ከቅርብ ጎረቤት ኬንያ ጀምረው ደቡብ አፍርሪካ፣ ሳዑዲና ታይላንድ እንዲሁም አውሮፓና አሜሪከ ለህክምና ይሄዳሉ፤ ሲፈልጉም ለመዝናናትና ከበሽታቸው ለማገገምም ሊሄዱ ይችላሉ፡፡ እኛ ደግሞ በወባና በርሀብ፣ በስደትና በሙስና እናልቃለን – ሲያስተውሉት ግን በርግጥም ጉደኛ ዘመን ነው እባካችሁን! በነገራችን ላይ ያቺ ዮዲት ጉዲት አዜብ የሚሏት መበለት መቼ ነው የ“ሀዘን” ልብሷን የምታወልቀው? ሀዘኑ ጎዳት አይደል? ቅድም በአንድ ስብሰባ ላይ እኮ ሃሳብ ልትሰጥ ግራ እጇን ስታንከረፍፍ አይቻት ነው – ሳያት ብቻ እንዴት ደሜ እንደሚንተከተክ አትጠይቁኝ፡፡ ባለራዕዩ ሰውዬ በአጽሙ ሀገር መግዛቱን እስኪያቆም ድረስ የምትቀጥል ይመስለኛል፡፡ ሌላውማ ዱሮውንስ ምኑ ቀረባትና! ወይ የሀፍረታችን ምንጭ ብዛት!
ኡክሬን በ3 ወር የሕዝብ አመፅ ድል በድል ሆነች
የምሥራች! ሕዝብ ማለት እንዲህ ነው፡፡ ኡክሬናውያን በሦስት ወር አመፅ በአሥር ዓመት ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ለድል መብቃታቸውን እየሰማን ነው፡፡ እልኸኞችና በጣም ጀግኖች ናቸው፡፡ ካለመስዋዕትነት ድል ባለመኖሩ ወደ መቶ የሚጠጉ ዜጎች(88) በዚህ በሰሞኑ አመፅ ተሰውተዋል፡፡ ጽናት ማለት እንዲህ ነው፡፡ የኛ ግን እንደተጀመረ ሳያልቅ ቁጭ ብሎ አለ፡፡ ግን እሱ ባለው ጊዜ ማለቁ አይቀርም፡፡ ያም ማለቂያ ጊዜ የቀረበ ይመስለኛል፡፡ ግን ግን … በዚህስ ላይ ለብቻው ትንሽ እናውራበት …
አንድ ሕዝብ ለተራዘመ ጭቆና የሚጋለጠው ለምንድን ነው?
በእኔ ዕይታ ሀገር በቀል አምባገነን ገዢዎች በሁለት ይከፈላሉ፡- በመጠኑ ማሰብ የሚችሉ ሀገር ወዳድ አምባገነኖችና ከከርሳቸው ውጪ ጭራሽ ማሰብ የማይችሉ ድፍን ቅል አምባገነኖች፤ (እነዚህኞቹ ከድፍን ቅልነታቸውና ከሆዳምነታቸው በተጨማሪ የውጪ ጠላትን ተልእኮ አንግበው ሀገርን ለማፍረስ የሚጥሩ መሠሪዎች ናቸው)፡፡ ሁለቱን በደርግና በወያኔ ልንመስላቸው እንችላለን፡፡ በጭካኔ ረገድ እምብዝም አይለያዩም፡፡ አንዳቸውን የሌላኛቸው ግልባጭ አድርጎ መውሰድ ይቻላል፡፡ በአገዛዝ ሥልት ግን ሰማይና መሬት ናቸው፡፡ ስለደርግ ማውራቱ ለአሁኑ አይጠቅመንም – በወደቀ ላይ ምሣር ማብዛት ለአሁኑ ችግር መፍትሔ አይሆንም፡፡ ወያኔ ክፉ ሽንት ነው፡፡ ወያኔ የክፉ ሽንት ውላጅ ነው፡፡ ቀደምት ጠላቶቻችን በሃይማኖታችን ሠርገው ገብተው ወሩን ሙሉ በዓል፣ ዓመቱን ሙሉ ፆም አፅዋም አድርገው ለ“ንጉሥ አይከሰስ ሰማይ አይታረስ” ተረት እንደዳረጉንና በማይምነት ጥቁር መጋረጃ ጀቡነው ለማስቀረት እንደሞከሩት ሁሉ ወያኔም በትውልድ ገዳይነቱ የሚታወቀውን የትምህርት ሥርዓት ከዘረጋ ወዲህ እንደከብት ለሆዱ የሚጨነቅ ትውልድ እንጂ ለሀገሩና ለኅሊናዊ ዕድገቱ የሚተጋ ዜጋ ሊፈጠር አልቻለም – በአብዛኛው፡፡ አንድ ሕዝብ ደግሞ በመንፈሣዊ ሕይወቱ ማለትም በአእምሯዊ ዕውቀትና በንቃተ ኅሊና የግንዛቤ ምጥቀቱ ወደፊት ካልተራመደ በስተቀር ከዚህም ባለፈ ቢያንስ የነበረውን እንኳን ጠብቆ መቆየት ካልቻለ ለገዢዎች ምቹ ነው፤ ይህ ዓይነቱ ማኅበረሰባዊ መደላድል እንዲፈጠር ደግሞ ጨቋኞች አጥብቀው ይሠራሉ፤ ከጓደኞቿ ተለይታ የምትወጣ ማሽላ አንድም ለወፍ አንድም ለወንጭፍ ሲሳይ እንደመሆኗ ሀገራቸውን የሚወዱና በትምህርት የላቁ ጥቂት ዜጎች ቢኖሩም አንድም ለሞት አንድም ለእሥራት አንድም ለስደት አንድም ለዕብደትና አሊያም ለአንገት መድፋት እየተጋለጡ ሀገር እንደግመል ሽንት የኋሊት ቀረች፡፡ አምባገነኖች ለኅልውናቸው የሚጠቅሙ ሁሉም የክፋት ሰበዞች እንዲለመልሙ ይጥራሉ፡፡ ከነዚህም አንዱ ዘረኝነት ነው፡፡ ዘረኝነት የማይምነት ውጤት ነው፤ ጦጣ ከጦጣ ጋር፣ ነብር ከነብር ጋር፣ ፍየል ከፍየል ጋር … መስተጋብር መፍጠራቸው ተፈጥሯዊ ነው፡፡ በዚህ ስሌት ሰው ከሰው ጋር ኅብረት መፍጠሩ የሚጠበቅ ነው – አንድ ዘር በመሆኑ፡፡ ነገር ግን ሰው ከሰው ጋር መተባበሩና መፈቃቀዱ ቢከብድ ቢያንስ በጥቁርና በነጭ ወይም በቢጫ፣ በሀገርና በክልል ወይም በአህጉር ደረጃ በሚታዩ ቅርበቶች መተባበር ቢኖር የሚታገሱት መለያየት ነው – ከእንስሳት እንደወረስነው ደመነፍሳዊ መለያየት ቆጥረን ማለት ነው፡፡ ከዚህ አልፎ ግን በኢትዮጵያ እንደምናየው የአንድን ዘር የበላይነት በሌሎች ላይ በግልጥ በሚታይ ተግባራዊነት ዐውጆ መንቀሳቀስ ምን ሊባል እንደሚችል ማሰቡ ራሱ ለራስ ምታት ይዳርጋል፡፡ ይህ ዓይነቱ ነገር ታዲያ የፍጹማዊ ማይምነት ውጤት መሆኑ ሊዘነጋ አይገባውም፡፡ በአንድ ሕዝብ መሀል ጤናማና ተፈጥሯዊ የሚባሉ ልዩነቶች አሉ፤ እነዚያ ጠብና ጭቅጭቅ አያመጡም፡፡ ከመንገድ የወጡ ልዩነቶች መረን በለቀቀ ሁኔታ ከተንሠራፉ ግን የአሁኑን የመሰለ ማኅበራዊ ቀውስ በማስከተል የሕዝብንና የሀገርን ኅልውና ይፈታተናነሉ፡፡ ይቅርታ ሁለተኛ አንቀጽ መድገሜ ነው፡፡
