Translate

Tuesday, May 6, 2014

የአራቱ ህ.ዋ.ሃ.ት መሪዎች በትግራይ ጉብኝት አነጋጋሪ ሆኗል

ከአስገደ ገ/ስላሴ፣ መቐለ
ሰሞኑን ባልተለመደ መንገድ ከትግራይ ክልል የሰልጣን መዋቅር እርከን ወጣ ያለ የክልሉን ስልጣን የተጋፋ (የነጠቀ) የስለላ ስራ የሚመስል እንቅስቃሴ ከ23 አመት የህ.ወ.ሃ.ት አገዛዝ በኃላ አራት አዛውንት የለውጥ ሃዋርያት መስለዉ በመላው ትግራይ የክልል፣ የዞን፣ የወረዳ ከዛም አልፎ በቀበሌ ከተሞች ሳይቀር በልዩ ሃይል ታጅበዉ እየዞሩ ሰንብተዋል።

የነዚህ ሃይል ሃዋርያት ጉብኝት አላማዉ ለህዝቡና የክልል መዋቅር ሰራተኞች ለህ.ወ.ሃ.ት ታጋዎች ግልፅ አልነበረም። ነገር ግን እንቅስቃሴአቸዉ በ3ት መንገድ ይፈፅሙት ጀመሩ። ከነዚህም አንደኛ በየከተማዉ ያለዉ ከንቲባ ስብሰባ አስጠርተዉ ከተሰብሳቢዉ ህዝቡ ላይ ችግር ምን አለ፤ ነፃ ሁናችሁ ንገሩንና ችግሩን አብረን እንፈታዋለን። ሁለተኛ ከነዋሪዎች ቤት ለቤት እየዞሩ የስለላና የመረጃ አሰባሰብ ግለሰቦች ን በማነጋገር ያለዉን ችግር ይጠይቃሉ። ሶስተኛ በ17ት አመቱ የትጥቅ ትግል ጊዜ ልጆቻቸዉ የሞቱባቸዉ አዛውንት ወላጆች ነባር ሚሊሻዎችና ነባር የፓርቲ አባላት ለነበሩና ነባር ታጋዮች የነበሩ የጦር አካል ጉዳተቾች በተናጠል አነጋግረዋል፤ ይህ ተግባር በሁሉም ከተሞችና ገጠሮች ይሰሩት ነበር።
በሁሉም ስብሰባ ያደረጉባቸዉ ከተሞች አብዛኛዉ ተሰብሳቢ ችግራችሁን ንገሩን ሲሉት ከመናገር ዝምታን ይመርጡ ነበር። ምክንያቱም የህ.ዋ.ሃ.ት መሪዎች ባለፉት 39 አመታት የትግልና የአገዛዝ ዘመናቸዉ ፓርቲዉ በሚፈፅማቸዉ ስህተቶች ህዝቡ አኩርፎ የተቃውሞ ጥያቄ ሲያነሳ ስብሰባ ላይ ነፃ ሁናችሁ ተናገሩ ተብለዉ ይነገሯቸውና ሃቅ መስሏቸዉ የተናሩ ወገኖች ከስብሰባ በኃላ የተናገርከዉን ከየት አመጣሀዉ? ምንጭህ ከየት ነዉ? ብለዉ ምክንያት በመፍጠር ያስሯቸውና ከባድ ጉዳት ያደርሱባቸው ስለነበረ አሁንም ያ ልምድ (የፍርሃት ተሞክሮ) ስላለ ዝምታ መርጠዋል። ዘንድሮ ግን አራቱ የለውጥ ሃዋርያት ሁለት አይነት ቡድን ከህዝቡ ተስተውሏል። አንደኛ በአሁኑ የተበላሸ አስተዳደር ተጠቃሚ የሆኑ ሃዋርያቱን ለማስደሰት እየወደሱ ሲናገሩ ሁለተኛዉ ወገን ደግሞ በህዝብ ያለዉ ሁሉም አይነት በደል በማውሳት የህ.ዋ.ሃ.