Translate

Thursday, April 24, 2014

በሱዳን ያሉ ስደተኞች በምጥ ቀጠና ውስጥ… (በግሩም ተ/ሀይማኖት)

ሰሞኑን ሱዳንም እንደ ሳዑዲ አረቢያ ኢትዮጵያዊያኖችን ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ደፋ ቀና እያለች ነው የሚል ወሬ ተናፍሶ ብዙዎች ምጥ በቁናን አስበው እህህህህን እያቀነቀኑ ነው፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትም ተስማምቷል፡፡ (ደህና ነገር አዘጋጅቶ ረግጠው የወጡ ይመስል ለማስመለሱ ፍጥነቱ ይገርማል፡፡ ከሰዑዲ ተመላሾች ምን ተደረገላቸው?) ታዲያ ሲስማማ የዜጎቹን መብት ለማስጠበቅ ቅንጣት ያህል እንደማይደራደር የብዙዎች ፍርሃት ነው፡፡ አሁን የስደተኛው ፍርሃቱ እውን ሆኗል፡፡ ይፋም ተደርጓል፡፡ ኢህአዴግ ዳግም ሊሳሳት የማይገባው በሳዑዲ አረቢያ እንደተደረገው ዜጎቻችንን በአደባባይ መጨፍጨፍ እና ማሰቃየት እንዳይከሰት ጥንቃቄ መደረግ አለበት፡፡ ቢሆንም ተቃዋሚ የሚባሉ በችግር ከሀገር የወጡ ስደተኞችና ኢህዴግን የማይደግፉ ግን እንኳን ወደ ሀገር መመለሱ እየተደረገ አይደለም አሁንም ጉሸማና እስር እንዳልቀረላቸው ይነገራል፡፡

