Translate

Wednesday, February 27, 2013

ሞት በምልጃ፤ የበረሃ ጣዕር!


ሞት በምልጃ፤ የበረሃ ጣዕር!

ማስለቀቂያ ካልተከፈለ – ኩላሊት ለገበያ
tigist gebre
በሱዳን ሰዎችን በማፈን ሲና በረሃ የሚሰውሯቸው ራሻይዳዎች የተደራጁ ናቸው። ከአረብ ምድር የፈለሱ ናቸው የሚባልላቸው እነዚህ ጎሣዎች በሱዳንና በኤርትራ የሚገኙ ሲሆን በተለይ በኤርትራ ያሉቱ ከዘጠኙ ጎሣዎች መካከል የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ አኗኗራቸው የዘላን በመሆኑ ከኤርትራ መንግሥት ቁጥጥር ውጪ እንደሆኑ ይነገርላቸዋል፡፡ እነዚህ ጎሣዎች እጅግ አሰቃቂ የሆነ የአፈናና የጭከና ድርጊት ሲፈጽሙ በወጉ ታጥቀውና ዘመናዊ ተሽከርካሪ በመያዝ ነው። የሚታፈነውን ሰው ከተቆጣጠሩ በኋላ አዋራ ይነሳል። የሚከንፉበት ተሽከርካሪ አሸዋውን ተርትሮት ሲወረወር የሚነሳው ጭስ ሲበተን እነሱ የሉም። ቀሪው ተግባር “ሚስትህን፣ ወንድምህን፣ እህትሽን፣ ዘመድሽን ለሚያርዱ የሰውነት ክፍል ሌቦች አሳልፈን ሳንሰጥ ዶላር ክፈል ወይም ክፈይ” የሚለው ድርድር ነው። ይህ ድራማ መሰል ንግድ ሲከናወን ተገደው ይሁን የንግዱ ተባባሪ በመሆን በውል በማይታወቅ ሁኔታ የድርድሩ አስተርጓሚ ሆነው የሚሰሩት ኤርትራዊያን እንደሆኑ ተሰምቷል። ኢትዮጵያዊያኖችም አሉበት ይባላል። ማንም ይስራው ማን ድርጊቱ አሰቃቂ መሆኑ ብዙዎችን አስለቅሷል። አስጨንቋል።
በደላሎች እስራኤል ለመግባት ጉዞ ከጀመሩት ወገኖች መካከል ስንቶቹ በሲና በረሃ ሟምተው እንደቀሩ መረጃ የለም። ከሱዳን ምድር ወጥተው ግብጽ በመሻገር ሲና በረሃ እንደ ከብት ተበልተው የሚጣሉት ወገኖች ስቃይ ለሰሚው ግራ ነው። ወገኖቻችን ላይ የሚደርሰው አሰቃቂ መከራ ከቀን ቀን እየተባባሰ ነው። አሰቃቂ ዜናዎች መስማት ለየእለቱ የሚያስፈልገን መሰረታዊ ጉዳይ እስኪመስል ተለመዷል። ይህ አሳሳቢ ጉዳይ “እስከመቼ በዚህ ይቀጥላል” የሚለው የሁሉም ወገን “ዳር ቋሚዎች” ጥያቄ ነው።
“ለጆሮ የሚሰለች ነው፣ እርዳታ መስጠት ታከተን፣ የሚል መልስ የሚሰጡ አጋጥመውኛል። ድርጊቱ ተደጋግሞ ለጆሮ የሚያሰለች ደረጃ እስኪደርስ እነዚህ ወገኖች የት ነበሩ? ቢያንስ ሌሎች ላይ ተመሳሳይ ችግር እንዳይደርስ ምን ሰሩ? በውጪ አገር ያለን ወገኖች የሚረዳውንና የማይረዳውን መለየት የተሳነን ይመስለኛል” በማለት በሚኔሶታ የሚኖሩት ወ/ሮ ሰብለ አስተያየታቸውንና ተማጽኗቸውን ያሰማሉ።
