Translate

Friday, October 11, 2013

“የይሉኝታ ፖለቲካ ይገድላል”

“የይሉኝታ ፖለቲካ ይገድላል”

mitmitta1

“ሙሉ ኢትዮጵያዊ ነኝ” ትላለች። የተወለደችው ዱከም ነው። በቀድሞው አጠራር በኢትዮጵያ የተለያዩ ጠቅላይ ግዛቶች ኖራለች። ሐረር፣ ባህርዳር፣ አስመራ፣ አዲስ አበባን በመጥቀስ ልዩ ትዝታዎች እንዳሏት ትናገራለች። ከዛሬ ሃያ ዓመት በፊት አሜሪካ ከትማለች።

“ፖለቲከኛ አይደለሁም፣ እኔ አገር ወዳድ ነኝ። አገሬ የማንኛውም ጉዳዮቼና የውሳኔዎቼ በሙሉ መለኪያ ሚዛኔ ናት” ትላለች። ለአገሯ ማድረግ የሚገባትን እንዳላደረገች ይሰማታል። የይሉንታ ፖለቲካ ችግርና መዘዝ ያሳስባታል። በመናገርና ሃሳብን በነጻነት ስለመግለጽ ያላት አቋም የጸና መሆኑን አትደብቅም። በማህበራዊ ገጾች ንቁ ተሳታፊና መረጃ በማስተላለፍ በርካታ ተከታታዮች አሏት። በኢትዮጵያውያን የወቅታዊ ጉዳዮች መወያያ መድረክ አስተባባሪ ከሆኑት አንዷ ኃላፊ (አድሚን) ናት። ቤተሰቦቿ ካወጡላት መጠሪያዋ ይልቅ ራስዋ ለራስዋ ስም ተክላለች። ሚጥሚጣ ትባላላች። ሚጥሚጣ ከጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣለቀረበላት የቃለ ምልልስ ጥያቄ ተባባሪነቷን በመግለጽ የሚከተለውን አውግታናለች። ለጥያቄያችን ፈጣን ምላሽ በመስጠቷ የዝግጅት ክፍላችን ምስጋናውን ያቀርብላታል። ሚጥሚጣን እነሆ!
ጎልጉል፦ ሌሎችን የሚያቃጥል ስብዕና አለሽ?
ሚጥሚጣ፦ ምን ማለትህ ነው?
ጎልጉል፦ ስምሽ እኮ ሚጥሚጣ ነው፤ ያወጣሽውም ራስሽ ነሽ፤
ሚጥሚጣ፦ ጉድ እኮ ነው፤ አንተ ሚጥሚጣ ትወዳለህ?
ጎልጉል፦ በጣም፤ ግን መጠሪያዬ አላደርገውም።
ሚጥሚጣ፦ ሚጥሚጣ ምኑ ነው የሚያስደስትህ?
ጎልጉል፦ ማቃጠሉ፤
ሚጥሚጣ፦ አሁን ገባህ? ሚጥሚጣ የተባልኩበት ምክንያት ተገለጸልህ?
ጎልጉል፦ ጠያቂዋ እኮ አንቺ ሆንሽ። ስለ ሚጥሚጣ የተለየ ማብራሪያ አለሽ?
ሚጥሚጣ፦ ሚጥሚጣ እንደሚያቃጥል የምታውቀው ስትቀምሰው ነው። ካልቀመስከው ያው ዱቄት ነው የሚመስለው። እኔም ልክ እንደሚጥሚጣው አቃጥላለሁ። የማቃጥለው ክፉ ነገር አይቼ ባለማለፌ ነው። አየህ በይሉንታ መኖር የሚያመጣውን ጣጣ አውቀዋለሁ። አንናገርም እንጂ በይሉንታ ያልተጎዳ ሰው የለም። አገራችንም በይሉንታ …
ጎልጉል፦ ላቋርጥሽና ባህሪሽ ለሌሎች ይመቻል?
ሚጥሚጣ፦ ይመስለኛል። ግልጽነትን ለሚወዱ እመቻለሁ የሚል እምነት አለኝ።
ጎልጉል፦ ለመሆኑ አፍቃሪ ነሽ?
ሚጥሚጣ፦ አልመስልም?
ጎልጉል፦ ሃይለኛ ናት ይሉሻል?
ሚጥሚጣ፦ ወይ ጉድ፣ እነማን ናቸው ደግሞ እንደዚህ ባዮቹ?
