Translate

Monday, February 25, 2013

ከእሁድ እስከ እሁድ


ከእሁድ እስከ እሁድ

(የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)
junedin reporter


“ጁነዲን ሳዶ ሳዑዲ ገብተዋል”
የቀድሞው የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩትና በቅርቡ ከሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትርነታቸው የተነሱት አቶ ጁነዲን ሳዶ ወደ አረብ አገር ማምራታቸውን አውቃለሁ ሲሉ አንድ ጎልጉል ተከታታይ ተናግረዋል።

ነዋሪነታቸው ሳዑዲ አረቢያ የሆነው እኚሁ ሰው ላቀረቡት ጥቆማ ማረጋገጫ አላቀረቡም። የሆነ ሆኖ አቶ ጁነዲን ኬንያ የፖለቲካ መጠየቃቸውን ኢትዮቻናል የሚባለው የመንግስት አንደበት የሆነው ጋዜጣ ይፋ አድርጓል። ኢትዮቻናልን በመጥቀስ ዜናውን በርካታ ሚዲያዎች የዘገቡት ሲሆን እስካሁን ድረስ ማስተባበያ አልቀረበም። አቶ ጁነዲን በትክክል ኬንያ የሚገኙ ከሆነ ኢህአዴግ ሊይዛቸው ስለሚችል ወደ ሌላ አገር ባስቸኳይ እንደሚያመሩ ከግምት በላይ አስተያየት ተሰጥቷል። ወደ አውሮፓና አሜሪካ ለማምራት አስቸጋሪ ሁኔታ ስለሚገጥማቸው ምን አልባትም የደንበኛችን ጥቆማ ትክክል ሊሆን ይችላል ተብሎ ቢገመትም ጎልጉል በራሱ መስመር ሊያረጋግጥ አልቻለም። አቶ ጁነዲን የሼኽ መሐመድ ሁሴን አላሙዲ የቅርብ ወዳጅ መሆናቸው ሲገለጽ የቆየ ጉዳይ ነው።
ኢህአዴግ ከዲያስፖራው ድጋፍ እንዳላገኘ ገለጸ
(ፎቶ: ከግድቡ ድረገጽ)
ዲያስፖራው ለአባይ ግድብ ቦንድ የሚፈለገውን ድጋፍ አለማድረጉን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ። የሚኒስቴሩ የግማሽ ዓመት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት እንደሚያስረዳው፣ ከዳያስፖራው ለአገር ልማት ሊገኝ የሚችለውን የሀብት ፍሰትና የልማት ተሳትፎ ለማሳደግ የሚያስችሉ ጥረቶች ቢደረጉም እየተገኘ ያለው ድጋፍ ግን ውስን ነው ሲል የተናገረው ሪፖርተር ነው።
በውጭ በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች 43 የድጋፍ አሰባሳቢና የቦንድ ሽያጭ ምክር ቤቶች አማካይነት  የድጋፍ ማሰባሰብ ሥራው በስፋት ቢሠራም ባለፉት ስድስት ወራት ለህዳሴው ግድብ የተገኘው አጠቃላይ ገቢ ግን 3.04 ሚሊዮን ዶላር ብቻ መሆኑን ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡ ከዚህ ውስጥ 2.7 ሚሊዮን ዶላር የተገኘው ከቦንድ ሽያጭ ሲሆን፣ የተቀረው 292 ሺሕ ዶላር ደግሞ በልገሳ የተገኘ ነው። ገንዘቡ እንደሚጠበቀው ባይሆንም ጠቃሚ መሆኑንና ወደፊት በስፋት መሠራት እንዳለበት የሚጠቁም ነው ሲል ሪፖርቱ ይገልጻል፡፡ በዚህም መሠረት የዳያስፖራ ፖሊሲ በማዘጋጀትና ሌሎችንም አማራጮች በመጠቀም ዲያስፖራውን ለማነቃነቅ በስፋት ዝግጅት ላይ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገልጿል፡፡
ታዋቂው የቻይና ኩባንያ ክስ መሰረተ
ፔትሮትራንስ የተሰኘው የቻይና ኩባንያ የካሉብና የሂላላ የተፈጥሮ ጋዝ መሬቶችን የኢትዮጵያ መንግሥት አላግባብ ቀምቶኛል ሲል ቅሬታውን ጄኔቭ ለሚገኘው ዓለም አቀፍ ንግድ ምክር ቤት አቀረበ፡፡