ት መሪዎችን ጭራሹን ሃገር የከዳችሁ ናችሁ ብሎ ልክ ልካቸውን ነገራቸዉ። አዛውንቶችም የተሰጣቸዉን የስድብ መረጃ በትእግስት በመሸከም የነገራችሁን ሁሉ ተቀብለናል ለዚህም ደረሰብን ያላችሁትን ችግር አድምጠናል፣ መልስ ይዘን እንመጣለን ብለዉ ተሰናበቱ። በተለይ ደግሞ በአላማጣ፣ በአድዋ፣ በአክሱም፣ በሽሬ ከባድ ፈተና ነበር ያጋጠማቸዉ።
በህዝብ የቀረበላቸዉ አስተያየት ህ.ወ.ሃ.ት ልጆቻችን ህይወታቸዉ ያለፉበት መሬት ላራሹ ጥያቄ የከተማ መሬት የግል ባቤትነት መሆን አለበት የሚል አላማ ከድታቹሃል፤ የትምህርት ፖሊሲያችሁ ትውልድ ገዳይ ነዉ፤ ያልለማን አልምተናል በድህንት ምክንያት ልጆቻችን በስድት ተበታትነዉ እያሉ ሃብታም ሁነናል ብላችሁ ዋሽታችሁናል። በከተማም ይሁን በገጠር ስራ አጥነት ስደት እያለ ፣ በማህበራዊ አገልግሎት ህክምናና ውሃ እጥረት ለበሽታ ተጋልጠን እያለን እናንተ ግን ሁሉም ነገር እንደተሟላልን አድርጋችሁ ትዋሻላችሁ። የንግድ ስርአቱን አበላሽታቹሃል፤ ፍትሃዊ ያልሆነ ግብር በመመደብ ምክንያት ባለሃብት ነጋዴዎች ከክልሉ ሸሽተዋል የኢትዮጵያ ህዝብ የታገለበት የመሬት ባለቤትነት ለነጠቃችሁት ባገሩ መጠለያ ሰርቶ ለመኖር አልቻለም። በአንፃሩም የህ.ወ.ሃ.ት ባለስልጣናት እስከ ቀበሌ መዋቅር ከናንተ ጋር ግንኙነት ያላቸዉ ግለሰቦች መሬቱን ወራችሁ ቤት ሰርታችሁበት ትኖራላችሁ። ድሃ ዜጎች ከ 30አመት በላይ ቤት ሰርተዉ የኖሩበት ቤታቸውን በማፍረስ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በበረሃ ተጥለዋል።የተቃውሞ ጥያቄ ያነሱም ታስረዉ፣ ያልተመለሱ ዜጎችም አሉ።
ሰልፍ የወጡ በጭስ ጋዝ በተኩስ በፖሊስ ድብደባ ተበትነዋል። ህብርተሰቡ ፍትህና ነፃነት አጥተዋል መልካም አስተዳደር የሚባል ለሽታም የለም ። መዋቅራችሁ በሙስና ተበላሽተዋል ጭራሹም የህዝብ ጩሀት የሚሰማ ጆሮ የላችሁም ብለዋቸዋል።በሽሬ ስብሰባ ስብሃት ነጋ የሰጡት ቃል አፋችሁ ሞልታችሁ በመናገር ወድቃቹሃል፣ አብቅታቹሃል ገደል ኣፋፍ ላይ ተንጠልጥላቹሃል እውነታችሁን ናችሁ ከናንተ ጋር ሁነን ችግሩን እንፈታዋለን ብሎዋቸዋል። በነ ስብሃት ነጋ በኩል ምንም ክርክር አልነበረም። ከዛም በኃላ ሃዋርያቱ ተደናግጠዉ ስብሰባውን አቋርጠዉ ሂደዋል ።
የለውጥ ሃዋርያቱ እንማን ነበሩ?