ጎልጉል፦ ተባራሪ አስተያየት ነው፤
ሚጥሚጣ፦ ተሳስተዋል። እኔ ፊት ለፊት እናገራለሁ እንጂ ሃይለኛ አይደለሁም። እንደውም የተገላቢጦሽ ነው። በነገራችን ላይ ፊት ለፊት የሚናገሩ ሰዎች ተወዳጅ እንደሆኑ ነው የማውቀው።
ጎልጉል፦ ጥያቄዬን አልመለሽልኘም። አፍቃሪ ነሽ? ማፍቀር ትችይበታለሽ?
ሚጥሚጣ፦ በሚገባ። አፍቃሪ ነኝ። አፍቃሪ ልብ አለኝ።
ጎልጉል፦ የባል ወይስ የቤተሰብ?
ሚጥሚጣ፦ እዚህ ላይ እናቁምና ወደ ሌሎች ጥያቄ እንግባ፤
ጎልጉል፦ ግልጽ ነኝ ብለሽኝ ነበር። ምን ተፈጠረ?
ሚጥሚጣ፦ ምንም። ግን ግልጽነት የሆድን ሁሉ በመዘርገፍ አይደለም። አያያዝህ መድረሻው ስለገባኝ ወደ ሌሎች ጉዳዮች እንድናመራ ለማሳሰብ ነው።
ጎልጉል፦ ፖለቲከኛ ነኝ ብለሽ ታስቢያለሽ?
ሚጥሚጣ፦ አላስብም። አይደለሁም! በእኔ ባህሪ ልሁን ብልም አልችልም። ስብዕናዬ አይፈቅድልኝም።
ጎልጉል፦ ታዲያ ምንድነሽ? በፖለቲካው መድረክ ንቁ ተሳታፊ እንደሆንሽ የሚታይ መሰለኝ፤
ሚጥሚጣ፦ እኔ አገር ወዳድ ነኝ። በቃ አገር ወዳድ። አገሬን የምወድ፣ ለአገሬ የምቆረቆር፣ አገሬንና ባህሌን የማከብር፣ የአገሬ ሁኔታ እንቅልፍ የሚነሳኝ አገራቸውን ለሚወዱና ላገራቸው ያላቸውን ክብር በተግባር ለሚገልጹ ወገኖች ሁሉ ትንሽ ትልቅ ሳልል ክብር የምሰጥ ሰው ነኝ።
ጎልጉል፦ ሁሉም እኮ ባገር ይምላል፤ የጠፋው ቃልን ጠብቆ አገርን የሚያገለግል ነው።
ሚጥሚጣ፦ ይህ የእኔም ጥያቄ ነው። ግራ የሚያጋባኝና ብዙዎች ልባቸው እንደተሰበረ ሁሉ እኔም የተጎዳሁበት ጉዳይ ነው። ይሉኝንታ ገደለን በማለት ብዙ ጊዜ የምናገረው ለዚህ ነው።
ጎልጉል፦ አንቺም ይሉኝታ ያጠቃሻል ማለት ነው?
ሚጥሚጣ፦ እኔ የመሰለኝንና ያየሁትን በገባኝ መጠን አስቤ የምናገር ሰው ነኝ። ችግሩ ያለው በቡድን ስትሰራ ነው። “ለዓላማ ሲባል ዝም እንበል” የሚል ፈሊጥ አለ። ሁሉም ችግሩ የትና ማን ዘንድ እንደሆነ ያውቃሉ። ሰው ሁሉ ለመታለል ፈቃድ ካልሰጠ በስተቀር፣ ፈቅዶና ወዶ ካልሆነ በስተቀር አይታለልም። እያወቁ ዝም የሚሉ የይሉኝታ እስረኞች ስለበዙ የተወሰኑ በጣት የሚቆጠሩ ግልጽ ቢሆኑ ዋጋ የለውም።
ጎልጉል፦ በመናገር እኮ ማስቀየም አለ፤
ሚጥሚጣ፦ አዎ! ብዙ መናገርና ያለ በቂ ግንዛቤ መናገር ሌሎችን ቅር ያሰኛል። ለመናገር ብሎ መናገርም ተመሳሳይ ጥፋት ያስከትላል። እኔ በግልጽ ያመንኩበትን ስናገር ሰው ለመጉዳት ብዬ አይደለም። በተደጋጋሚ አስቤና መርምሬ የተረዳሁትን ችግር በሆዴ አልይዝም። ምን አልባት “ነገረኛ ነች” የተባልኩት ከዚህ በመነሳት ሊሆን ይችላል።
ጎልጉል፦ በይቅርታ ታምኛለሽ?