ፔትሮትራንስ በሶማሌ ክልል በኦጋዴን የተፈጥሮ ጋዝ ክምችቶች ለማልማት የሚያስችል ስምምነት ከማዕድን ሚኒስቴር ጋር በሐምሌ ወር 2003 ዓ.ም. ተፈራርሞ ነበር፡፡ ማዕድን ሚኒስቴር ኩባንያው በገባው ውል መሠረት የመስክ ሥራ አልጀመረም በሚል የፔትሮሊየም ልማት ስምምነቱን በሐምሌ 2004 ዓ.ም. ማቋረጡን ይፋ አደርጎ ነበር። የኩባንያው ኃላፊዎች ከማዕድን ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎች ጋር ለመደራደር በተደጋጋሚ ያደረጉት ሙከራ ባለመሳካቱ፣ ጉዳዩን ለዓለም አቀፍ ንግድ ምክር ቤት ግልግል ተቋም በታኅሳስ ወር መጨረሻ አቅርበዋል ብሏል፡፡ የማዕድን ሚኒስቴር ኃላፊዎች ለድርድር ፈቃደኛ ከሆኑ ለግልግል ተቋሙ የቀረበው አቤቱታ ሊቋረጥ እንደሚችል ሪፖርተር ምንጮቹን ጠቅሶ አስታውቋል፡፡
“ኢትዮጵያን ከመቅጣት አብሮ መቆየት”
ኢትዮጵያን አስመልክቶ በርሊን በተካሄደ ስብሰባ ተናጋሪ የነበሩት የኢትዮጵያ ጉዳይ አጥኚ ፕሮፌሰር ሽቴፋን ብሩነ ኢህአዴግን አሁን ያሉት አመራሮች የቀድሞውን ታጋዮች አይወክሉም አሉ። ፕሮፌሰሩ ስለ ጀርመንና ኢትዮጵያ ግንኙነት ፍንጭ ሰጥተዋል።
በሐምቡርግ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ጉዳይ አጥኚ ፕሮፌሰር ሽቴፋን ብሩነ የኢትዮጵያን የወደፊት ሒደት ማወቅ የሚቻለዉ በገዢዉ ፓርቲ መሪዎች መሐል ያለዉ የሐይል አሰላለፍ በግልፅ ሲታወቅ መሆኑን፣ «ኢትዮጵያ ከመለስ በኋላ» በሚል ርዕሥ ስር መናገራቸውን የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ አመልክቷል።
አርሶ አደሮችን በማፈናቀል ለባዕድ ከበርቴዎች መሬት በመቸርቸር፣ በምርጫ ማጭበርበር፣ በሰብአዊ መብት ረገጣ፣ ፖለቲከኞችንና እስረኞችን በማሰር ግንባር ቀደም የሆነው ኢህአዴግ ይህንን ሁሉ ሲያደርግ ለምን አውሮፓውያኑና አሜሪካ ዝምታን መረጡ በሚል በስብሰባው ላይ ለተነሳው ጥያቄ፤ ዉይይት ላይ የተገኙት በጀርመን የዉጪ ጉዳይ ሚንስቴር የአፍሪቃ ቀንድ ጉዳይ ምክትል ሐላፊ ሆልገር ክሬመርን “ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር መደራደር ከባድ ነው” የሚል መልስ ሰጥተዋል። ፕሮፌሰሩ በበኩላቸው ኢትዮጵያን በኢኮኖሚ ማዕቀብ አግዶ፣ ኢትዮጵያን ከማጣት ይልቅ አብረው መቆየትን መርጠው ሊሆን እንደሚችል መላምት መስጠታቸውን ከጀርመን ሬዲዮ ዘገባ ለመረዳት ተችሏል። በስብሰባው ላይ የመንግስት ተወካዮች አልተገኙም።
የፖሊስ አዛዡ በመንግስተ ሰማያት
(ፎቶ: stuffkit ድረገጽ)
የሳምንቱ አስገራሚ ዜና የቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ አዛዥ ነኝ ያሉ (ሳጅን ዘመድኩን) ከአሜሪካ ሬዲዮ የአማርኛ ክፍል ጋዜጠኛ ሰለሞን ክፍሌ ጋር ቃለ ምልልስ ሲያደርጉ የሰጡት ምላሽ ነው። በአዲስ አበባ ሙስሊሞች ቤታቸው ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ መፈተሹንና በፍተሻው ሰበብ ወርቅ፣ ሞባይልና የተለያዩ ንብረት መዘረፋቸውን ካስታወቁ በኋላ ምላሽ እንዲሰጡ የተጋበዙት የቦሌ ክፍለከተማ ፖሊስ አዛዥ በመልሳቸው ዛቻ ሰንዝረዋል።
አዛዡ ለቀረቡላቸው ጥያቄ “አላውቅም” የሚል መልስ ከሰጡ በኋላ ጋዜጠኛ ሰለሞን የአቤቱታውን መነሻ አጠንክሮ ሲጠይቅ “ከአሁን በኋላ ቢደውሉ ያሉበት ቦታ ድረስ መጥቼ እወስድዎታለው” የሚል ዛቻ አስከተሉ። ጋዜጠኛውም “እኔ እኮ ዋሽንግተን ዲሲ ነው ያለሁት” ሲል “ለማሰር” እንዲችሉ ትክክለኛ አድራሻውን አመላከታቸው። አዛዡም “ዋሽንግተን አይደለም መንግስተ ሰማያት ቢኖሩ ምንም የሚያገባኝ የለም … ” በማለት በቁጥጥር ስር እንደሚያውሉት ነገሩት። ሰለሞን “ፍርዱን ለአድማጮች እሰጣለሁ” በማለት ግርምቱን በመግለጽ ተሰናብቷል።
