Translate

Monday, October 21, 2013

የአስተሳሰብን ህግ ካልጠበቅን ለመግባባት ያቅተናል!!! ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም

ለብዙ ዓመታት የማውቀው ወዳጄ ገብሩ ታረቀኝ በፍትህ ጋዜጣ ላይ፣ የማላውቀው አቶ ዓሥራት በአድማስ ጋዜጣ ላይ በትግሬነታቸው ተቆርቁረውና እኔን ባዕድ አድርገው የጻፉትን አንብቤ ሁላችንንም የሚያውቁ ሌሎች ሰዎች አስተያየት እንዲሰጡበት በማለት መልስ ከመስጠት ተቆጥቤ ቆየሁ፤ ሆኖም እስካሁን ከአንድ ሰው በቀር የደረሰልኝ የለም፤ ስለዚህ እኔው ልጋፈጠው፡፡
 ገብሩ ወዳጄ ነው የምለው ሰው ስለሆነ የጋለ ስሜቱን ይዞ አደባባይ ከመውጣቱ በፊት ከእኔ ጋር ጉዳዩን አንስቶ አለመወያየቱ ከሚችለው በላይ የሆነ ግፊት ቢያጋጥመው መስሎ ታየኝ፤ እንዲያውም ሌላ ሰው እሱ ያለውን ሲናገር ቢሰማ ለእኔ ቆሞ ይከራከራል ብዬ የምገምተው ሰው ነበር፤ አንድ ሳይካያትሪስት (የአእምሮ ሐኪም) ሲናገር እንደሰማሁት የጎሳ አስተሳሰብ የጎሳን ድንበር ጥሶ ወዳጅነት የሚባል ነገር አያውቅም ያለውን አስታወሰኝ፤ ይህ እንደማይሆን ተስፋ አለኝ፡፡
በምን ላይ እንደጻፍሁት ሳልናገር ለሁለቱም የትግራይ ተቆርቋሪዎች የሚከተሉትን አጫጭር ነጥቦች ላመልክታቸው፡-
1. ወያኔ ..ከሚኒልክ በፊት ኢትዮጵያ አገር አልነበረችም ሲል የአፄ ዮሐንስንና የራስ አሉላን ትግሬነትና ኢትዮጵያዊነት በመካድ.. ጀመረ፤
2… የጎንደርን በሬ፣ የጎጃምን በሬ፣ የሸዋንም በሬ፣
ባንድ አርጎ ጠመደው የትግሬው ገበሬ..
(የትግራይን የኢትዮጵያዊነት መሰረት ለማስረዳት የጠቀስሁት)
3. ..የትግሬ ዘር (ኤርትራውያንን ጨምሮ) የኢትዮጵያ መሰረት ነው፤ የትግሬ ዘር የኢትዮጵያን ታሪክ ተሸካሚ ነው፤ እንኳን በኢትዮጵያዊነታቸው ያሉትን ትግሬዎች የተገነጠሉትንም ለማጥፋት ማሰብ በምድርም በሰማይም ይቅርታ የማያስገኝ ወንጀል ነው፡፡ ከኤርትራውያን ጋር የተደረገውንም የወንድማማቾች ጦርነት አጥብቄ የተቃወምሁት በዚህ ምክንያት ነበር፤ በሰሜን ያሉትን ወንድሞቻችንንና እህቶቻችንን ከመቅጽበት ወደባዕድነት ለውጠን አሁን ደግሞ የተረፍነውን አጥፊና ጠፊ አድርጎ መፈረጁ ለማንም የሚበጅ አይሆንም፡፡..