ወያኔ ዘመናዊና ጥራት ያለው ትምህርት በኢትዮጵያ እንዳይኖር የሚጥረው ለምን እንደሆነ እናውቃለን፡፡ በተማረና በሠለጠነ ማኅበረሰብ ውስጥ የወያኔን የመሰሉ ማስጠሎ የመንግሥት ሥርዓቶች ለ23 ዓመታት አይደለም ለአንድ ዓመትም ሊቆዩ አይችሉም፡፡ ጉዳዩ የሕዝብ ብዛት አይደለም፡፡ በአንድ ሰው ወይም በአንድ ቡድን ፍላጎት ለመመራት(ለመገዛት) ምቹ ሆኖ የሚገኝ 85 ሚሊዮን ሕዝብ በአንዲት ቀጭን ለበቅ ወይም በቁጣ ድምፅ ብቻ እንደሚነዳ የሃምሳና ስልሳ ከብቶች መንጋን ያህል አያስቸግርም፤ ይህን ዘግኛኝ ሀገራዊ ገጽታ እውን ለማድረግ ደግሞ የአሁኑ ብቻ ሣይሆን የቀደሙት መንግሥታትም የበኩላቸውን ጥረት አድርገዋል፡፡ ወያኔ በተመቻቸለት ጥርጊያ ዘው ብሎ ድንገት ገባና በማን አባት ገደል ገባ የእረኞች ጥንታዊ የማጣያ ዘዴ በትምህርት ያልገፋውን ሕዝብ በማናቆር መርዘኛ ሥርዓቱን ዘረጋ፡፡ ጨካኝ አምባገነናዊ ሥርዓት በመዘርጋት ረገድ 1.3 ቢሊዮን የሚገመተው የቻይና ሕዝብ ዕጣም ከኛው ተመሳሳይ ነው – በኑሮ ተሽሎ መገኘቱ የነፃነትን ጣዕም እንደሚያጣጥም ሊያስቆጥር አይችልም፤ እርግጥ ነው ቻይናውያን በአምባገነን ቻይናውን እንጂ እንደኛ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በካዱ አጭበርባሪና ህግአልባ ማፊያዎች አይገዙም፡፡ የገዢዎች ዋና የሚጨነቁበት ነገር የአገዛዝ ዘዴን ማወቁ ላይ ነው፡፡ በተለይ ዴሞክራሲ በሌለባቸው ሀገራት መንግሥትና ሕዝብ ማለት ዐይጥና ድመት ማለት ናቸው፡፡ ዐይጦች ከድመት ጥቃት ለማምለጥ ሁልጊዜ ብልህና አስተዋይ መሆን አለባቸው፡፡ ድመት ለዐይጥ ምንም ዓይነት ምሕረት አታደርግም፡፡ ዐይጦች ችሮታና ምሕረትን ከድመት ከጠበቁ የዋህነት ነው፤ የብዛት ጉዳይ ከቁብ ሳይጣፍ፡፡ ድመት በሕይወት የያዘቻትን ዐይጥ ዐይኗን አጥፍታ እንዴት እንደምትጫወትባት አስታውሱ፤ ወያኔም ተቃዋሚዎችን በአጠገቡ አስቀምጦ በቅርብ እየተቆጣጠረ እንዴት እንደሚጫወትባቸውና በሀገሪቱ ዴሞክራሲ ያለ ለማስመሰልም እንዴት እንደሚጠቀምባቸው ልብ በሉ፡፡ በውጪ ያሉትንም ሰው እያሠረገ ሲቻል ለማጥፋት ሳይቻል ለመከፋፈልና ለማዳከም፣ የሕዝብ አለኝታና የብሶት መተንፈሻ የሆነውን ኢሳትንም ለማዘጋት የሚያደርገውን ጥረት ሁሉ አትርሱ፤ እንዳሻው ከሚፈነጭበት የሕዝብ ጫንቃ ላይ ሊያወርደው የሚሞክርን ኃይል ሁሉ ባለ በሌለ ዘዴና ጉልበት ማጥፋት የወያኔ ትልቁ ሥራ ነው – ሌላው ሁሉ ሁለተኛና ሦስተኛ ከፈለገም መቶኛ ነው፡፡ ከጭቆና ለመውጣት ሆ ብሎ የሚነሣ በአግባቡ የተማረና የሠለጠነ፣ ከአጉል ባህልና ከጎጂ ልማድ ነጻ የወጣ፣ ቀናነትን መከባበርንና ትህትናን የተላበሰ፣ በእውነተኛ የሃይማኖት አባቶች የሚመራ፣ ዘረኝነትንና አድልዖዊነትን የሚጠየፍ ማኅበረሰብ መፍጠር ከተቻለ ነጻነትና ዴሞክራሲ ለነዚህ ነገሮች እንደምርቃት ያህል በተፈጥሯቸው ወደሕዝባችን የኅሊናና የፖለቲካዎች ጓዳ የሚገቡ እንጂ ብዙ ትግልን የሚጠይቁ አይሆኑም፡፡ መማርና መሰልጠን ሲባል ደግሞ ለአንድ ወገን ብቻ የሚተው ሣይሆን ለሁሉም ነው፡፡ ሕዝቡ ዘመናዊ ከሆነ አመራሩም ዘመናዊ የመሆን ዕድሉ ከፍተኛ ነው – ያልዘሩት አይበቅልምና አሁን ሥልጣን ላይ ያለው ኃይል አብዛኞቻችንን እንደሚመስል ወይም እንደማይመስል ለማወቅ ትንሽ ራሳችንን የመፈተሸ ሥራ ማካሄድ ሳይኖርብን የሚቀር አይመስለኝም፡፡ አንድ ሕዝብ ከሚገባው በላይ ወይም በታች መሪ አያገኝም የሚባለውን ነባር አባባል መመርመርና ራሳችንን ከዚህ ነጥብ አኳያ ማስተካከል ይኖርብናል፡፡ እኛ ጥሩ ስንሆን ጥሩ መሪ ይኖረናል፤ እኛ መጥፎ ስንሆን ደግሞ መጥፎ መሪ ይገጥመናል፡፡ ፈረንጆቹ “what goes around comes around” የሚሉት “ሆድን በጎመን ቢደልሉት ጉልበት በዳገት ይለግማል” ወይንም “አለባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ” ለማለት ፈልገው ይመስለኛል፡፡ አዎ፣ እኛን እላይ ለማየት ከፈለግን የላዩን ወደኛው አምጥተን ከታችኛው ጋር ማስተያየትና ልዩነታችንን መገንዘብ ይጠበቅብናል፡፡ የላይኛው ከታች እንጂ ከላየ-ላይኛው ጽርሃ አርያም እንደማይወርድ ማወቅ አለብን፤ አራት ኪሎ የምትገቡት በሁኔታዎች አስገዳጅነትም በሉት በሌላ አንተና እርሷ ወይም እገሌና እንቶኔ እንጂ ከጨረቃ ወይም ከማርስ አዲስ ትውልድ ተፈጥሮ አይደለም…፡፡ ባልተማረ ሕዝብ ውስጥ አጋጣሚን እየተጠቀመ ወደሥልጣን የሚወጣው በአብዛኛው ብዙም ያልተማረው ቀጣፊና መልቲው ነው – ይህን ለብዙ ጊዜ አይተን በተግባር አረጋግጠናል፡፡ የቅርቦቹ ተፈሪ መኮንን፣ መንግሥቱ ኃ/ማርያምና ለገሠ ዜናዊ ዲ ኤን ኤያቸው ቢጠና ከሌላው ሕዝብ የሚለዩት የሚቃወሟቸውን ቀድመው በማጥፋት ድፍረትና ጭካኔ የተሞላበት አፋጣኝ እርምጃ በመውሰዳቸው እንዲሁም በሥልጣን ሽሚያ የሚጠረጥሯቸውን ጓደኞቻቸውንና የቤተሰባቸውን አባላት ሳይቀር ከጉያቸው እያወጡ እንደሰውነት ተባይ በጣቶቻቸው በመጨፍለቅ ምንም ዓይነት ሥጋት እንዳይኖርባቸው በማድረጋቸው እንጂ የክሮሞዞማቸው ቁጥር ከእኔና ከአንተ በልጦ ወይም በኢትዮጵያዊነታቸው እነሱ ተሽለው