Translate

Monday, December 18, 2017

ኦህዴድ በህወሓት ላይ ላወጣው መግለጫ ሃይለማርያም ምላሽ ሠጠ


በጨለንቆ በተፈፅመው የጅምላ ግድያ በስተጀርባ ማን ነው ያለው ? 
የኢፌዲሪ ህገ-መንግስት አንቀፅ 87 (3) ስር የአገር መከላከያ ሰራዊት የአገርን ሉዓላዊነት ለማሰከበር ነው የተቋቋመው። በዚሁ ንዑስ አንቀፅ 4 እና 5 ስር የአገር መከላከያ ሰራዊት በማንኛውም ጊዜ ለህገመንግስቱ ታዛዥ በመሆን ለፖለቲካ ፓርቲዎች ውግንና ሳያሳይ ነፃ ሆኖ የአገር ደህንነት የመጠበቅ ስራውን እንደሚሰራ ይደነግጋል። ይሄው የመከላከያ ሰራዊቱ ከውጭ የሚመጣውን የአገሪቱን ጠላት ለመከላከል በአገሪቱ ብሄር ብሄረሰቦች የተገነባ ከተቋቋመለት አላማ ውጭ ታሪካዊ ስህተቶችን በህዝቦች ላይ ሲፈፅም ታይቷል።
የህገ-መንግስቱ አንቀፅ 8 (1-5) ስር የአገሪቱ ህዝቦች ሉዓላዊነት አስመልክቶ የአገሪቱ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦና ህዝቦች የኢተዮጵያ ሉዓላዊ የስልጣን ባለቤት መሆናቸው ይደነግጋል። ይህ ህገ-መንግስት የአገሪቷ የሀጎች ሁሉ የበላይ ሆኖ ባለበት ሁኔታ የስልጣን ባለቤት የአገሪቷ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦና ህዝቦች ሆኖ እያሉ በማንኛው የአገሪቱ ባለስልጣን ውሳኔ ወይንም በማንኛውም የመንግስት አካል ወሳኔ ከህገ-መንግስቱ ጋር የሚጋጭ ተግባር በፈፀም በማይቻልበት ሁኔታ የአገሪቱ መከላከያ ሰራዊት ከተሰጠው የስልጣን ገደብ ጥሶ ህዝቡ ውስጥ በመግባት ጉዳት እያደረሰ ይገኛል።
ለዚህ መልካም ማሳያ የሚሆን ጥቂት ሀላፊነት በጎደላቸው የመከላከያ ሰራዊት አባላት በምስራቅ ሀረርጌ ዞን በሜታ ወረዳ በጨለንቆ ከተማ በኦሮሞ ህዝብ ላይ የተፈፀመ ዘግናኝ የጅምላ ፍጂት ነው። ከዚህ ጅምላ ፍጂት በስተጀርባ ማነው? ያለው የሚለው ጥያቄ ለህዝቡ መመለስ ግዴታ ነው። ከዚህ አፀያፊ ድርጊት በስተጀርባ ያለ ሃይል ሊጋለጥ ይገባል።
ለህግም መቅረብ ይኖርበታል። በአገራችን ህገ-መንግስት መሰረት የመጨረሻው የመከላከያ ሰራዊቱ አዛዥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ነው። እንደዚህ አይነት ወንጀሎች ሲፈፀሙ ከእውቅናው ውጭ ከሆነ መርምሮ የማስተካከያ እርምጃ መውሰድ የሚገባው ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ይህንን ከማድረግ ፋንታ ተመሳሳይ ወንጀሎች በሚፈፀሙበት ወቅት ዝምታን መምረጥ ለሚፈፀመው ወንጀል እውቅና መስጠቱን ያሳያል።