ሚጥሚጣ፦ በሚገባ። ካጠፋሁና እኔ ያሰብኩበት መንገድ በጓሮ ሳይሆን በግልጽ አሳማኝ ማብራሪያ ከቀረበበት አምናለሁ። ለጥፋቴም ይቅርታ እጠይቃለሁ። ብዙ ጊዜ ግን አጋጥሞኝ አያወቅም።
ጎልጉል፦ ለምን?
ሚጥሚጣ፦ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ዙሪያ የሚሰሩ ጥፋቶች ግልጽና ሊደበቁ የማይችሉ ናቸው። በተለይ በተቃዋሚዎች ዘንድ ያለው ችግር ምርምርና ጥናት የሚጠይቅ አይደለም። አስቀድሜ እንዳልኩት በይሉኝታ ታስረን እንጂ እናፍረጥርጠው ብንል የአፍታ ጉዳይ ነው።
ጎልጉል፦ ስለ ይሉኝታ ፖለቲካ ተጨማሪ አለሽ?
ሚጥሚጣ፦ እውነተኛ አገር ወዳድ ስትሆን መነጽርህ አገርህ ብቻ ነት። አገራቸውን በፍቅር የሚወዱ ሁሉንም ነገር የሚመዝኑት ሩቅ ባለው ትውልድ ሚዛን ነው። አገራቸውንና ህዝብን የሚዛናቸው ውሃ ልክ ያደረጉ ሰዎች ሸፍጥ አይገባቸውም። ማሸርገድ አያውቁበትም። በስም፣ በዝናና በማዕረግ እየተደነቁ ሁሌም ትክክል ናቸው ስለሚባሉ ሰዎች ደንታ የላቸውም። ይህ ስብዕናቸው ሁሌም ከይሉኝታ በላይ ያደርጋቸዋል። አብዛኞች ግን ይህንን ውብ ስብዕና በዝምታ ገድለውት ያገራቸው ጉዳይ ተመልካች ሆነዋል።
ጎልጉል፦ ስለ አድፋጭ ዜጎች እያወራሽ ነው?
ሚጥሚጣ፦ ከፖለቲካው ራሳቸውን አግልለው ጊዜ የሚጠብቁ ለማለት ፈልገህ ከሆነ የምለው የለኝም። የሚማርክ ነገር ሲኖር ያደፈጠው የተሸሸገበትን ግድግዳ እያፈረሰ ትግሉን ይቀላቀላል። ብዙም ቅስቀሳ አይፈልግም። በሌላ አነጋገር “የፖለቲካ ማገዶ አይፈጁም” (ረዥም ሳቅ …) ወያኔን ለመጣል ተነስተናል ብለው አንድ ርምጃ ሳይራመዱ እርስ በርስ ሲባሉ የሚታዩትን ፖለቲከኞች እያዩ እነዚህ ሰዎች እንዴት ወደ ፖለቲካው መንደር ይመጣሉ? ሁሉም የቤተሰብ ያህል የሚቀርቧቸውን ሰዎች ከጎናቸው አሰልፈው ሲነታረኩና የተቃውሞ ፖለቲካ ከተጀመረ አንስቶ ስልጣን አንለቅም ብለው ሲራኮቱ የሚመለከቱ ዜጎች “ምን በወጣን” ቢሉ እንዴት ይፈረድባቸዋል? እናም ጥያቄህን ቀጥል።
ጎልጉል፦ ከማድፈጥ ይልቅ በተሳትፎ ማስተካከያ ማድረጉ አይመረጥም? ማድፈጡና አያገባንም በማለት ዳር መቀመጥ በራሱ የሚወገዝ ነው የሚሉ አሉ?
ሚጥሚጣ፦ ትክክል ሊሆኑ ይችላሉ። በእኔ አመላከካት ግን ወያኔን ለመቃወም የፓርቲና የድርጅት ችግር ያለ አይመስለኝም። ድርጅትና ፓርቲ እንደ ድግስ ምግብ በየአይነቱ አለ። ከብሄር ጀምሮ እስከ ብሔራዊ፣ ትጥቅ ትግል የሚያምኑና በሰላማዊ መንገድ ለመታገል የሚወዱ ተለጣፊዎቹን ጨምሮ የድርጅት ችግር የለም። ችግሩ ያለው ታግለው የሚያታግሉት ጋር ነው። ሌሎችን የሚስብና የሚማርክ የፖለቲካ ትግል ህብረት እስካልተፈጠረ ድረስ ባለህበት እርገጥ ነው።
ጎልጉል፦ ተስፋ የቆረጥሽ ትመስያለሽ?
