Translate

Thursday, February 28, 2013

ከኢህአዴግ ጋር ቅርበት እንዳላችው የሚታሙት ብፁዕ አቡነ ማቲያስ 6ኛው ፓትርያርክ ሆነው መመረጣቸው ይፋ ሆነ


የአሜሪካው ሲኖዶስ ምርጫውን እንደማይቀበለው በመግለጫው አሳውቋል
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን 6ኛ የፓትርያርክ ምርጫ ዛሬ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም. ተከናወነ፡፡ ቀደም ሲል የሟቹ ብፁዕ አቡነ ጳውሎስን ሞት ተከትሎ በአዲስ አበባና በአሜሪካ ባሉት ቅዱስ ሲኖዶስ መካከል የተቋረጠው እርቀ ሰላም እንዲቀድም የተለያዩ ጥረቶች ቢደረጉም ሳይሳካ በመቅረቱ ከአዲስ አበባው ቅዱስ ሲኖዶስ ጳጳሳት መካከል 6ኛ ፓትርያርክ እጩዎች ይፋ በተደረገው መሰረት ብፁዕ አቡነ ማቲያስ 6ኛ ፓትርያርክ ሆነው መመረጣቸው ይፋ ሆኗል፡፡
በእጩነት ከቀረቡት ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታ ዳውሮ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ፣ብፁዕ አቡነ ህዝቄል የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ እና የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ጸሐፊ እና ብፁዕ አቡነ ማቲያስ የኢየሩሳሌም ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ እንደነበር ለምርጫው የተዘጋጀ የግል መኀደራቸው አመልክቷል፡፡
በእጩ አቀራረብ ዙሪያ በርካታ አነጋጋሪ ጉዳዮች በጳጳሳት መካከል መፈጠሩና ከዕጩዎች መካከል አሁን ፓትርያርክ ሆነው መመረጣቸው ይፋ የሆኑት ብፁዕ አቡነ ማቲያስ ዘ-ኢየሩሳሌም አሜሪካዊ ዜግነት ያላቸው ናቸው፤ስለዚህ እጩዎች ውስጥ መካተት የለባቸውም የሚል ተቃውሞ ቀርቦባቸው እንደነበር ተጠቁሟል፡፡

ዛሬ እየተደረገ በነበረው 6ኛው የፓትርያርክ ምርጫ ደጀ ሰላም በምታካሂደው “ኢ-ቀጥተኛ” የምርጫ ድምጽ አሰጣጥ ከመረጡት መካከል ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በከፍተኛ ድምጽ በመምራት ላይ ሲሆኑ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ በሁለተኛነት ይከተላሉ። ዜናው በተጠናቀረበት
ሰዓት ያለው ዝርዝር ይህንን ይመስላል።
1) ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ 328 ድምጽ (33%)
2) ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፣ 185 ድምጽ (18%)
3) ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፣ 160 ድምጽ (16%)
4) ብፁዕ አቡነ ማትያስ፣ 159 ድምጽ (16%)
5) ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፣ 81 ድምጽ (8%) አግኝተው እንደነበር ቅርበት ያላቸው ድረገፆች ዘግበውት ነበር፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በአሜሪካን ሀገር የሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዛሬ በአዲስ አበባ የተደረገውን 6ኛ ፓትርያርክ ምርጫ እንደማይቀበልና እውቅናም እንደማይሰጠው ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

No comments:

Post a Comment