ሃዋርያቱ ስዩም መስፍን ከ36 አመት በላይ የህ.ዋ.ሃ.ት እና የመንግስት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የነበሩ፣ አቶ አባይ ፀሃዬ እስከ 1982 ዓ/ም ድረስ የማለሊት ሊቀመንበር የነበሩ አሁን በሚኒስተርነት ማእረግ አማካሪ ሆነዉ የሚሰሩ፣ ስብሃት ነጋ እስከ 1982 ዓ/ም ድረስ የህዋሃት ሊቀመንበር የነበሩና ከዛም በኃላ የኢፈርት ቦርድ ሊቀመንበር አሁን በመንግስት ባለስልጣ ፀጋይ በርሀ ቀደም ሲል የትግራይ ክልል በምክትል ሊቀ መንበር እስከ ሊቀመንበር ሆነዉ የነበሩ ናቸዉ። እነዚህ ሃዋርያት ትግል ከጀመሩበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ቅርብ ጊዜ የሻዕቢያ ጠበቃ በመሆን ብዙ የትግራይ ታጋዮችና ህዝብ በማሰርና በማሰቃየት ስራ ይሰሩ ነበር፤ ኢትዮጵያ ሃገራችን የባህር በር ባለቤትነትዋ እንድትነጠቅና ሉአላዊትዋ ሃገራችን በመቆራረስ ወሳኝ ሚና የነበራቸዉ ሲሆኑ በሃገራችን በተለይ በትግራይ በሁሉም አፈናዎች አስተዋፅኦ የነበራቸዉ በትግራይ ብሎም በሃገራችን ያለዉ የሙስና ወረራ አበጥረዉ የሚያውቁ ሙስናን ለመምታት ቁርጠኞች ያልሆኑ የህዝብ ብሶት መፍትሄ ከማይሰጡት የህዋሃት መሪዎች እንደሆኑ ሁሉም የሚያውቀዉ ነዉ።
90 ሚልዮን የኢትዮጵያ ህዘብ የመሬትና የቤቱን ባለቤትነት ተቀምቶ የህ.ዋ.ሃ.ት ኢህኣዴግ ተጠማኝ (ጠሰኛ) ሆኖ የዜግነቱን ማንነት እንዲያጣ ያደረጉ ናቸዉ። በሃገራቸን ያሉት የሙስና ግበረ ሃይላት በደምብ የሚያውቁ የህዋሃት ኢህኣዴግ መሪዎች አፄ ሃ/ስላሴና ከደርግ ንጉሳዊ ቤተሰብ በላይ የቅምጥል ኑሮ እጅጉን የላቁ መሆናቸዉ ዘር ማንዘራቸዉ ውጭ አገር ያሰፈሩ መሆናቸውን በትግራይ ብሎም በሃገር ያለዉ ጥልቀት ያለዉ ድህነት አበጥረዉ የሚያውቁ እና ለችግሩ መፍትሄ ደንታ የሌላቸዉ ሃዋርያት ናቸዉ።
ህዝብ አራቱ ሃዋርያይት ሊያመጡለት የሚፈልገዉ መልስ ምንድነዉ?