አይደለም፡፡ ይህን የአጭበርባሪዎች መንገድ እስከወዲያኛው የምንዘጋው ታዲያ ብዙው ዜጋ ሲማርና ሲሰለጥን በዚያም ምክንያት እውነተኛ ዴሞክራሲን ለይምሰልና ለታይታ ሳይሆን በማወቅና በሃቅስናሰፍን ነው፡፡ መንገድና ሕንጻ ደግሞ የጥቂቶችን ኢኮኖሚያዊ ብልጽግና እንጂ የብዙኃንን ሁለንተናዊ ዕድገትና ልማት የሚያንጸባርቅ ሊሆን እንደማይችል ተደጋግሞ ተነግሯል፡፡ ስለዚህ ራስን በትምህርትና በዕውቀት እንዲሁም በቀና አመለካከትና አስተሳሰብ ለመገንባት ዘወትር መጣር ይኖርብናል ማለት ነው፤ ከልጆች አስተዳደግና ከቤተሰብ አያያዝ ጀምሮ ብዙ ይጠበቅብናል፡፡ ሕዝቡ ጠሊቅ እንቅልፍ ውስጥ ገብቶ በ“አንተ ታውቃለህ” ብቻ፣ በ“ከዚህ ይብስ አታምጣ” ብቻ፣ በ“ሺም ታለበ መቶ ያው በገሌ” ብቻ … ተወስኖ የሚኖር ከሆነ የጥቂቶች መፍጨርጨር ብቻውን የትም አያደርስም፡፡ ሊያውም ከጥቂቶቹም ውስጥ ብዙዎቹ ድብቅ አጀንዳቸው ለግል ጥቅምና ፍላጎት መሆኑን መገመት አስቸጋሪ ባልሆነበት ሁኔታ፡፡ አንድ ጠብሰቅ ያለ አንቀጽ መሰለሴ ነው፡፡
ማኅበረሰባችን አሁን የሚገኝበትን ቅርጽ ማሰቡ ሊያደክም ይችላል፡፡ አእምሮን ያናውዛል፡፡ ቲቪም ተመልከት፤ ሬዲዮም አዳምጥ፤ ከሰው ጋርም አውራ – ከማንም ጋር ተነጋገር ደርዝ ያለው ነገርና የትምህርትን ውለታ የሚያስታውስ አንድም ነገር ማግኘት እየከበደ ነው፤ አብዛኛው ወሬ ስፖርት፣ ተራ አሉቧልታና ወሲብ ነው፡፡ ጭንቅላትን በሚያፈነዱ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ችግሮች በተወጠረች ሀገር ውስጥ እንደደላው ሰው ሚዲያውና የሰዎች ትኩረት ሁሉ ይበልጡን በትርኪ ምርኪ ነገሮች ተጣብቦ ስታይ የት ነው ያለሁት ትላለህ – እርግጥ ነው ብዙ የጊዜው ሰዎች ጠግበዋልና ለነሱ ዘመኑ ሠርግና ምላሽ ነው፤ ከተሞችንና መዝናኛ ሥፍራዎችን በሞላ ተቆጣጥረዋል፡፡ የብዙዎች መዘናጋት የሚያሳየው ግን አንድም አፈናው በማያፈናፍን ሁኔታ ተባብሶ አፋችንን ሙሉ በሙሉ አዘግቶናል ወይም ሰው ችግሩን ትቶ በዋዛ በፈዛዛ ጊዜውን ለማሳለፍ ወስኗል ማለት ነው፤ ብቻ ሁኔታው በእጅጉ አሳሳቢ ነው፡፡ በዚህ መሀል ኃይለመድኅንን የመሰሉ ጀግኖችን በድንገት ማግኘቱ አጥንትን ዘልቆ የሚያለመልም ተስፋን ማጫሩ በጄ እንጂ ሁኔታዎች አስከፊ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡ የሀብት ክፍፍሉን ስናይ፣ በቃላት ለመግለጽ የሚከብደውን የኑሮ ውድነት ስንታዘብ፣ በዘረኝነት ላይ የተመሠረተውን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ወታደራዊና ሃይማኖታዊ መዋቅር ስንመለከት፣ የሕዝቡን የንቃተ ኅሊና ደረጃ ስንቃኝ፣ የምሁራንንና የልሂቃንን ዝምታና እረጭታ ስናስብ፣ የወያኔ ፖለቲከኞችን የልብ ድንዳኔና ጭካኔ ስንመለከት፣ የሙስናውን መስፋፋትና የንግዱን መረን ማጣት ስናይ፣ የባለሥልጣናትን ማይምነትና የአስተዳደር ችሎታ ማነስ ስንታዘብ፣ የድህነትን መክፋት ስናስብ፣ የርሀብተኛውን ቁጥር ስናይ፣ በኑሮ ጣጣ ምክንያት በሀሽሽ፣ በመጠጥና በነገር ሰክሮና አብዶ ብቻውን እያወራ የሚሄደውን ዜጋ ስናስብ፣  … እኛንም ዕበዱ ዕበዱ የሚል መጥፎ መንፈስ ሊወርረን ይችላል፡፡ … በነጋዴዎችና ባለሥልጣናት የሙስና ትስስር ከቆዳችን አልፎ ዐፅማችን እንዴት እንደሚገሸለጥ አንድ ምሳሌ ልናገርና ላብቃ፡፡ በነገራችን ላይ የኔ የ4 ሺህ ብር የተጣራ ደሞዝ ቤተሰቤን ማስተዳደር ካቆመ ቆይቷል – ታዲያ እንዴት ትኖራለህ ካላችሁ መልሴ፣ ዘፋኙ “እኔስ እንደምንም … ሰው አልችል አይልም…” እያለ እንዳቀነቀነው እንደሰው ‹ባጀት በማጠፍ›ና ብዙ ነገሮችን አስቦ በመተው ብቻ ነው (ለምሳሌ ሥጋን፣ ወተትን፣ ቅቤን፣ ነጭ ጤፍን፣ ህክምናን፣ መዝናናትን …. ከዝርዝርህ ታወጣና ወይም እንደመስቀል ወፍ በተወሰነ ጊዜ ‹ታያቸውና› መኖር ተብሎ ትኖራለህ – ከዚያም እንደሰው ተፈጥረህ ስታበቃ እንደበግ ኖረህ ትሞታለህ፤ ሞትህም ተብሎ ወግ አይቀርም ዘመድ አዝማድና ጓደኛ እንደነገሩ ያለቅስልሃል ወንድሜ – እንጂ የሉካንዳ ቤት መስኮት ላይ መቆም አይደለም በዚያ በኩል ማለፍም የሞራል ብቃት ላይኖርህ ይችላል – ሕዝቡ እኮ በቁሙ ሞቷል ማለት ይቻላል፤ አብዛኛው ዜጋ የሚኖረው በተዓምርና በምትሃት ይመስላል፡፡ ምናለ በሉኝ ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ ሥጋ ቤቶች ሥጋቸውን በነጭ ሱቲ ይሸፍኑና ለማየት ብቻ ሳያስከፍሉን የሚቀሩ አይመስለኝም፤ ለዚያስ አያድርሰኝ)፡፡ የኔ ደሞዝ እኔንና ቤተሰቤን በቅጡ ማኖር ካቆመ ከኔ አምስትና ስድስት እጅ ወደታች የሚገኙ ዜጎች አሁን በሚከፈላቸው በዱሮው ገንዘብ ሥሌት በሣንቲም ደረጃ የሚገመት ደሞዝ እንዴት እንደሚያኖራቸው ይታሰባችሁ፡፡ ማሰብ ደግሞ “እኔ እንትናን ብሆን” ብሎ እንጂ ለራስና ስለራስ ብቻ መሆን የለበትም፡፡ የአርባ ብር የዱሮ ደሞዝ ምን የመሰለ ቪላ ቤት ያሠራ ነበር – ሊያውም