የካቲት 3፤2005 (2/10/2013) የቪኦኤ አማርኛ ክፍለ ጊዜ ያሰማው እረፍት የሚነሳ ዜና እስካሁን አልተቋጨም። ሱዳን ሸገራብ በሚባለው ሰፊ የስደተኞች ጣቢያ ከባለቤታቸውና ከሁለት ልጆቻቸው ጋር ይኖሩ የነበሩ ወ/ሮ ትዕግስት ገብሬ ጥር 22 ቀን 2005 ዓ ም ቤተ ክርስቲያን ለመሳለም ከቤታቸው ይወጣሉ። በካምፕ ውስጥ ከሚገኘው ቤታቸው ወጥተው በግምት ሰላሳ ሜትር ሳይርቁ ታፈኑ።
ባለቤታቸው አቶ መልካሙ ባዬ ለቪኦኤ እንደተናገሩት አፋኞቹ ራሻይዳዎች ናቸው። ራሻይዳ የቆዳቸው ቀለም ጠየም ያለ የሱዳን፣ የኤርትራና የግብጽ ዜግነት ያላቸው ሲሆኑ ቀደም ሲል ከሶስት እስከ አራት ሺህ ዶላር እየተቀበሉ በደላላ አማካይነት ስደተኞችን በሲና በረሃ ወደ ግብጽ ያሻግሩ ነበር። እስራኤል በሲና በረሃ ወደ ድንበሯን ዘልቀው የሚገቡበትን የስውር መንገድ ስትዘጋው ራሻይዳዎቹ የገቢ ምንጫቸው ተዘጋ። ገንዘብ የለመዱት ወንበዴዎች የንግዱ ስልት ቀየሩና ሰው ማፈን ጀመሩ። አፈናውንም ከሚያካሂዱባቸው መንገዶች ጥቂቶቹ ድንበር አቋርጠው የሚጓዙትን አድፍጠው በመያዝ፣ ስደተኞችን ከስደተኛ ካምፕ አፍኖ በመውሰድ፣ ከሌሎች አፋኞች ስደተኞችን በአነስተኛ ገንዘብ በመግዛት እንደሆነ በጉዳዩ ላይ ጥናት ያደረጉት ሜሮን እስጢፋኖስ ይናገራሉ፡፡
ወ/ሮ ሰብለ ደምሴ ይህንን ዜና ሲሰሙ ደነገጡ። ዜናውን ካሰራጨው የቪኦኤ ዝግጅት ክፍል አድራሻ በመጠየቅ አቶ መልካሙን አገኟቸው። አቶ መልካሙ በቃለምላልሳቸው ወቅት እንደተናገሩት ሁሉ ለወ/ሮ ሰብለ የደረሰባቸውን ሁሉ አጫወቱ። ወ/ሮ ሰብለ “የሰማሁት ሁሉ እረፍት ነሳኝ። የማውቃቸውን ሰዎች ማስቸገር ጀመርኩ። ጊዚያዊ የባንክ ሂሳብ በመክፈት ገንዘብ ማሰባሰብ ጀመርኩ። ህይወት ለማትረፍ እየጣርኩ ነው” ሲሉ ጥሪ ያካተተ አስተያየት ሰነዘሩ።
ወ/ሮ ትዕግስት ገብሬ አሁን ያሉበት ሁኔታ አሳሳቢ ነው። አፋኞቹ 35 ሺህ ዶላር ካልቀረበላቸው የሰውነት አካል ክፍል ለሚዘርፉት አራጆች ያስረክቧቸዋል። እዚያ ከደረሱ ድርድር የለም። የሰውነት ክፍላቸው የበለጠ ዋጋ ስለሚያወጣ ሌሎች ወገኖች ላይ እንደተፈጸመው እርሳቸውም ላይ ይከናወናል።
የ12 እና የ 1 ዓመት ከስምንት ወር ልጅ ያላቸው ወ/ሮ ትዕግስት ባለቤታቸውን በስልክ እንዲያነጋግሩ ይደረጋሉ። ባለቤታቸውም ይሰቃያሉ። እግራቸውና እግራቸው መካከል ብረት ተደርጎባቸዋል። ይደበደባሉ። ይህ ሁሉ የሚደረገው ባለቤታቸው የተጠየቁትን ገንዘብ ባስቸኳይ እንዲከፍሉላቸው ለማስጨነቅ ነው። ባለቤታቸው እንደተናገሩት “ምንም አማራጭ የለኝም። የተጠየቀውን ገንዘብ ማግኘት አልችልም። ልጆቼ ወደፊት ሲጠይቁኝ ለምኜ አቃተኝ ለማለት እየለመንኩ ነው። ባለቤቴ ግን ምንም ማድረግ እንደማልችል ታውቃለች፤ … ” ብለዋል።