ሚጥሚጣ፦ በፍጹም። አላደርገውም። ህሊናዬ የሚፈቅደውን ማድረግ ከኔ የሚጠበቀውን ማከናወን ካልቻልኩ አደራዬን አልተወጣሁምና ያኔ ተስፋ ቆርጫለሁ ማለት ነው። አሁን ግን ማድረግ የሚገባኝን እያደረኩ ነው።
ጎልጉል፦ በይሉኝታ ፖለቲካ ደረሰ የምትይው ተጨባጭ ክስረት አለ?
ሚጥሚጣ፦ ስንቱን ልዘርዝር። አገር የሚያውቀውና ጸሃይ የሞቀው ጉዳይ ነው። የፈረደበት ምርጫ 97 ተከትሎ የተፈጠረው የቅንጅት መከፋፈል የውድቀታችን ቁንጮ መገለጫ ነው። ሁሉም ጉዳይ በወቅቱ በግልጽ ተነጋግረው ሊያርሙት ሲገባ በይሉንታ ችግራቸው ላይ ተኝተው ህዝብን ጉድ አደረጉ። ህዝብ አዘነ። አንገቱን ሰበረ። ያ ሁሉ ለለውጥ የተነሳ ሰራዊት አፈረ። ከዛም አንድነት ብለው መጡ ራሳቸው የቀድሞዎቹ የስህተት አባቶች ተመልሰው አንድነት ብለው ቢመጡም እንደ ስማቸው ከልብ አንድ ሆነው አልነበረምና በየጊዜው ይጣሉ ጀመር።ይባስ ብለው ተከፋፈሉ። አዳዲስ ሰዎች ወደ ፓርቲው አመራር ይመጣሉ ተብሎ ሲጠበቅ የቀድሞዎቹ እየተናከሱ መንገዱን ቀጠሉ። ፓርቲ እየቀያየሩ መገላበጥ ሆነ። አሁን ድረስ የጸዳ ነገር የለም። ይህንን ስል ንጹሃን የሉም ማለቴ አይደለም። የሚወደድ ስብእና ያላቸው አሉ …
ጎልጉል፦ የድርጅት አባል ነሽ?
ሚጥሚጣ፦ በቅርቡ የተቋቋመው የሰማያዊ ፓርቲ እያሸነፈኝ ነው።
ጎልጉል፦ ለማመን ይከብደኛል፤
ሚጥሚጣ፦ ለምን? ምን ሌላ ፓርቲ አለ? አሉ የሚባሉት ኮማ ውስጥ ናቸው። ሁሉም በመኖርና አለመኖር መካከል ባሉበት ወቅት ሰማያዊ ፓርቲ አንቅቷቸዋል።
ጎልጉል፦ በሰማያዊ ፓርቲ መማል የጀመርሽ መሰለኝ፤
ሚጥሚጣ፦ እኔ መማል ካለብኝ የምምለው በውዱ የኢትዮጵያ ልጅ ኦባንግ ሜቶ ነው። ኦባንግ አገር ወዳድነቱን በተለያዩ ጊዜያት፣ በተለያዩ መንገዶች፣ ያለ ማቋረጥ በፍጹም ቀናነት እያስመሰከረ ያለ ጀግናዬ ነው። መሃላን ስላነሳህ እንጂ በመሃላ የጀመርኩት ሰዎች በዜግነት ለሚሰሩት ስራ አውቅናና ድጋፍ ከመስጠት በዘለለ ልዩ የአድናቆት ከበሮ በመምታት አላምንም። ወደ ሰማያዊ ፓርቲ እንመለስ?
ጎልጉል፦ ይቻላል? ግን ለምን ሰማያዊ ፓርቲን መረጥሽው?