ፉሪና ሱሉልታ ሳይሆን አዲስ አበባ መሀል ከተማ፡፡ አርባ ብር አሁን በአንድ ተራ ቡና ቤት ልሙጥ ሽሮ ቢያበላ ነው፡፡ ለአንድ ተራ የሀብታም ነጋዴ ቤት ሊቀረጽ የማይችል የበር ቁልፍ ለመግዛት የኔን ደሞዝ እንደሚፈጅ ሰምቻለሁ – አራት ሺ ብር! ምሳሌ ሆቴል በሚባለው አንዱን ቤቱን ለግርማ ወ/ጊዮርጊስ መኖሪያ በመቶ ሺዎች ብር ለመንግሥት ያከራየው ወያኔ ሰውዬ ሁቴል ቤት ብትገቡ አንድ ክትፎ ብር አራት መቶ ብር ነው አሉ፡፡ እኔ በዚያ ቤት ውስጥ የወር ደሞዜን እንዳለ ባወጣት አሥር ጊዜ ክትፎ መብላት እችላለሁ ማለት ነው፡፡ … ወደምሳሌየ ልሂድ መሰለኝ፡- አንድ የአምስተኛ ክፍል ምሩቅ ነጋዴ ነው፡፡ ዕድሜው ወደሃያዎቹ እኩሌታ ነው፡፡ የሠራው ቤትና ያገባት ምሽት ሌላ ናቸው፡፡ መኪናውን አታንሱት፤ ግራ እጁ ላይ ያለው የውሻ ሰንሰለት እሚያህል የወርቅ ካቴናም እንዲሁ አይነሳ፡፡ በአንድ ጉዳይ ተገናኘንና ሊጋብዘኝ ሆነ – አፈኛ ሰው አንዳንዴ ጋባዥ አያጣም መቼም፡፡ “የሆድ ምቀኛው አፍ ነው” እንደሚባለው ግብዣን ከልክዬ ሆዴ እንዳይቀየመኝ የማላደርገው ጥረት የለምና በደስታ እሺ አልኩ፡፡ አምስት ሰዎች ሆነን ወደርሱ ምርጫ ምግብ ቤት አመራን፡፡ ምን አለፋችሁ – ለኔ ብቻ የወጣውን ሳሰላው ብር 350 ነው – አንድ ኪሎ የፍየል ጥብስና አንድ ጠርሙስ ከግማሽ ጠጅ፡፡ ጠጁ ደግሞ አሁን በብጥሌ ብርሌ ስድስት ብር የሚሸጠው ነፍሱን ይማርና የቤተ መንግሥቱ የጋሽ ድጋፌ ጠጅ እንዳይመስላችሁ – በሊትር መቶ ብር ነው፤ አለፈልኝ ነው እምልሽ የኔ እህት፡፡ የገረመኝ ለግብዣው ያን ያህል ገንዘብ መውጣቱ ወይም እኔ ሠርቼ እየገባሁ የበይ ተመልካች መሆኔ አይደለም፡፡ ያ ወጣት ልጅ ሀሁን ሳያውቅ በሸውራራ የንግድ አሠራር በሚያገኘው ገቢ በወር ከ75 ሺህ ብር በላይ ዕቁብ ይጥላል፡፡ ምቀኝነት የተጠናወተኝ እንዳይመስላችሁ – በፍጹም፡፡ ግን የሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ አካሄድ ወደገደል እየወሰደን መሆኑን ለማሰገንዘብ ያህል ነው፡፡ ለነገሩ ሚስቱ ሦስተኛውን ልጅ ስለወለደችለት ከአልማዝ ጌጥ በተጓዳኝ የ2.5 ሚሊዮን ብር መኪና ገዝቶ በጦፈ ግብዣ ላይ የሸለመ ወያኔ መኖሩንስ ከፋክት መጽሔት አንብቤ የለምን? እንዲህ ዓይነት ነጋዴዎችን አንቀባርሮ የሚያኖረው ደሞዜ ለኔ ባይተርፈኝ ታዲያ ይፈረድበታል ምዕመናን? የሰው ልጅ ግብዝነት ግን ይገርመኛል – በዚህ ዓይነት የውሻቸውን ልደት