የ 12 ዓመቷ ልጃቸው ሱፊ “እኛንም እንዳይወስዱን ስለምንፈራ ከቤት አንወጣም” በማለት ልብ የሚነካ መልስ ከቪኦኤ ለቀረበላት ጥያቄ መልስ ሰጥታለች፡፡ “እናቴን አፈኗት” ያለችው ህጻን የበርካታዎችን ልብ እረፍት ነስታለች። ወ/ሮ ሰብለ “እንደዚህ አይነት አሳዛኝ ሲቃ ተሞላበት ጉዳይ እየሰማን በውጪ ያለን ወገኖች እንዴት 30 ሺህ ዶላር ማዋጣት አቃተን” ሲሉ ይጠይቃሉ። ወ/ሮ ትዕግስት ጸሃይ ቢተርፉ ለሌሎች በማስተማር ተመሳሳይ ችግር በሌሎች ወገኖቻችን ላይ እንዳይደርስ የማድረግ ስራ ይሰራል የሚል እምነት እንዳላቸው አስታውቀዋል።
በሰብአዊ ተግባርም ሆነ በየትኛውም ዓይነት ማህበር ተመሳሳይ ስራ ተሳትፎ እንደሌላቸው ያስታወቁት ወ/ሮ ገነት፣ ይህን ጉዳይ የሳቸውን ልብና አእምሮ ዕረፍት ነስቶት ለዚህ ተግባር ራሳቸውን እንደሰጡ ሁሉ፣ ሌሎችም ይህንን ልብ ሰባሪ አደጋ ሌሎች ወገኖችም ሰምተው ተባባሪ እንዲሆኑ በሚል ለጎልጉል አስተያየት መስጠታቸውን ተናግረዋል።
ለመንግስት ስለማሳወቃቸው ተጠይቀው በሱዳን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጸሐፊ ስልካቸውን በማፈላለግ ካገኙ በኋላ ማነጋገራቸውን ይገልጻሉ። በምላሹም “ይልቁኑ አፋኞቹ ስልካችሁን እንዳያውቁ ተጠንቀቁ። እየደወሉ ይጨቀጭቋችሁዋል” የሚል የማስፈራሪያ ማስጠንቀቂያ ማግኘታቸውን ይናገራሉ።
ቴዲ አፍሮ በፑንት ላንድ ሞት የተፈረደበትን የትግራይ ተወላጅ ኢትዮጵያዊ ቀድሞ በመድረስ ህይወቱን እንደታደገው አቶ መልካሙ አስታውሰው በተመሳሳይ የባለቤታቸውን ህይወት ሊታደግ የሚችል ወገን ሊኖር እንደሚችል ተቁመው ለማንኛውም “መፍትሔው እግዚአብሔር ዘንድ ነው” የሚል መልዕክት በቪኦኤ በኩል አስተላልፈዋል።
ወ/ሮ ሰብለ በበኩላቸው “ፈቃደኛነቱ ካለ ሁሉንም ነገር ማድረግ እንችላለን” በማለት የጀመሩት የነብስ ማዳን ስራ በቅርብ ወዳጆቻቸው መደገፉን አስታውቀዋል። አያይዘውም ሩጫው ከጊዜ ጋር መሆኑንን አመልክተዋል።
ገንዘቡ ከተገኘ ለአፋኞቹ እንዴት ይደርሳል? ወ/ሮ ትዕግስትስ እንዴት ነጻ ይሆናሉ? በሚል ወ/ሮ ሰብለ የሰሙት ነገር እንዳለ ለተጠየቁት፣ ሰዎቹ እስራኤል አገር ወኪል አንዳላቸውና፣ ገንዘቡ ለወኪሎቻቸው ሲገባ ግብጽ ወስደው እንደሚለቋቸው፣ ይህንን ለማከናወን የሚችሉ ሴት አቶ መልካሙ ማዘጋጀታቸውን እንደነገሯቸው የሴትየዋን ስም በመጥቀስ ተናግረዋል።