የመከላከያ ሰራዊቱ የኦሮምያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ወደክልሉ እንዲገባ ጥሪ ባላደረገለት ሁኔታ የክልሉን ህዝብ የሉዓላዊ ስልጣኑ ባለቤትነት መብት በመግፈፍ የፈፀመውና እየፈፀመ የሚገኘው ወንጀል የአገሪቱን ህገ-መንግስት በግልፅ የጣሰ ነው። ይህንን ስንል የመከላከያ ሰራዊቱ በሙሉ የዚህ ችግር ሰለባ ናቸው ማለታችን ሳይሆን የህዝቡ ወገንተኝነት ያላቸው የመከላከያ አባላት እንዳሉ ሁሉ ጥቂት የሰራዊቱ አባላት ግን ሆን ብለው ህዝቡ ላይ ጉዳት እያደረሱ መሆናቸው በግልፅ እየታየ ነው።
በመሆኑም የህዝቡን ደህንነትና ሰላም ከማስጠበቅ ፋንታ የህዝቡን ሰላም እያደፈረሱና ጉዳት እያደረሱ ያሉ የሰራዊቱ አባላት ለህግ ሊቀርቡ ይገባል። የህግ የበላይነት እንዲከበር የሚመለከተው አካላት ሁሉ ካልተንቀሳቀሰ ነገም ተመሳሳይ ችግር መከሰቱ የማይቀር ነው። የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስትም በዚህ ደረጃ ትኩረት ሰጥቶበት የመፍትሄ አቅጣጫ በማስቀመጥ እየሰራ ይገኛል።
የመከላከያ ሰራዊቱ የቆመለትን አላማ በመዘንጋት ያለሙያው በህዝቡ ውስጥ በመግባት ማወክ የማንን አላማ ከግብ ለማድረስ እንደሆነ ተለይቶ መታወቅ አለበት። የፌዴራል መንግስትና የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ይህንን አሰቃቂ ወንጀል የፈፀሙትን የሰራዊቱ አባላትእና ከበስተጀርባ ሆነው ያቀዱትን ለህግ ለማቅረብ እየሰሩ ይገኛሉ። የሚደረስበት ውጤትም ለህዝቡ ይፋ ይደረጋል።
የክልሉ የጸጥታ አካላትም የክልሉን ህዝብ ሰላም ለማስከበር ማንኛውንም አይነት መስዋዕትነት ለመክፈል ከማንኛውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆን አለባቸው። ህዝቡ አላስፈላጊ መስዋዕትነት እንዳይከፍል በመረጋጋትና በጥንቃቄ ሊንቀሳቀስ ይገባል። ከሁሉም በላይ መደማመጥና በአንድነት መንቀሳቀስ እጅግ ወሳኝ ነው።
የኦሮሞ ህዝብ ላቀረበው የመብት ጥያቄ፣ መብቱን በሰላማዊ ትግል ለማስከበር ስለተንቀሳቀሰ በቀዬው ላይ በጅምላና በተናጠል የመገደል፣ ከሚኖርበት አከባቢ የመፈናቀልና ሽብር ሊፈፀምበት አይገባም። የኦሮሞ ህዝብ ትናንት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስከበር ደሙን የከፈለና አገሪቷ ሉዓላዊነቷን ጥብቃ ለዛሬ እንድትበቃ ከሌሎች ህዝቦች ጋር በመሆን የተጠየቀውን ዋጋ ሁሉ የከፈለ ህዝብ ነው። የአገሪቷ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ትናንት ያንን ሁሉ መስዋዕትነት የከፈሉት ለዚሁ አገር አንድነት፣ ሰላምና ብልፅግና ነው።