የሚያከብሩ ከውሻቸው የማይሻል ጭንቅላት ያላቸው ሀብታሞችም እኮ ይኖሩ ይሆናል፡፡ ወይ ሰው ሆኖ የመፈጠር አበሳ! ግን ግን ይህች ሀገር የማን ናት? መንግሥትን ደጀን ያደረጉ ሌባ ነጋዴዎችና ሙሰኛ ባለሥልጣናት እየተመሳጠሩ እስከመቼ ነው በተለይ የተቀጣሪ ሠራተኛውን ኑሮ መቀመቅ እንዳወረዱት የሚቆዩት? እኛስ ወግ ደርሶን ከአኗኗሪነት ወጥተን ማለፊያ ሕይወት የምንመራው መቼ ነው?  እነሱ አንገት ካጡ መብታችንን ማስከበር የምንችልበት መንገድ የለም ወይ? (በነገራችን ላይ በመንግሥት ትምህርት ቤቶች ከሚማሩ ተማሪዎች ከፊሉ ምሣ እንደማይዙ፣ ከነዚሁ ከፊሎች ውስጥ ግማሾቹ በቀን አንዴ እንኳን የረባ ነገር እንደማይመገቡና ከነዚህ ግማሾች ውስጥ ብዙዎቹ ከምግብ ዕጥረት የተነሣ በየክፍላቸው ‹ፌንት› እያደረጉ እንደሚወድቁ የሰማችሁ ይመስለኛል፡፡ ሌላ ሌላውን ቅንጦት እርሱትና በልብስ ረገድ እንኳን በውድ ዋጋ ከስንት አንዴ የምትገዛ ሞተ ከዳ (ልባሽ ጨርቅ) እየተጣጣፈችና መልኳን ከአንዴም ሁለት ሦስቴ እየቀየረች ለበርካታ ዓመታት ትለበሳለች፡፡ ባይገርማችሁ ስገዛት ቢጫ የነበረች አንዲት ጃኬቴ መጀመሪያ ወደቀይነት ከዚያም ወደ አረንጓዴነት አሁን በማብቂያው ደግሞ ወደአመዳምነት ተለውጣለች፤ ሁሉንም ቀለሞች ታዳርስ እንደሆነ ጉዷን አያለሁ በሚል ከመኝታ ሰዓት ውጪ አዘውትሬ በመልበስ  መጨረሻዋን በጉጉት እየተጠባበቅሁ ነው – በእግረ መንገዱም ጓደኞቼ ከሩቅም ሆነ ከቅርብ፣ ከፊት ለፊትም ሆነ ከበስተጀርባ እኔን በአሻጋሪ አይተው በጃኬቴ ለመለየት አይቸገሩም፡፡) ነገ ሩቅ ይመስላል፤ መምጣቱ ግን አይቀርም፡፡ ትንሽ ዕውቀት መጥፎ መሆኑን ከልብ እረዳለሁ፤ ስለዚህም ለእኔ እውነት በመሰለኝና ባመንኩበት ነገር ብዙም ባልተለመደ ግልጽነት “በዘባረቅኋቸው” የግል አስተያየቶቼ የተነሣ ያስቀየምኳችሁ ብትኖሩ በኅያው እግዚአብሔር ስም ይቅር እንድትሉኝ እለምናለሁ፡፡ ሚዲያዎች ጥናቱን ይስጣችሁ – እኔስ ተወረድኩት፡፡
መውጫ፡-  
“ሥጋን ከመግደል አልፈው ነፍስን መግደል የማይችሉትን ሰዎች አትፍሩ፤ ይልቁንስ ነፍስንና ሥጋን በገሃነም  ሊያጠፋ የሚችለውን አምላክ ፍሩ፡፡” ማቴ. 10፣ 28
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ፡፡ የነጻነቷን ትንሣኤም በቅርብ ያሳየን፡፡
(ዕለተ የካቲት ገብርኤል 2006ዓ.ም፤ ከሌሊቱ 9፡00 ሰዓት ላይ ተጽፎ አለቀ)

No comments:

Post a Comment