“በድብደባና በስቃይ ደክሜያለሁ። አሁን ገንዘቡ ተከፍሎ ቢለቁኝም በረሃውን አቋርጬ ግብጽ የምደርስበት አቅም የለኝም። እሞታለሁ። አትክሰሩ። እኔ አልተርፍም። የምትችሉ ከሆነ ህይወቴን ይወስዳት ዘንድ ለፈጣሪ ጸልዩ” ይህ ሲና በረሃ ታፍኖ የቆየ ኤርትራዊ ወጣት ለወንድሞቹ የተናገረው የመጨረሻ ንግግር ነበር። ወንድሞቹ እስራኤል አገር በስደት ሃዘን ተቀመጡ። ከዚያ በኋላ ስልካቸውን ቀየሩ። ወንድማቸውን በስልክ ድምጽ ነፍሱ ሳይወጣ ሞቱን ተቀበሉ” ሲሉ የሰሙትን ወ/ሮ ሰብለ አጫውተውናል። በሌላም በኩል በተመሳሳይ ታፍና የነበረች አንድ ወጣት የሚከፈለው ተከፍሎ በቅርቡ ከግብጽ አዲስ አበባ እንደገባች አመልክተዋል።
ለመጀመሪያ ጊዜ በሰሙት የሲና በረሃ አሰቃቂ ስቃይ ሳቢያ የወ/ሮ ትዕግስት ገብሬን ህይወት ለማትረፍ ራሳቸውን ከፊትለፊት ያቆሙት ወ/ሮ ሰብለ ሊያነጋግራቸው ለሚፈልግ ሁሉ የኢሜል አድራሻቸውን  አስታውቀዋል።  yegetasew@yahoo.com
ዝግጅት ክፍሉ፦ በተመሳሳይ፣ በተለያዩ ስፍራዎች የሚፈጸሙትን የወገኖቻችንን ስቃይ አስመልክቶ ላልሰሙ ትምህርት ይሆን ዘንድ ጽሁፍ ለምትልኩልና ወገኖች ሁሉ ቅድሚያ እንደምንሰጥ ለመግለጽ እንወዳለን። በተለይም በሱዳን የስደተኞች ካምፕ ከ30- 40 ዓመት የኖሩ ስደተኛ ወገኖች ጉዳዩን አስመልክቶ የኢትዮጵያዊን ተሳትፎ ምን እንደሚመስል ብትጠቁሙን ጉዳዩን እንደምናጣራው ከወዲሁ እንገልጻለን።
ወ/ሮ ሰብለና ለተመሳሳይ አላማ የተነሱት እህቶች የሚከተለውን ደብዳቤ ለእምነት ባልደረቦቻቸውና ለቤተክርስቲያን ያቀረቡትን የተማጽኖና እንቅስቃሴያቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ ከዚህ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።

የካቲት ፲፫/፳፻፬
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈሥ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
እውነት እላችኋለሁ ከሁሉ የሚያንሱ ከነዚህ ወንድሞቼ ለአንዱ እንኳን ስላደረጋችሁ ለእኔ አደረጋችሁ” ማቴ ፳፭  ፴፱
ጉዳዩ፦ በስደት ላይ እያሉ በአጋቾች ለታገቱ እናት ማስፈቻ የሚሆን ገንዘብ ስለማሰባሰብ
የክርስቶስ ሰላም ይብዛላችሁ በማለት መንፈሳዊ ሰላምታችንን እያስቀደምን ወደ ጉዳዩ እንገባለን።
ወ/ሮ ትዕግስት ገብሬ በሱዳን አገር ሸገርአብ የስደተኞች ጣቢያ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያዊት ስደተኛ ሲሆኑ በ01/22/13 ጠዋት ወደ ቤተክርስቲያን ሲሄዱ በራሻይዳዎች ታግተው በህይወት ለመውጣት ገንዘብ እንዲከፍሉ ተጠይቀዋል።