በሳውዲ የታሰሩት ክርስቲያኖች አገራቸው ሊመለሱ ይችላሉ ተባለ
በሳውዲ አረቢያ በእስር ላይ የሚገኙት 53 የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ ኢትዮጵያውያን አሁንም በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ የመኖሪያ ፈቃድ ካላቸው ሁለት ኢትዮጵያውያን በስተቀር ሁሉም ወደ አገራቸው ሊመለሱ እንደሚችሉ ጉዳዩንበቅርብ የሚከታተሉ ኢትዮጵያውያን ለኢሳት መግለጻቸው ታውቋል።
ኢትዮጵያውያኑ መቼ እንደሚመለሱ እስካሁን ባይታወቅም በቅርቡ ከሳውዲ ሊባረሩ እንደሚችሉ ጠቁመዋል። ከእሰረኞቹ መካከል 46ቱ ሴቶች ሲሆኑ፣ ፖሊሶች ለስነልቦና ጉዳት እየዳረጓቸው መሆኑም ታውቋል።
የዓለምአቀፉ ማህበረሰብ የእስረኞችን ደህንነት በተመለከተ በቂ ትኩረት አለመስጠቱ እንዳሳዘናቸው ኢትዮጵያውያኑ ተናግረዋል ሲል ኢሳት ዘግቧል። በሳዑዲ አረቢያ የክርስትና እምነት መከተል የሚያስከትለው መዘዝ ወገኖቻችንን እየጎዳ መሆኑ በተዘገበበት ዜና ስር አስተያየት የሰጡ “የሰው አገር ለመኖር ያገሩን ህግ ማክበር ግድ ነው።”፤ “ማን ሂዱ አላቸው?”፤ “አገሪቱ የሙስሊም አገር ናት …” የሚሉ አስተያየቶች ተነበዋል።
በስምጥ ሸለቆ ነዳጅ ፍለጋ ሊጀመር ነው
ጋምቤላ ነዳጅ ተገኝቷል
አፍሪካ ኦይል ኮርፖሬሽን በመካከለኛው የኢትዮጵያ ስምጥ ሸለቆ አካባቢ የነዳጅ ልማትና ፍለጋ ሊያካሂድ መሆኑን ፋና ብሮድካስቲንግ አስታወቀ። የማዕድን ሚኒስቴርና ኩባንያው በፍለጋው  የስምምነት ሰነድ ተመፈራርመዋል።
በፊርማው ወቅትም የማዕድን ሚኒስትሯ ወይዘሮ ስንቅነሽ እጅጉ “ነዳጅ ፈላጊ ኩባንያው በሃገሪቱ ጥናቶችን ሲያደርግ እንደመቆየቱና በሌሎች ሃገራትም ስኬታማ ስራዎችን እንደመስራቱ፣ ፍለጋው ውጤታማ ይሆናል ብለን እናምናለን” ብለዋል። የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ጀምስ ፍሊፕስ  “በኢትዮዽያም ተስፋ ሰጪ ጥናቶችን አካሂደናል ወጤታማ እንደምንሆነም እምነታችን ነው” ማለታቸውን ፋና ገልጿል።
ቱሎው ኦይል የሚባለው የነዳጅ ፍለጋ ላይ የተሰማራው ድርጅት እያካሄደ ያለው ቁፋሮ ውጤታማ መሆኑንና ቁፋሮው በተሳካ መልኩ እየተካሄደ በመሆኑ በአጭር ጊዜ ውጤቱን እንደሚያስታወቁ ሚኒስትሯ መናገራቸውን ተመልክቷል። በጋምቤላ ነዳጅ እየፈለገ ያለው የካናዳ ኩባንያ የተሳካ ውጤት እያስመዘገበ በመሆኑ ተጨማሪ ቦታ እንደተሰጠው ይፋ መደረጉ ይታወሳል። ከአካባቢው የሚወጡ መረጃዎች ነዳጅ እንዳለና ጥቅም ላይ መዋል እንደሚችል በመረጋገጡ ተጨማሪ ቦታ መከለል አስፈልጓል።
መልዕክት ከፍኖተ ነጻነት ጋዜጣ
የህትመት መሳሪያ ለመግዛት መረዳጃ ገንዘብ አላላክ (የፍኖተ ነጻነት ጋዜጣ ዝግጅት አስተባባሪ ኮሚቴ በሰሜን አሜሪካ)
ቀደም ሲል ለፍኖተ ነጻነት ጋዜጣ የህትመት መሳሪያ ማደራጃ ለመግዛት እንዲቻል ጥሪ መቅረቡ ይታወሳል። በጥሪው መሰረት በርካታ ወገኖቻችን ተግባራዊ ምላሽ እየሰጡ መሆናቸው በወገኖቻችን እንድንኮራ አድርጎናል።
ይሁን እንጂ በርካታ ወገኖቻችን በገንዘብ አላላኩ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ በመጠየቃቸው ይህን ማብራሪያ አቅርበናል።
ገንዘቡ የሚገባው በቀጥታ በፍኖተ ነጻነት አካውንት ነው።

No comments:

Post a Comment