    በዚህ ዙሪያ ሱዳን ያሉ ወዳጆቼን ለማናገር ሞክሬ ነበር፡፡ ሁሉም ፍርሃት የሸበባው በመሆኑ ችግሩን ገልጸው ለመናገር ያልደፈሩ መሆናቸው ያመሳስላቸዋል፡፡ ፍርሃታቸውን ሳይ ገዢው ፓርቲ በህዝቡ ላይ እያደረሰ ያለውን ግፍ ብገነዘብም ስደት ተወጥቶም መፈራቱ አሳዝኖኛል፡፡ በሀገር አላኖር፣ በሰው ሀገርም አላኖር ማለቱም ይገርማል፡፡ መግረም ብቻም አይደለም ይሄ ትውልድ የለበሰውን የፍርሃት ሸማ የሚያወልቀው መቼ ነው ያሰኛል፡፡ በሌላ በኩል ያናገርኳቸው ሁሉ የሚስማሙበት አንድ ነገር አለ፡፡ ወደ ሀገር መመለሱ ብቻ ሳይሆን አሁንም ኢትዮጵያዊያን ላይ እየተደረገ ያለው ግፍ ማነው ሀይ የሚለው? ዋነኛ ጥያቄያቸው ሲሆን መታሰር እና መደብደብ፣ እንግልት እንዲቆም እና በሰላማዊ መንገድ ወደ ሀገር መመለሱ እንዲከናወን ይመኛሉ፡፡ ወደ ሀገር መመለሱ ሳይታሰብ ጀምሮ ኢትዮጵያዊያን የሚሰቃዩበት ሁኔታ እንዳለ ነው አሁንም የሚናገሩት፡፡ የፍርሃታቸው ምንጭም ይሄው እስር እና እንግልት ይመስለኛል፡፡
   በፊትም ቢሆን ሱዳን ውስጥ የኢህአዴግ ካድሬዎች የፈለጋቸውን ማድረግ እንደሚችሉ የታወቀ ነው፡፡ የኢህአዴግ ካድሬዎች ከሀገር ውጭ እንደልብ ከሚንቀሳቀሱባቸው ሀገሮች ዋነኛዋ ሱዳን ናት፡፡ አሁን ደግሞ እንኳን ዘንቦብሽ እንዲሁም…እንዲሉ ተቃዋሚ ሀይሎች እንቅስቃሴ ከጀመሩ ጀምሮ ሱዳን ከለላ፣ መሸጋገሪያ እንዳትሰጥ ያልተደረገ አይነት ጥረት የለም፡፡ እንዲያውም ድንበር አካባቢ ያለው መሬት ተቆርጦ የተሰጠበው በአባይ ግድብ ድጋፍ ለማግኘትና ለተቃዋሚዎች መንቀሳቀሻ መሬት እንዳትፈቅድ እጅ መንሻም ለማድረግ ነው የሚሉ ፍንጮች አሉ፡፡ የሆነው ሆኖ ሲዳን ውስጥ በየቦታው የወያኔ ጭፍራዎች፣ ካድሬዎች ስደተኛውን አላኖር ብለዋል፡፡ ስደተኛውን የመከታተላቸው ሂደት UNHCR ቢሮ ድረስ ዘልቆ የገባ በመሆኑ ከቢሮው የሚሰጠውን የስደተኛነት ማረጋገጫ /Mandate/ በአመት መታደሱ ቀርቶ በየስድስት ወሩ እንዲታደስ በማድረግ ስደተኛውን ለመቆጣጠር እንዲያመቻቸው  አድርገዋል ብለው ቅሬታ የሚያቀርቡ ልጆች አጋጥመውኛል፡፡
  በርካታ ኢትዮጵያኖች በየቀኑ እየታሰሩ እንደሆነም የገለጹልኝ ልጆች አሉ፡፡ እስር ቤት ለገቡት የሚያያቸው ወይም የሚከራከርላቸው የለም፡፡ እምዱርማ የሚባል እሰር ቤት አለ፡፡ እዚህ እስር ቤት የሚሰቃዩ ኢትዮጵያዊያኖች ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ የምግብ ችግር አለ፣  እንኳን መብታቸውን መጠየቅ ይቅርና ሄደህ ለማናገር አትችልም፡፡ ወደዛ መሄድ ራሱ አስፈሪ ስለሆነ ማንም ደፍሮ ሄዶ ሊያይ አይቻልም…ብቻ ያሉበትን ሁኔታ ማወቅ እንኳን አስቸጋሪ ነው ብለውኛል፡፡ እግዚአብሄር ስደተኛ ወገኖቻችን ከሚደርሰው…ከፈሩት ስቃይ አንተ ጠብቅልን፡፡
     በኤምባሲውም ምንም ተስፋ እንደሌላቸው ሲገልጹልኝ…‹‹ኤምባሲው ስራው ለዜጎች የሚጠቅም ሆኖ አይተነብ አናውቅም፡፡ ከትግራይ ክልል የሚመጡ ራሳቸውን ትግራይ ባንድ ብለው የሰየሙ አርቲስቶች አሉ፡፡ ሙዚቃ ዝግጅት ያደርጋሉ ማታ ማታ ማስጨፈር ነው፡፡ የኢህአዴግ አባል ካልሆንክ ምንም ችግር ቢደርስብህ የሚደርስልህ የለም፡፡ አባል ለመሆን ብር ክፈል ትባላለህ፡፡ መታወቂያ ትይዛለህ፣ የአማራ፣ የትግራይ፣ የኦሮሞ፣ የደቡብ…ልማት ማህበር አባል ለመሆን ነው ይሄ ሁሉ….ምዝገባ ክፍያ…መንግስት  ነኝ ብለው ስልጣን ላይ የተፈናጠጡት ሰዎች መቼ ይሆን ከዜጋቸው መብት ይልቅ ገንዘብ ማስቀደም የሚተዉት? መቼ ይሆን እንብላው እንብላው…ገንዘብ አምጡ አምጡን የሚተዉት? አሁንማ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደድሮው ፌደራል ፖሊስ መጣ ሲባል ሳይሆን የሚፈራው ለዚህ ነገር መዋጮ ሆኗል ፍርሃቱ…
                    ቸር ያሰማን እሰኪ…

No comments:

Post a Comment