የኣምባገነኑ የአብዮታዊ ዲሚክራሲ ሁሉም አይነት ፖሊሲ ተሰርዞ የነፃ ኢኮኖሚ ስርአት ይፈልጋል፣ ከአፋኝ የህ.ዋ.ሃ.ት ስርአት ወጥቶ የግለሰብ መብት የሚያረጋግጥ ዲሞክራሲ፣ ፍትህ፣ ነፃነት፣ የህግ የበላይነት የሰብአዊና ዲሚክራሲያዊ በምቶች በተሟላ መንገድ እንዲረጋገጥለት ህዝብ የመሬት ባለቤት እንዲሆን ዜጎች መጠለያ የሚሰሩበት መሬት በነፃ እንዲያገኙ ፣ የሊዝ ፖሊሲ እንዲሰረዝ ዜጎች ከ 20 አመት በላይ ቤት ሰርተዉ የነበሩበት ቤታቸዉ የፈረሰባቸዉ ካሳ እንዲሰጣቸዉ፣ መሬት እንዲመለስላቸዉ ፣ የገጠር መሬት የግል ባለቤትነት ተረጋግጦ ህዝባችን የታገለበት መሬት ላራሹ አዋጅ እንደገና እንዲታወጅ ከሙስናና ወገናዊነት አድልዎ ነፃ የሆነ ስርአት አምጥቶ ከቁንጮ እስከ ቀበሌ አስተዳደር ተሰግስገዉ ያሉተን ሆዳም ሌቦች ተመንጥረዉ ስርአቱ እንዲቀየር ይፈልጋል።
የፍትህ አካለት ዳኛ ፣ፖሊስ፣ አቃቤ ህግ ደህንነት የሃገር መከላከያ ሰራዊት ከኢኣዴግ ብቻ አጃቢነት ነፃ ሆነዉ ለህዝብ እንዲያገለግሉ የመንግስት ብዙሃን መገናኛ ዜጎች እኩል እንዲጠቀምባቸዉ የግል ፕሬሶች መብታቸዉ ያለ ገደብ እንዲረጋገጥላቸዉ ይፈልጋል።ትውልድ ገዳይ የሆነዉ የትምህርት ፖሊሲ ስራ ፈጣሪ እና ስራ አጥነት የሚያስወግድ እንዲሆን ፖሊሲ ወደ ነበረበት እንዲመለስ አስተማሪዎች የሞያ እድገት አግኝተዉ ኑሮአቸዉ ተሻሽሎ ጥሩ አምራች ዜጋ እንዲያፈሩ ይፈልጋል።ያላአንዳች ተፅእኖ ከሰላማዊ ፓርቲ ጋር ተወዳድረን በነፃ ምርጫ የስልጣን ሽግግር እናደርጋለን ፣ ሁሉም የምርጫ መዋቀር ነፃ ታማኝ ገለልተኛ እንዲሆኑ በመንግስት መዋቅር ግልፅነት እና ተጠያቂነት እንዲኖር የመንግስት መዋቅሮች የህዝብ አገልጋይ እንዲሆን ይፈልጋል።
በበዙ ቢሊየን የሚገመት ገንዘብ የኢፈርት የአካል ጉዳተኞች ሃብት ለህ.ዋ.ሃ.ት መሪዎች ለልጆቻቸዉ ለዘር መንዝራቸዉ መንደላቀቂያ መሆኑ ቀርቶ በህዘብ ባለቤትነት እጅ ሆኖ ለድህነት ማጥፊያ እንዲውል ይፈልጋል።ከስደት የተመለሱ ዜጎችም እንዲቋቋሙበት የእርዳታ ማህበር ድርጅቶች ከህ.ዋ.ሃ.ትና ከመንግስት ተፅእኖ ነፃ ሆነዉ ለህዝብ እንዲረዱ እንፈልጋለን። ንፁህ ውሃ፣ ህክምና አድልዎ የሌለዉ እርዳታ እና ሰፍቲኔት የተጠና በዝቅተኛ ወለድ ብድር ቅናሽ የማዳበሪያ ዋጋ በህዝብ ፍላጎት እንዲሆን ፣አካል ጉዳተኞች፣ አረጋውያን በትግል ለተሰዉ ታጋይ ወላጆች እንክብካቤ እንዲደረግላቸዉ ይፈልጋል።
