Translate

Wednesday, April 9, 2014

ዲና ሙፍቲ ይመችዎት – “በነጻው ፕሬስ” ስም

ቀጭኑ ዘ-ቄራ

dina_mufti


ለምሳሌ አንድ አናጢና ግንበኛ የነበረ ሰው ጊዜ ረድቶት ወይም ተምሮ ወይም እድገት አግኝቶ ወይም …. በቃ በሆነ ነገር የጦር ጄኔራል ቢሆንና ተመልሶ ግንበኛ ቢሆን ምን ተብሎ ሊሰየም ነው? ግራ ያጋባል። ግን ደግሞ ላያጋባም ይችላል። የዛሬዎቹ ጄኔራሎች ኢንቨስተር ስለሆኑ ነዋ!! ለምሳሌ አንድ አምባሳደር ተብሎ የ”ተመደበ” ሰው፣ በግምገማ በሉት በገገማ “በቃህ” ቢባልና ቀድሞ ወደነበረው ሙያ ወደ ነርስነቱ ቢመለስ ምን ተብሎ ሊጠራ ነው? “አምባሳደር፣ ነርስ፣ እገሌ …”?

ቀጭኑ ዘ-ቄራ ነኝ። በውል በማይገባችሁ ምክንያት ተሰውሬ ነበር። ዛሬ እግር ጣለኝና “ላሸብር” መጣሁ። ሰላምታዬ መሆኑ ነው። መለስ ድንጋዩ ይቅለላቸው፣ አርማታው ስፖንጅ ይሁንላቸውና ብዙ አይነት የሰላምታ ቋንቋና ስታይል “አውርሰውን” አልፈዋል። ታላቁና አርቆ አስተዋዩ መሪያችን!! ህወሃቶች በዚህም ይቀኑ ይሆናል እኮ። መለስዬን ማን የነሱ ብቻ አደረጋቸው? እስኪ አርፈው ይተኙ፣ ይሙቱበት… እኔ ወደ ጉዳዬ ላምራ። “ግን መቃብራቸው ልዩ ጥበቃ የማይደረግለት ለምንድነው?” ሳልል ማለፍ አልፈልግም። ዋ!! ድንገት ቢነሱ!! ዋ ብያለሁ …
ግን አሁን አምባሳደር የነበረ ሰው ጡረታ ወጥቶ ደላላ ቢሆን “አምባሳደር፣ ደላላው፣ እገሌ” እያልን ልንጠራ ነው? የአገራችን ሚዲያዎች ነጻ መውጣት ያቃታቸው ከስም ስያሜ ጀምሮ ነው። ካላይ ያነሳኋቸው የኢህአዴግ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ “አቶ” ይቅርታ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ስም ነው ሌላ ጉዳይ ውስጥ ቀርቅሮ ያስለፈለፈኝ። እሳቸው አሁን የተመደቡበት መደብ “አምባሳደር” በሚል ርዕስ ከሆነ ግድ የለኝም። ግን ለጌቶቻቸው ቀላጤ ሆነው በህዝብ ግንኙነትና አንደበትነት ተመድበው ከሆነ ለጊዜው “አቶ” በቂ ነው። የነጻው ፕሬስ ሰዎች ወይም የበርጫ ቤት ባልደረባዬ ሽመልስ ከማል እርማት ይስጡበት።
አንድ በርጫ የሚወድ ጋዜጠኛ፣ አምባሳደር ዲና ሙፍቲን “ይከይፉኛል” በማለት አድንቆቱን ይቸራቸዋል። ዜና ሲጠፋ ሚስኮል ማድርግ ብቻ ነው። ምን ልታዘዝ በማለት የተመደቡበትን መደብ ሳይለቁ መግለጫ ይሰጣሉ። መብራት ሃይል ሰንደቁን አባሮ የመደባቸው ካድሬ መግለጫ መስጠት የጀመሩ ሰሞን ባህር ዳር እየደወሉ “ዛሬ ማታ ዜና ተመልከቱ፣ እኔ እታያለሁ” ይሉ ነበር። የመጀመሪያ ቀን ለዋንየው