ብዙ ሌሎችንም መጥቀስ እችላለሁ፤ ልብ ላለው ይበቃል፡፡
በደርግ ዘመን በዩኒቨርስቲ ውስጥ ስናወራ ስለ የአእምሮ ወዝ-አደር ስናገር አንዱ ካድሬ የአእምሮ ወዘ-አደር የሚባል ነገር የለም ብሎ ተቆጣ፤ አብረውን የነበሩት ሁሉ በስምንት ተኩል እኔ ቢሮ እንዲመጡ ጋበዝሁና መጽሐፉን ይዤ መጣሁና ለካድሬው አሳየሁት፤ በሌላ ጊዜ ደግሞ ሌኒን ተናዶ በደርዘን የሚቆጠሩ ካድሬዎችን በአንድ ትጉህና ታታሪ ባለሙያ የሚለውጠኝ ባገኘሁ ብሏል ስል ያው የማይማር ካድሬ ተቆጣና ..አይወጣውም…. አለ፤ መቶ ብር ከኪሴ አወጣሁና አንድ ጊዜ በነፃ አስተምሬሃለሁ፤ አሁን ግን መክፈል አለብህ፤ የሌኒንን ጽሑፍ ካላመጣሁልህ መቶ ብር ታገኛለህ፤ ካመጣሁ ግን መቶ ብር ትከፍላለህ ብለው አሻፈረኝ ብሎ በስሀተቱ ጸና፤ አቶ ዓሥራት ብዙውን ጽሑፎቾን አንብቤአለሁ ሲል እውነት እንዳልሆነ ስለማውቅ ውርርድ ላቀርብለት ፈልጌ ነበር፤ ስለአማራ የተናገረው እኔ የጻፍሁትን እንዳላነበበ ጥሩ ማስረጃ ነው፤ ሳያውቁ በእርግጠኛነት አዋቂ መስለው ለሚቀርቡ ቀላሉ መንገድ በአደባባይ ውርርድ ነው፤ ገብሩ ታረቀ እንኳን በአሜሪካ የፈረንጅ ልጆች ሲያስተምር ስለኖረ በአገር ውስጥ የተጻፈውን ሁሉ ማንበቡ አጠራጣሪ ነው፡፡
ለነገብሩና ለነዓሥራት ትልቁ ፍሬ ነገርና ቁም-ነገር ትግሬነታቸውን ለብቻቸው የያዙት መስሎአቸው ነው፤ በትግሬነታቸው ውስጥ አነሱንና እኔን የሚያያይዙ ብዙ ከባድ ሰንሰለቶች መኖራቸውን አያውቁም፤ ለነሱ ትግሬ ከትግሬነት ሌላ ፋይዳ ወይም ትርጉም የለውም፤ እንደዚህ ያለ ክርክር መነሳቱ ኢትዮጵያዊነት ምን ያህል እንደላላ የሚያመለክት ነው፡፡
..ማወቅ ወደ እርግጠኛነት የሚያመራው በመጠራጠርና በመጠየቅ ነው፤ አለማወቅ ግን ምንጊዜም ወደጠን ካራ የጨለማ እርግጠኛነት የሚመራ ነው፤ አለማወቅ ከኃይል ጋር ሲጋባ የአምላክን ቦታ ይይዝና እስመ አልቦ ዘይሰአኖ ይሆናል፡፡..