ሚጥሚጣ፦ ኢንጂነር ይልቃል ዘለቀ አገር ቤት ወያኔ ጎን ተቀምጠው ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ህገ መንግስታዊ መብታቸው ላይ ተኝተው የነበሩ ድርጅቶችን ማንቃት በመቻሉ ብቻ አደንቀዋለሁ።
ጎልጉል፦ አንቺ ብታደንቂውም “ልደቱ አያሌው” እያሏቸው ነው፤
ሚጥሚጣ፦ ሰምቻለሁ። ከሆነም የራሱ ጉዳይ። በሙያው ኢንጂነር ነው። አሁን በሞላ ግንባታ አንድ መንገድ ቆሞ ቢያሰራ ለኑሮው በቂ የሚሆነውን ገንዘብ ያገኛል። ይህን ያህል የሚጨንቀኝ ጉዳይ አይደለም። ነገር ግን የማዝነው አዲስ ብቅ የሚሉትን በሙሉ ጥላሸት እየቀባን ህዝብ የሚያምነው መሪ ማጣቱ ነው። ሁሉም ቀለም እየተቀባ የሚታመን መሪ ታጣ። ይህ አደገኛ ችግር ነው። አዲስ ሃሳብ ይዞ የሚነሳ ሰው ሲመጣ ታርጋ እየለጠፍን እንዴት ነው አብላጫ ቁጥር ያላቸውን ዜጎች ተሳትፎና ድጋፍ ማግኘት የሚቻለው?
ጎልጉል፦ ግን እኮ የግንቦት 7 አባልና ደጋፊ ነሽ ትባያለሽ?
ሚጥሚጣ፦ አይደለሁም። በቅርቡ የተካሄደውን ስብሰባ አዳምጫለሁ። ምንም እንኳ ለሰላማዊ ትግል ሙሉ ድጋፍ ቢኖረኝም ወያኔን ለመጣል አማራጭ ነው ተብለው የሚቀርቡ ሃሳቦችን አልቃወምም። ይቀጥሉ። ይበርቱ!!
ጎልጉል፦ እምነትሽ ሰላማዊ ትግል ላይ ነው ማለት ነው?
ሚጥሚጣ፦ አዎ!! ግን ብዙ ማብራሪያ የለኝም። በህዝብ ንቅናቄና እምቢተኛነት ለውጥ እንደሚመጣ አምናለሁ። ችግሩ በሰላማዊ ተቃውሞ ላይ አልተሰራም። የሙስሊሞች የድምጻችን ይሰማ ጥያቄ በሰላማዊ ተቃውሞ ላይ ከተሰራ ወያኔንን ማንበርከክ እንደሚቻል አሳምኖናል ባይ ነኝ።
ጎልጉል፦ ሞት ትፈሪያለሽ?
ሚጥሚጣ፦ አንተስ?
ጎልጉል፦ እኔ ሰው አፈር ውስጥ ሲገባና ሲከደንበት ያሳዝነኛል፤
ሚጥሚጣ፦ ለመሞት እንደተፈጠርክ ካወክ ሞት እንዴት ያስፈራል። የሚያስፈራው በቁም እየረከሱ መኖር ነው። ሞትማ ሞት ነው። ስትሞት ሁሉም ያልቃል። በቃ አሁን መለስ ዜናዊ አፈር እንደሆነው። በቃ!! በነገራችን ላይ ስለሞት አስቤ አላውቅም። በርግጥ ያሳዝናል። ማዘንና መፍራት ይለያያሉ። ልክ ነኝ?
ጎልጉል፦ ደፋር ነኝ ስላልሽኝና ደፋር የተባሉ ሞት ስለሚፈሩ ነው የጠየኩሽ፤
ሚጥሚጣ፦ ደፋር አይደለሁም። እኔ በነጻነት የምናገር ሰው ነኝ። አደራህን ደፋር ነኝ ብላለች ብለህ እንዳትጽፍ!
ጎልጉል፦ በነጻነት መናገር ፈልገሽ ያልተናገርሽው በውስጥሽ የታመቀ ጉዳይ አለ?
ሚጥሚጣ፦ መታመቅ ሳይሆን ብናገረው ዋጋ የሌለውና በድምጽ ብልጫ የማሸነፍበት መስሎ ስላልታየኝ ዝምታ የመረጥኩባቸው ጉዳዩች አይጠፉም። እኔ ይሉኝታ ባያጠቃኝም በይሉኝታ የተሸነፉ በበዙበት ሁኔታ የማልናገራቸው ነገሮች አሉ።
ጎልጉል፦ የወቅታዊ መወያያ መድረክ ECADF ላንቺ ምንሽ ነው?