ሰውዬ ደውለውለት “ማን ጋር እንደደወልክ አውቀሃል” አላቸው። እሳቸውም ስማቸውን በመጥራት “እኔ እኮ ከፌዴራል መንግስት ነው የምደውለው” እንዳሉት እጎናቸው ያለ ሰው አጫውቶኛል። “ማን ይሙት” ካላችሁ፣ አንድ የምምልበትና የምገዘትበት ስም ነበረኝ “ተሰዋብኝ”። ስምም ይሰዋል። ዘንድሮ!! እኔን!! ለነገሩ የዘንድሮ መሐላ “ሰለሜ ሰለሜ” ሆኗል።
አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ለመለስ ሲያለቅሱ የሚያሳውን ፊልም እስኪ ዝም በሉና እዩት። እየተዝረበረቡ ሲነፈርቁ ጅል ነው የሚመስሉት። ለነገሩ ጅል መስለው ቁብ አሉበት። ከሳቸው ጋር አገራቸው ኮንፍራንስ የተካፈለ ሰው ሲናገር እንደሰማሁት የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር እያሉ ከአጃቢዎቻቸው ጋር መጡ። ኮንፍራንሱ ላይ እድል ተሰጣቸውና ተናገሩ። “እኔ የኢየሱስን ስም መጥራት የማይገባኝ … ” በማለት አነቡ። ተንበርክከው ነፈረቁ። ሁለት ኣመት ሳይሞላ እስክስታ ጀመሩ። ሰለሜ ሰለሜ እያሉ እሬብ ለሬብ ተያይዘው ዘለሉ።
አራዳው መለስ ነብሳቸውን ገለባ ያድርገውና፣ ቀላል ለማለት ነው ገለባ ያልኩት “የኢትዮጵያ ሚሌኒየም” ሲከበር አላሙዲን ባስገነቡት የኮንቴነር ቤት ውስጥ ነው። ለመሆኑ እሱ ቦታ የማን እንደነበር ስማቸው በኖህ የሚጀምር አንድ ሃብታምና አዋቂ ሰው አፈላልጋችሁ ድረሱበት። ከሂልተን እስከ ሸራተን በተደረገ ግብዣ የተሰረቀ ፕሮጀክት ነው። በትክክልም ላሸብር እንደመጣሁ የገባኝ አሁን ነው። ኮንቴነርም ቢሆን ይሁን፣ ፕሮጀክቱ ድራማ ቢኖረውም ማን እንደሳቸው። በብድርም ቢሰራ ይሁን ከማለት ውጪ ምን ይባላል? አላሙዲ ግን ይገርማሉ እኮ። በሄክታር 0.20 ሳንቲም ግብር መክፈል አቅቷቸው ከሆለታ አበባ እርሻቸው እንዲነሱ የገበሬ ማህበር ደብዳቤ ጽፎላቸዋል ነበር። ብዙ ነገር አለ። ጥልዬ ምንድን ነበር ያለው “ሆድ ይፍጀው” ግን ለምን ሆድ ይፍጀው እኛን ራሳችንን ፍጅ-ት ያድርገን።
እናም አምባሳደር ዲና ሙፍቲ “ሙድ” አላቸው። ሚዲያውን ለባላንስ/ማመጣጠኛ ረድተውታል። አንድ ወዳጄ ሲተርባቸው ሳይደወልላቸው ከዋለ “ምነው ወዳጆቼ ጠፉ ብለው ይጨነቃሉ። ለመረጃ ነው፣ የታሰረ ጋዜጠኛ ወይም የተዘጋ ፕሬስ አለ?” ብለው የወዳጆቻቸውን ደህንነት ይጠይቃሉ። ግን እኮ ዝም ከማለት መናገር ይሻላል። ለተመደቡበት ቦታ ብቃት አላቸው። ኢህአዴግም በረከትም “ይመችህ” ያሏቸው ይመስላል። በተለይ ለሰነፍ ጋዜጠኞች መተዳደሪያ ሆነዋል። በነገራችን ላይ “ለመረጃ” በማለት የታሰሩ ጋዜጠኞችና የተዘጋ ፕሬስ እንዳለ ሲጠይቁ መልሱ “ምን ነጻ ፕሬስ አለና” የሚል ነው አሉ።