ሁለቱም ሰዎች፣ ፕሮፌሰር ገብሩም አቶ ዓሥራትም ባሳዩዋቸው ሁለት የእውቀት ጉድለቶች ልጀምር፤ ይህንን ማድረጉ አያስደስተኝም፤ ነገር ግን አለማወቅን ወደ እውቀት እየለወጡ ሰዎችን ማሳሳቱ፣ ከዚያም አልፎ በትግራይ ማህበረሰብ ላይ አውቀውም ይሁን ሳያውቁ የጥላቻ መርዝን ለመንዛት የሚደረገውን ሙከራ አገርን የሚጎዳ ነውና ሊታለፍ አይገባም፤ ፕ/ር ገብሩም አቶ ዓሥራትም በሂሳብ ትምህርታቸው ስለ Set theory ትንሽ ቢያውቁ ..የኤርትራና የትግራይ ዜጎች..ያልሁት ደማቸውን አያፈላውም ነበር.. ትግራይ በኢትዮጵያ ውስጥ፣ ኢትዮጵያ በትግራይ ውስጥ ይገኛሉ፤ የኔ ስህተት የአንባቢዎችን ደረጃ ከፍ አድርጌ መመደቤ ነው፡፡
ሌላው የእውቀት ልዩነት ሰው የመሆን ግንዛቤያችን ነው፤ ለእኔ ሰው በቁና የሚሰፈር፣ ወይም በከረጢት የሚታሰር አይደለም፤ እያንዳንዱ ሰው በነጠላ ለራሱ ስራ ኃላፊነቱን ይወስዳል፤ እንኳን በ2004ዓ.ም ጥንትም ቢሆን ጽድቅም ሆነ ኩነኔ የግል ነው፤ በጎሳ ወይም በጅምላ አይመጣም፤ የሰው ልጅ እንደ አይጥና እንደድመት አይደለም፤ እንኳን አብሮ የኖረና የተዛመደ፣ አንዱ ለሌላው የመጨረሻ መስዋዕትነት የከፈለ ቀርቶ እንግዳም ቢሆን አንዱ ለሌላው መሰረታዊ ጠላትነት የለውም፤ ፕ/ር ገብሩና አቶ ዓሥራት እንጀራቸውን ለማብሰል ለትግሬዎች ዘብ የቆሙ መስለው ባልገባቸው ነገር ሁሉ ደማቸውን ያገነፈሉት እኔን ባዕድ በማድረግ ለመጠቀም ነው፤ ለእነሱ አዝናለሁ፤ የትግራይ ህዝብ እኔን በነሱ ዓይን እንደማያየኝ አምናለሁ፡፡
ፕ/ር ገብሩ ..እኔም እንደአስገዶም ገ/ስላሴ የወዲያ ማዶ ልጅ ነኝ.. ይላል፤ ወዲያ ማዶ ስል ትግራይ ማለቴን ማን ነገረው? ስብሐት ነጋን ወዲህ ማዶ ሳደርገው በገብሩ ግንዛቤ ትግሬ አይደለም ማለቴ ነው መሰለኝ.. ገብሩን ወዴት ከፍ ከፍ እለዋለሁ.. ገብሩ የወዲያም የወዲህም ልጅ አይደለም፤ የባህር ማዶ ልጅ ነው..
ሁለተኛ ስለኤርትራውያን የተናገረው መልካም ስሜቱን ከመግለጽ በቀር መጽሐፉን ቢያነብበው ኤርትራውያን በስሜት ሳይሆን በተግባር እሱ ..እስረኞች.. ያላቸው ሰዎች የገለጹትን እውነት ያስተባብለዋል፤ በተጨማሪም ለታሪክ ባለሙያው መንገር ካልሆነብኝ የሠርጸ ድንግልን ዜና መዋዕል ቢያነበው ከወራሪ መከላከል እንደሚችሉ ሊገነዘብ ይችላል፡፡
ሶስተኛ፣ ..የሞራል ሉዓላዊነት.. በአማርኛም ሆነ በእንግሊዝኛ አልገባኝም፤ አላግባብ ተሰካክቶ የተደነቀረ ነገር ነው፡፡
