Translate

Thursday, April 3, 2014

የማለዳ ወግ… በጨለመው የሳውዲ ወህኒም ይነጋል… (ነብዩ ሲራክ)

ግፍ ከበዛበት ወህኒ የአክብሮት ስላምታየ ይድረሳችሁ! (ነብዩ ሲራክ፣ ከሳውዲ አረብያ ውህኒ ቤት)

Nebiyu Sirak
ጋዜጠኛ ነብዩ ሲራክ
እነሆ ለሁለተኛ ጊዜ ለአፍታ ያህል እድሉን አግኝቸ ወህኒ የመውረዴን እውነታ ላስረዳችሁ ግድ አለኝ ። ዛሬ አስረግጨ የምነግራችሁ ወህኒ የመውረዴ ምክንያት ሚስጥር ግምሽ እድሜየን ህግና ስርአቷን አክበሬ የኖርኩባትን የሳውዲት አረቢያን ህግ ተላልፊ አይደለም ! የስደተኛው ጉዳይ ያገባኛል በሚል የማቀርበው መረጃ ቅበላየ የማይመቻቸው ፣ ያመማቸው ከተሴረውና እየተሴረ ካለው እገታ ጀርባ ስለመኖራቸው አልጠራጠርም ። … ዛሬ በዚህ ዙሪያ ብዙ አልልም!
አላወቁትም እንጅ ክፉዎች ጠቅመውኛል ፣ ያላየሁትን እንዳይ አድርገውኛል። መንገዱ የከፋ ቢሆንም በወሰዱኝ መንገድ ተመርቸ እሰማው የነበረውን የወገኖቸ የወህኒ የከፋ ኑሮና ህመም ፣ በተቆርቋሪ ጠያቂ ማጣት ፣ በፍትህ መነፈግ እይሆኑ ያሉትን ከመስማት ማየት ማመን ነውና በአካል ማየት ችያለሁ !
ከመታሰሬ ጥቂት ቀናት በፊት በግፍ ለተደበደበው፣ ሁለት አይኑን ላጣውና “አይሆኑ ከሚሆን ቢሞት ይሻላል” ተብሎ የፎቶ መረጃው ሳይቀር በእጀ የገባውን ወጣት ምንዱብ የወህኒ ህይወትን ተጨባጭ ታሪክ ከአይን እማኞች ቃርሜያለሁ! እሱም ያለው ከታሰርኩበት የቅርብ ርቀት ነው ።… አትጠራጠሩ አገኘውም ይሆናል !

በዚህ የጭንቅ ሰአት ከእኔና ከቤተሰቦቸ ጎን ሆናችሁ አለኝታነታችሁን ለገለጻችሁልኝ ምስጋናየ ከፍ ያለ ነው ! ዛሬ ወደ ዝርዝር ጉዳዩ አንገባም ። በመላ አለም የምትገኙ ወገኖቸ ያሳያችሁኝ ድጋፍና መቆርቆር ከጨለማው ቤት ደርሶኝ ጽናት አጎናጽፎኝ ሰንብቷል። ይህም በአረብ ሃገር ስደተኛ ዙሪያ ሳቀርነው ለነበረው መረጃ ያገኘሁት ክብርና ሞገስ ሆኖ መከራውን አስረስቶኛል: ) ምስጋናየ አይለያችሁ!
ወገኖቸ ወዳጆች ፣ ዛሬ ሰላም መሆኔን ብቻ ተረዱ ብየ እንጅ በሰፊው ስለሚሆነው አቅም በፈቀደ መጠን እናወራለን ! ዝምታው ከናፈቅኳቸው ልጆቸ ፣ ከቤተሰቦቸና ከእናንተ ጋር የሚያደርሰው መንገድ ውል እንዲይዝ የሚደረገው ሙከራ ውል እንዲይዝ የሚተጉ ወገኖችን ሂደት ላለማደናቀፍ ብቻ ለመረጋጋት ሲባል ብቻ ነው !
በጨለመው የሳውዲ ወህኒም ይነጋል ፣ በንጋቱ ጮራ ታግዘን የምናወጋው የማለዳ ወግ ናፍቆኛል: ) ይህን ለማድረግ የሚከፈለውን ሁሉ ለመክፈል ደግሞ ልቤ ብርቱ ነው …
ሰላም ለሁላችሁ !
ነቢዩ ሲራክ
ከአንዱ የሳውዲ ወህኒ ቤት

No comments:

Post a Comment