እዚህ ላይ ተመቸኝ። አዎ ነጻ ፕሬስ ወዴት ግድም ነው የሚገኘው? የት ነው ነጻ ሚዲያ ያለው። ከኢህአዴግን እየበላ የሚያመሰግን አለያም ሲመች እየተቸ ሲነቃነቅ ጥብቅና የሚቆም ወገንተኛ፣ ይህ አንዱ ነው። ሌላው ጭልጥ ብሎ መቃወም ነው። “ይህ ጥሩ ነው ግን” ብሎ የሚጀምር እንኳን የለም። ከጅምሩ ራሱ ኢህአዴግ በረከትን ልጓም የሌለው በትር ሰጥቶ ሊማርና ሊገራ የሚችለውን ጅምር አከሸፉት። ተወደደም ተጠላም ግን የተመጣጠነ ሚዲያ ግድ ነው። አለያ መጀመር እንጂ መጨረስ ይከብዳል።
ሃይለማርያም ሰለሜ ሰለሜ መጨፈር የሚችሉ አይመስለኝም ነበር። በነፈረቁበት ቤት እየተፍለቀለቁ ተምነሸነሹ – ደስ ይላል። ቤተ ክርስቲያናቸውና የሚያመልኩት መንፈስ ምን እንደሚላቸው ባለውቅም ሲጨፍሩ ደስ ብሎኛል። ቴድሮስ አድሃኖም እንደውም የቱሪዝምና ባህል ሚኒስትር ሁነው ኪነቱን ቢያነቃንቁ እመርጣለሁ። በነጻነት ፉት እያሉ እንዲሰሩ!! ሃይለ ማርያም ሲጨፍሩ በደስታ ስሜት ሆኜ መለስን ነፍስ ዘራሁባቸው። ህዝብ ፊት ቀርበው ዘፈን ምረጡ ሲባል “ሱዳንኛ” መርጠው ነው ከውዳቸው/ይቅርታ ውዳቸው የሌሎችም ውድ ነበሩ/ አብረው መስታዋት ቤት ውስጥ ሆነው በእጥርጥር የደነሱት!! የት? ሚሌኒየም አዳራሽ። አስቡት ኮንቴነር ቤት ውስጥ፣ በጋርዶች በተከበበ፣ በከባድ መሳሪያ በታጠረ፣ ጥይት በማይበሳው መስታዋት ውስጥ ሆኖ መዝናናት … ለትዝታ ያህል ነው። ታዲያ እሳቸው ሲሞቱ ያርማጮ ገበሬ ደረት መታ፣ ጸጉር ነጨ፣ የመንዲ እናት ደረቷን ደቃች። አዲስ አበባ በየቀበሌው ድንኳን ተጥሎ የቀበሌ የጸጥታ ሃላፊና ሊቀመንበርን “ነብስ ይማር፣ እግዜር ያጽናችሁ” እያለ ህዝብ ሲሰናበት … ጉድ እኮ ነው።
ቀጭኑ ዘ-ቄራ ኢህአዴግ “እንዲቀየር” የሚፈልገው እንዲህ ያሉ መለኪያ አልባ በሽታዎች ገሀድ ሲወጡ በዛው በጠንባራ ሚዲያ ለመመልከት በመጎምጅት ነው። እና መለስ በሱዳን ዘፈን ጨፈሩ!! ለምን? መሄድ የምትፈልጉ ሂዱና ጠይቋቸው። ቀጭኑ ሞትን ይፈራዋል። በድንገት ተስፈንጥሮ መሔድን አይወድም። አሁን የአራራ ሰዓት ነው!! ልሂድበት። እናንተም ተቀንጠሱ!! አምባሳደር ሙፍቲ ይመችዎት!!
ማሳሰቢያ፡- ከላይ ስለ አምባሳደርነት በምሳሌ ያነሳሁት የሙያ መጠሪያ ከአምባሳደር ዲናም ሙፍቲም ሆነ ከማውቃቸው አምባሳደሮች ጋር አንዳችም ግንኙነት የለውም። አምባሳደርነት የስራና የቦታው ሹመት እንጂ እንደ ሙያ ስም ለዘላለም ከሞት በኋላም የሚያገለግል አይደለም ለማለት ብቻ ነው!!

No comments:

Post a Comment