አራተኛ፣ ለኢጣልያ ገብረው የጠላት ወታደር በመሆን ወገናቸውን የወጉት ኤርትራውያን እጅና እግር መቆረጡ በአሁኑ ጊዜ ላለነው የሚዘገንን ነው፤ ነገር ግን ፕ/ር ገብሩ በዓድዋ ጦርነት በምኒሊክ አገዛዝ የተደረገውን ሲናገር በቅርቡ በማይጨው የደጃዝማች ኃ/ስላሴ ጉግሳን ሆነ በሌላ የተፈፀመን ቅጣት አለማንሳቱ፤ በአገራችንም ቢሆን የአፄ ቴዎድሮስን አልሰማም ይሆን? የአጼ ዮሐንስንስ አልሰማም ይሆን? ወይስ እኔ እንዳነሳለት ፈልጎ ይሆን? አንዳንድ ነገሮችን እየነቀሱ በማውጣት ታሪክ እንደማይጻፍ ለፕ/ር ገብሩ መንገር አያስፈልግም፤ የምኒልክን ሀጢአት ለማበራከት ከሆነ ከሸዋ ሳይወጣ በጧፍ ያነደዱትን ሊጨምርበት ይችላል፡፡
አሁን ከባድ ወደሚመስሉኝ ነጥቦች ልምጣ፤ ለእኔ እንደሚገባኝ ታሪክ ሁነትን በመግለጽ ይጀምራል፤ በትክክል ለተመዘገበው ሁነት ፍቺ መስጠት፣ ወይም ጥሩና መጥፎነቱን በመግለጽ ፍርድ መስጠት በኋላ የሚመጣ ነው፤ በሌላ አነጋገር ፍርድ ሁነትን ተከትሎ ይመጣል እንጂ የሁነቱ ፍቺ ወይም በሁነቱ ላይ የሚሰጠው ፍርድ አይቀድምም፤ ይህ ከሆነ ፈረንጆች እንደሚሉት ፈረሱን በጋሪው ለመጎተት እንደመሞከር ይሆናል፤ አጉል ድካም ነው፤ አንድ ጊዜ ብቻ አይደለም፤ ለሁለት ጊዜ ገብሩ ለማድረግ የሚፈልገው ይህንን ነው፤ ምን እንደተናገርሁ ለአንባቢው ሳይነግር፣ በራሱ ግምት የተናገርሁ ለመሰለው ነገር ፍቺና ፍርዱን መስጠት ይጀምራል፤ ይህ የእውቀትና የእውነት ፈላጊ ምሁር የአጻጻፍ ስርዓት አይደለም፤ በዚህ ጉዳይ አቶ ዓሥራት እኔ ያልሁትን በትክክል ጠቅሶ ወደራሱ አስተያየት ይሻገራል፤ ይህ ተገቢ ነው፡፡
ገብሩ ግን ..ኢትዮጵያዊ ዜግነትን በትግራይ ዜግነት መተካትዎ ምን ቢያስቡ ነው?.. ይለኛል፤ መጀመሪያ በዚህ ጉዳይ ላይ እኔ ምን እንደተናገርሁ አይገልጽም፤ የተገነጠለውን ኤርትራን ይገድፍና ዘልሎ ትግራይን ለማስገንጠል የፈለግሁ ለማስመሰል ..ምን ቢያስቡ ነው?.. ይለኛል.. ኤርትራን የጨመረ እንደሆነ ተንኮሉ ይበላሻል.. ለኢትዮጵያውያን ነግሮ ሊያስወነጅለኝ ፈልጎ ነው? ወይስ ለአስገንጣዮቹ ነግሮ ሊያስሸልመኝ.. ለተገንጣዮቹና ለአስገንጣዮቹ በስሜት ማንኛችን እንቀርባለን?
ከላይ እንደጠቀስሁት በሂሳብ ወይም በፍልስፍና ንባብ ቢደገፍ እዚህ ስህተት ላይ አይወድቅም ነበር፤ ..ምን አስበህ ነው?.. የሚለው ለመወንጀልና ለማስወንጀል የተቃጣ ለማንም ግልጽ የሆነ ንጹህ ተንኮል ነው፤ ከኢትዮጵያ ዜግነት የተለየ የትግራይ ዜግነት መኖሩን ሊነግረኝ ያሰበ ይመስላል፤ እንዲህ ያለ መያዣና መጨበጫ የሌለው ነገር እኔ አልተናገርሁም፤ በ1998 ጓደኞቼና እኔ ከተከሰስንበት አንዱ የትግሬን ዘር ለማጥፋት መሞከር የሚል ለጆሮም የሚቀፍ ነገር ነበር፤ በ1998 ፍርድ ቤት በቀረብንበት ጊዜ የዛሬው የገብሩ ጽሑፍ ቢገኝ ትልቅ ማስረጃ ሆኖ ይቀርብ ነበር፤ እግዚአብሔር ሲያወጣን ገብሩ በዚያን ጊዜ ከእኛ ጣጣ ተከልሎ በአሜሪካው ነበር፤ ዛሬም 1998 እየሸተተ ነውና ገብሩ ስራ አያጣም፡፡