ሚጥሚጣ፦ ብዙ የተማርኩበት ትምህርት ቤቴ ነው። የአገር ፍቅር የነገሰበት ሩም ነው።
ጎልጉል፦ ፓልቶክ ሱስ ይሆናል የሚሉ አሉ፤
ሚጥሚጣ፦ ፓልቶክ ሳይሆን የእኛ መድረክ ፍቅር አለብኝ። የወቅታዊ መወያያ መድረክ ሱስ አለብኝ። እወደዋለሁ።
ጎልጉል፦ መልካም ምሳሌዎቼ የምትያቸው አሉ?
ሚጥሚጣ፦ “እንደልቡ” የመጀመሪያው ነው። “እንደልቡ” አብረውት መስራት ለሚፈልጉ ሁሉ እሺ ባይ ታታሪ ሰራተኛ ነው። አብሮ ለመስራት የሚመች ሰው ነው። “ሙያዬ ምስክር” ስለ አገር ስትናገር ታስገርመኛለች። መጽሃፍ አለማዘጋጀቷ ያናድደኛል። “ዓላማ” ትዕግስትን በማስተማር የለበሰችውን የአዞ ቆዳ አውልቃ ያጠለቀችልኝ ታላቅ እህቴ ናት። ብዙ ሊረሱ የማይችሉ ሰዎች አሉ። አሁን ለምሳሌ “ባልዌን” ልትረሳው አትችልም። ቁጡ ነው። ወዲያው ደግሞ ይረሳዋል። ጥሩ ስብዕና አለው ሰው ነው። ግን ብቻ ይቅር ለራሱ እነግረዋለሁ። (እዚህ ላይ “እንደልቡ፣ ሙያዬ ምስክር፣ ዓላማ፣ ባልዌ” በመባል የተጠቀሱት የመዋያያ መድረኩ ዋና ኃላፊዎችና የረጅም ዓመታት ተሳታፊዎች ናቸው፤ ሚጥሚጣ የጠቀሰቻቸው በፓልቶክ ስማቸው ነው)
ጎልጉል፦ ጀምረሽማ አታቋርጪም፤
ሚጥሚጣ፦ ማጣላት አይቻልም ለራሱ እንግረዋለሁ።
ጎልጉል፦ ከአለቃሽና ከቤተሰብ ጋር ስልክ ስታወሪ ቆይተሽ ስትጨርሺ “ማይክ ፍሪ” ትያለሽ በሚል ያሙሻል፤
ሚጥሚጣ፦ ሳቅ … ሳቅ ይህ ሁሉ የፓልቶክ ሱሰኛ ነሽ ለማለት ነው? ወይ ጉድ…
ጎልጉል፦ የናንተ ፓልቶክ ክፍል ለወደፊቱ ምን እንዲሆን ትመኛለሽ?
ሚጥሚጣ፦ ታላላቅ የሚባሉ ሰዎች አሉበት፣ በርካታ ተሞክሮና ልምድ ያላቸው ሰዎች የሚታደሙበት፣ ተጣልተን ወዲያው የምንታረቅበት የቤተሰብ ያህል የምንቀራረብበት ክፍል ነው። እስከ ወዲያኛው ፍጹም ገለልተኛ ሆኖ እንዲኖር እመኛለሁ።
ጎልጉል፦ ምን ያስጠላሻል?
ሚጥሚጣ፦ እባብ አልወድም።
ጎልጉል፦ በጣም የምትወጂውስ?
ሚጥሚጣ፦ ሚጥሚጣና ሙዚቃ።
ጎልጉል፦ምን ዓይነት ሙዚቃ?
ሚጥሚጣ፦ የክራርና የመሲንቆ።
ጎልጉል፦ቁርጥና ጠጅስ?
ሚጥሚጣ፦መጠጥ አልወድም። በልጅነቴ ጥንስስ ከሸተተኝ ያመኝ ነበር። ቁርጥ ግን እወዳለሁ።
ጎልጉል፦ ከአብዮት ዘፈን የቱ ደስ ይልሻል?
ሚጥሚጣ፦ “ፈጣን ነው ባቡሩ፣ ቆራጥ ያልሆናችሁ እንዳትሳፈሩ፣ ፈጣን ነው ባቡሩ” የሚለውና “ተነሳ ተራመድ፣ ክንድህን አበርታ ላገር ብልጽግና ለወገን መከታ” የሚሉት ይታወሱኛል። በነገራችን ላይ በርካታ ደስ የሚሉ የአብዮት ዘፈኖች ተዘፍነው ነበር። ምን ያደርጋል…!! (Photo: 
Mitmitta Facebook)

No comments:

Post a Comment