ባለቤታችው አቶ መልካሙ ባዬ በዛው በሸገርአብ የስደተኞች ጣቢያ ከአንድ ዓመት ከሰባት ወር ህፃን እና ከአስራ ሁለት ዓመት ታዳጊ ሴት ልጆቻቸው ጋር የሚኖሩ ሲሆኑ የተጠየቀውን ገንዘብ ለመክፈል ምንም አይነት አቅም ስለሌላቸው በ02/10/13/ በተላለፈው የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው ክፍል የመስታወት ዝግጅት ላይ ወገን ይደርስላቸው ዘንድ ተማጽነዋል ።
/ሙሉ ቃለ-መጠይቁን በዚህአድራሻ ማግኘት ይቻላል?
እኛም ሥማችን ከደብዳቤው መጨረሻ የተዘረዘረው ግለሰቦች ይህንን የተማጽኖ ድምጻቸውን ሰምተን ክርስቲያናዊ እና ወገናዊ ግዴታችንን ለመወጣት ከአሜሪካ ድምጽ/VOA / ጠይቀን በተሰጠን የስልክ ቁጥር በመደወል አቶ መልካሙን /የታጋቿ ባለቤት / አነጋግረን በምን ልንረዳቸው እንደምንችል እና አሁን ባለቤታቸው ያሉበትን ሁኔታ በዝርዝር አስረድተውናል።
በእኛ በኩል እስካሁን የተከናወኑ ተግባራት፦
1. በለንደን የሚገኘውን የAmensity International Sudan Team ስልክ በመደወል በእርግጥም ወ/ሮ ትዕግስት ገብሬ ከላይ በተጠቀሰው ቀን በአጋቾች እንደተወሰዱ በሱዳን ያለው UNHCR እንዳሳወቃቸው ሰምተን ጉዳዩ እውነተኛ እንደሆነ አጣርተናል።
2. በሱዳን ካርቱም ላለው የኢትዮጵያ ኤንባሲ በአንባሳደሩ ጸሐፊ በኩል ጉዳዩ የሚመለከተው ቆንስላ ክፍል ክትትል እንዲያደርግ አሳውቀናል።
3. የምናውቃቸውን ሰዎች ቃለ ምልልሱን ሰምተው የእርዳታ እጃቸውን እንዲዘረጉ ጥረት እያደረግን ነው።
4. ተጨማሪ የአየር ሰዓት አግኝተው እርዳታ ይጠይቁ ዘንድ በሸገር ሬድዮ የ‘ታድያስ አዲስ’ አዘጋጅ ከሆነው ከሰይፉ ፋንታሁን ጋር ተነጋግረን ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ 02/16/13 ሌላ ቃለ-መጠይቅ እንዲደረግላቸው አድርገናል
5. በአሁኑ ሰዓትም በዚሁ በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ የተለያዩ የራድዮ ጣቢያዎች ይህንን አሳዛኝ ነገር ወደ ህዝብ ጆሮ እንዲያደርሱ እየጠየቅን ነው።
6. በተጠላፊዋ ስም የFacebook ገጽ ከፍተን ፈቃደኛ የሆኑ ሰዎች በPaypal እርዳታ የሚሰጡበትን መንገድ እያመቻቸን ነው
7. Tewahedo.org. የተባለው የቤተክርስቲያን ድህረ-ገጽ ይህንን አሰቃቂ ነገር በፊት ገፁ እንዲለጥፍ አስፈላጊ መረጃ ልከናል።