አንድ የታሪክ ባለሙያ ፕ/ር ትናንት በጋዜጣ የተጻፈውን በትክክል መድገም ሲሳነው ከአስር፣ ከሃምሳ፣ ከመቶ ወይም ከዚያ በላይ የቆዩ ጉዳዮችን እንዴት አስታውሶ እውነቱን ሊናገር ነው? እኔ የጻፍሁትን እሱ በመሰለው ተርጉሞ ከአገርና ከዘመድ ጋር የሚያጣላ ከባድ ነገር ሲለጥፍብኝ በጣም ያሳዝናል፤ መቼም ኢትዮጵያ ሆነና ነው እንጂ በሌላ አገር ቢሆን የጋዜጣው አዘጋጅ ያልተባለ ነገር ተቀብሎ አያሳትመውም ነበር፤ ከዚያም በላይ ገብሩና እኔ ስለምንተዋወቅ እሱ የጻፈውን ሌላ ሰው ቢጽፈው ገብሩ ይቃወማል ብዬ ሙሉ እምነት ነበረኝ፤ እንዲህ ዓይነት ጭራሽ ትርጉም የሌለው ነገር እኔ አልወጣኝም፤ ከኢትዮጵያ የተለየ የትግራይ ዜግነት የሚባል ነገር መኖሩንም አላውቅም፤ ዜግነት ምን እንደሆነና ከጎሳዊነት የተለየ መሆኑን አውቃለሁ፤ ዜግነትን በጎሰኛነት የሚተኩት እነማን እንደሆኑ ገብሩ አላወቀም ማለት ነው፤ ወይም አምስት መቶ ዶላር ኪራይ የሚከፈልበት ጊዜያዊ ዜግነት ከሌለው በቀር ወደ ቀበሌ መታወቂያ ለማውጣት ሲሄድ ያስረዱታል፤ እኔ ግን ዜግነትንና ጎሰኛነትን አላነካካቸውም፤ ዜግነቴንም እንዲያው በዋዛ አላየውም፡፡
* ..የኤርትራና የትግራይ ዜጎች.. ያልኋቸው ኢትዮጵያውያን ካልሆኑና የዜግነት ግዴታ ከሌለባቸው ኃላፊነቱን ከየት አምጥቼ ጫንሁባቸው?
* ገብሩስ የኢትዮጵያ ዜግነታቸውን ተገፈፉ ብሎ ወደቁጣና ወደመከፋት ያመራው ዜግነታቸውን ከዜግነታቸው ግዴታ እንዴት ለይቶ ነው?
የዜግነት መብትና ግዴታ በእያንዳንዱ ግለሰብ ፈቃድ ላይ የተመሰረተ ነው፤ ዘርን ወይም ጎሳን ከዜግነት ጋር ማገናኘት ግልጽ ስህተት ነው፤ በ1969 ሶማልያ ኢትዮጵያን በወረረበት ጊዜ አንድ የትግራይ ዜጋ በራሱ ፈቃድና ወጪ አዲስ አበባ መጥቶ ለመዝመት መወሰኑን በቴሌቪዥን አይተናል፤ የኢትዮጵያ ዜጋ ስላላልሁት በተግባር የገለጠውን የዜግነት ግዴታ ይፍቀዋል የሚል የጎሳ ህመም የያዘው ብቻ ነው፡፡
እጅግ የሚያስደንቀውና ከገብሩ በጭራሽ የማልጠብቀው የቼኮዝላቫኪያውን ጸሐፊ የሀበሻ ጀብዱ የሚለውን መጽሐፍ ገና ሳያነብበው መጥላቱ ነው፤ እኔ ሰውዬውን ጎበዝ በማለቴም የተበሳጨ ይመስላል፡፡