17 አመት ሙሉ ታግለዉ ያለአንዳች ጡረታ በግፍ የተባረሩ ታጋዮች በህ.ዋ.ሃ.ት መሪዎች ያለዉ ሃብት እንዲቋቋ ሙበት ይፈልጋል። በደርግ ስርአት ጊዜ በተለያዩ ሃይሎች ጋር ተሰልፈዉ አካላቸዉ የጎደሉ ዜጎች እንዲቋቋሙ ይፈልጋል። በህዝብ ውስጥ ተሰግስገዉ ህዝቡን እየከፋፈሉ የተረጋጋ ኑሮ ኖሮት በፍቅርና በመተሳሰብ እንዳይኖሩ የሚያደርጉ የህ.ዋ.ሃ.ት ሰላዮች እንዲወገዱለት አንድ ለአምስት የስለላ አደረጃጀት እንዲቀር አርሶ አደሩ መሬቱን ሊያከራያት በባንክ ሊያስይዛት ይፈልጋል።ህዝቡ ያለፍርድ ቤት እንዳይታሰር የቀበሌ አስተዳደሪዎች ማህበራዊ ፍ/ቤት የተማሩ እንዲሆኑ በህዘብ ተወዳጆች የሆኑ ከሙስና የፀዱ እንዲሆኑ፣ ሲቪክ ማህበራት ከህዋሃት መሪዎች ጣልቃ ገብነት ነፃ እንዲሆኑ ይፈልጋሉ።
የመንግስት ሰራተኞች ከጎስቋላ ኑሮ ሊያወጣ የሚችል ደምወዝ እንዲኖራቸዉ በስራ ላይ በሞያቸዉ እንዲመዘኑ እድገት እንዲያገኙ ይፈልጋል። ምርጥ ምርጡን እና ጥቅማ ጥቅሙን ለህ.ዋ.ሃ.ት አባላት መሆኑ ቀርቶ ዜጎች በስራቸዉ መጠን ተመዝነዉ መጠቀም አለባቸዉ። የዜጎች መስፈርት ከህ.ዋ.ሃ.ት ኣባል መሆን እንደሌለበት ሊሆን ይፈልጋል። ፍትሃዊ የግብር አደላደል ኑሮ ባለሃብቶች ያለአንዳች ተፅእኖ ሃብታቸውን አሰማርተዉ ስራ ፈጣሪ እንዲሆኑ ይፈልጋል ዩኒቨርሲቲ ተምረዉ በስራ አጥነት ተበታትነዉ የሚገኙ ስራ ፈጣሪ ፕሮጀክት እንዲፈጠርላቸዉ በሙስና የሚባክነዉ ሃብት ለዚህ እንዲውል ፣ለባለስጣናት እና የሙሰኞች ምንጩ ታውቆ እርምጃ እንዲወሰድ ይፈልጋል።
ታዲያ ከላይ የተዘረዘሩት የህዝብ ፍላጎቶች አራቱ ሃዋሪያት እንንዲመለሱ ያደርጋሉ?
እንዴት ብሎ ገዢዎችና ስልጣን የጣፈጣቸዉ እነዚህ ችግሮችን ከመለሱ ገመድ በአንገታቸዉ ውስጥ አስገብተዉ እንዴት ብልዉ ይታነቃሉ ? አይታሰብም እነዚህ አራት ሃዋሪያት ህ.ዋ.ሃ.ትን 39 አመት የመሩ ናቸዉ በሃገራችን ያለዉ ብሶትም የፈጠሩት እነሱ ነበሩ። አሁን ስህተታችንን አርመን ከህዝብ ጋር አብረን እንሰራለን ቢሉ ማን ያምናቸዋል። እነዚህ ሰዎች ባሁኑ ጊዜ ሁሉም ነገር ስለፈረሰባቸዉ ሁኔታውን ቆም ብለዉ አስበዉበት የኢትዮጵያ ህዝብ የውርደት ካባ ከሚያለብሳቸዉ ራሳቸዉ በሰላማዊ ሽግግር ስልጣኑን ለህዝብ ቢያስረክቡት ይሻላል።

No comments:

Post a Comment