8. ለዚሁ አገልግሎት ብቻ የሚውል የባንክ አካውንት ከፍተናል
በአሁኑ ሰዓት ገንዘቡ በፍጥነት መከፈል ካለመቻሉ የተነሳ በወ/ሮ ትዕግስት ላይ በኤሌክትሪክ እና በእሳት መቃጠል፤ ድብደባ፤ ተዘቅዝቆ መታሰር፤ እንዲሁም የሞቱ ሰዎችን አጥንት እያሳዩ የሥነ-ልቦና ጥቃት ማድረስ እና ሌሎችም ኢ- ሰብአዊ ድርጊቶች እየተፈጸሙባቸው መሆኑን ባለቤታቸውን በስልክ ባገኟቸው ቁጥር ከሚነግሯቸው ነገር ለመረዳት ችለናል።
ይህንንም ደብዳቤ ለመላክ የተገደድነውም በእኛ አቅም የተጠየቀውን 25,000.00 USD ሰብስበን የእኝህን እናት ህይወት ለማትረፍ የማንችል መሆኑን በማመናችን እና ይህ ገንዘብ ካልተከፈለ ግን አጋቾቹ “ከፍለን ነው የገዛናት ቢያንስ ያንን ለመመለስ ኩላሊቷን አውጥተን እንሸጣለን ” በማለት በግልጽ በመናገራቸው ይህ አደገኛ ነገር ከመከሰቱ በፊት ህዝበ ክርስቲያኑ የሚችለውን አድርጎ እኝህን እናት ለልጆቻቸው እንዲያተርፍላቸው በእግዚአብሔር ሥም በመጠየቅ ነው።
በአሁኑ ሰዓት መዋጮ መጠየቅ እንዴት ከባድ እንደሆነ ለሁላችንም ግልጽ ነው። ጉዳዩ የህይወትና የሞት መሆኑ አስገድዶን እና ለወገን ደራሽ የሆነውን ኢትዮጵያዊ ወገናችንን ተስፋ አድርገን ይህንን ለህዝበ ክርስቲያኑ እንድታስተላልፉልን የተሰደዱት ሁሉ መከታ በሆነችው በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ሥም በታላቅ ትህትና እንጠይቃለን። ከሁሉ በላይ ማህበረ ካህናቱም እና ምዕመኑ እኚህ እናት በህይወት ይወጡ ዘንድ ወለተማርያም እያሉ በፀሎት እንዲያሳስቡላቸው እንጠይቃለን።
ከመንፈሳዊ ሰላምታ ጋር
እሴተ ህይወት/ኢየሩሳሌም ጸጋዬ/ እህተ ማርያም (አዜብ ሮባ) ሰብለ ወንጌል /ሰብለ ደምሴ/
To wire money:
Seble Demissie Asefa
Swift code for international money wiring :WFBIUS6FFX
Routing number : 121000248
Online or in person transfer in the USA routing number : 019000019.
Account number is 7728584504.
Bank name: Wells Fargo
ስልክ ፡ (612) 636 1266 ስልክ ፡ (651) 366 2310 ስልክ፡ (612) 232 8720
የግርጌ ማስታወሻ፦
የባለቤታቸው አቶ መልካሙ ስልክ ቁጥር 011 249 116 112 170 ሲሆን አስፈላጊውን ጥያቄ ሁሉ ለመመለስ በማናቸውም ሰዐት ዝግጁ እንደሆኑ ለመግለፅ እወዳለን።

No comments:

Post a Comment