..የትግሬ ሽፍቶች.. በሚለውም ጥቅስ ተበሳጭቷል፤ የእሱ መበሳጨት አንሶ ሌሎችን ለመቆስቆስ ..በዚህ አባባልዎ ብዙዎች ዜጎችን ሳያስከፉ እንዳልቀሩ ሳልጠቅስ ለማለፍ አልፈልግም.. ይላል፤ ብዙ ሰዎችን የሚያስከፋው አባባሌ ምን እንደሆነ የታሪክ ፕ/ሩ አልተናገረም፤ የእኔን ጽሑፍ ያላነበበ ሰው አንድ መጥፎ ነገር የተናገርሁ ይመስለዋል፤ እኔ ያልሁት ስላልተጠቀሰ አንባቢው የራሱን ፍርድ ለመስጠት እንዳይችልና የገብሩን ፍርድ ብቻ ተቀብሎ መስመር እንዲይዝ ይጋብዘዋል፤ ከገብሩ እኔ የምጠብቀው አንደኛ ምንም ያህል ቢያስከፋ እውነትን ለመቀበል ዝግጁ መሆንን ነበር፤ ሁለተኛ ፀሐፊው የጠቀሳቸውን የትግሬ ሽፍቶች ለትግራይ ህዝብ በሙሉ ማልበስ አጉል ጎሰኛ አስተሳሰብ ነው፤ ትዕግስትና ፍላጐት አድሮበት መጽሐፉን ቢያነብበው የራስ ስዩምም ጦር ከራስ ካሣ ጦር ጋር ተሰልፎ ሲዋጋ እንደነበረ መረዳት ይችል ነበር፤ በህገ ኀልዮት (ሎጂክ) ለጥቂቶች የተነገረውን ለጠቅላላው ማልበስ ልዩ ስም ያለው የአስተሳሰብ ጉድለት ነው፤ ነገር ግን ፕ/ር ገብሩ በዚህ በህገ ኀልዮት ስሀተቱ እኔን ለማቄል ..በሽፍቶች አሳበው መላውን ትግሬ ለመፈረጅ ነው የሚል እሳቤ የለኝም ይላል፤.. እንኳን ይቺንና የዝንብ ጠንጋራ እናውቃለን ሲባል አልሰማም መሰለኝ..
በፍትህ ጋዜጣ ከአቶ ስብሓት ነጋ ጋር የተጀመረው ክርክር በአንድ ጉዳይ ላይ ነበር፤ ከዚያ ክርክሩ እየወረደ የጎሳ ሽታ ይዞ መጣ፤ የኔ የመጨረሻ ጥረት ይህንን የጎሳ ሽታ ለማስወጣት ነበር፤ ሐጎስ እርገጤ ሌባ ነው ሲል በላቸው የሚናደድ ከሆነ፣ እርገጤ ሐጎስ ሌባ ነው ሲል ጥዑም የሚናደድ ከሆነ እንደሰዎች ለመነጋገር የምንችልበት ጊዜ አልደረሰም ማለት ነው፤ በግላችንም ሆነ በህዝብነታችን የሚያዳክመን አጉል መሸፋፈንና ድብብቆሽ ነው፤ እውነቱን ለማወቅና እውነቱን ለመናገር ድፍረቱን ከአገኘን ሳንጎዳዳ እንደልብ ለመነጋገር እንችላለን፤ ለጋዜጦቹም ሆነ ለአንባቢዎች አንድ ለመግባቢያ የሚረዳን ሀሳብ ላቅርብ፤ INTERNET ውስጥ ገብተን LOGICAL FALLACY ብለን ብንጠይቀው በምንነጋገርበትም ጊዜ ሆነ በምንጽፍበት ጊዜ ሊረዳን የሚችል ትምህርት የምናገኝ ይመስለኛል፤ በገለባ እየለወጥን የምናውቀውንም የማናውቀውንም እያደባለቅን ብንነታረክ ዋጋ የለውም፤ ከዚያም በላይ እያንዳንዳችን ተምረናል፤ አውቀናል፤ ብለን በውስጣችን ያለውን መርዝ ከምንነዛው በውስጣችን ይዘነው እኛኑ እንዳደረገ ያድርገን፡፡

No comments:

Post a Comment