ዛሬም ጥቂት የመከላከያ ሰራዊቱ አባላት ህዝቡ የጣለባቸውን ሃላፊነት በመዘንጋት ሰላማዊውን ህዝብ በቀዬው ላይ መግደል አስነዋሪ ነው። በመሆኑም ይህንን ወንጀል የፈፀሙትን አካላት ለህግ ማቅረብ ያስፈልጋል። ይህንን ለማድረግ በአንድ ባንዲራ ስር አብረን ለምንኖር የአገሪቱ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች አንድነትና ድጋፍ ጊዜው አሁን ነው። በጨለንቆ በተፈፀመው የጅምላ ግድያ በስተጀርባ ማን ነው ያለው? ለሚለው ጥያቄ ህዝቡ በግልፅ መልስ ሊያገኝ ይገባል።
የኦሮሚያ ኮሙኒኬሽን ቢሮ

የኃይለማርያም ደሳለኝ መግለጫ
የተከበራችሁ የአገራችን ሕዝቦች- እንደምን አመሻችሁ
በቅርቡ በተለያዩ የሐገራችን አካባቢዎች በተከሰቱ ግጭቶች ምክንያት የሐገራችንን ሰላም እና መረጋጋት የሚያውኩ ችግሮች ታይተዋል።
በተከሰቱት ግጭቶች ምክንያት የሰው ህይወት ጠፍቷል፤ ዜጎች ከመኖሪያ ቀያቸው ተፈናቅለዋል፤ የህዝብ ሐብት እና ንብረት ወድሟል፤ እጅግ የምሳሳለትን የሰላም፤ የልማት እና የዴሞክራሲ ስርዓት ግባንታ ሥራችንን የሚጎዱ ችግሮች ተከስተዋል።
በተለይም በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች ግጭት መከሰቱ ይታወቃል።
የፈዴራል መንግሥት ከሁለቱ የክልል መንግሥታት ጋር በቅርበት በመሥራት ችግሩ እንዲቀረፍ ያለሰለሰ ጥረት በማድረግ ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ ጉዳዩ እልባት ወደ ሚያገኝበት ምዕራፍ በመሸጋገር ላይ ነበር።
ሆኖም በቅርቡ ግጭቱ እንደገና ያገረሸ ሲሆን በነጹሀን ዜጎቻችን ላይ የሞት፣ የአካል ጉዳትና የሐብትና ንብረት ውድመት በማስከተል ላይ ይገኛል።
በምዕራብ ሐረርጌ በድሮሎቢ ወረዳ በጋድሌ ቀበሌ ለደህንነታቸው ሲባል በአካባቢው በአቅራቢያ በሚገኝ ፖሊስ ጣቢያ ተጠልለው በነበሩ የኢትዮጵያ ሶማሌ ተወላጆች የጅምላ ግዲያ ተፈጽሞባቸዋል።
በራሴና በፌዴራል መንግሥት ስም በንጹሐን ዜጎች ላይ በደረሰው አዳጋ የተሰማኝን ጥልቅ ሐዘን እየገለጽኩ ለተጎጅዎቹ ቤተሰቦች፣ ዘመድ አዝማድና ለመላው የአገራችን ህዝቦች መጽናናትን እመኛለሁ።
መንግሥት ድርጊቱን እያወገዘ ጉዳዩን የሚያጣራ ግብረ ኃይል ያቋቋመ መሆኑን ለመግለጽ እወዳለሁ፤ የማጣራቱ ሂደት እንደተጠናቀቀም አስፈላጊውን እርምጃ የሚወሰድ ሲሆን የማጣራት ሂደቱን ውጤት ለሕዝቡ በዝርዝር እንደምንገልጽ ከወዲሁ ለማሳወቅ እፈልጋለሁ።
በተመሳሳይም በጨለንቆና ሌሎች አካባቢዎች በተከሰቱ ግጭቶች ሳቢያ በአካቢወ በሚኖሩ የኦሮሞ ተወወላጆች ላይ የሞትና መየቁሰል አደጋ አጋጥሟል።
በድጋሚ በመንግሥትና በራሴ ስም በዜጎቻችን ህልፈተ ሕይወት ምክንያት የተሰማኝን ጥልቅ ሐዘን እየገለጽኩ ለተጎጂዎቹ ቤተሰቦች፣ ዘመድ አዝማድና ለመላ የአገራችን ህዝቦች መጽናናትን እመኛለሁ።
የጸጥታ ኃይሎቻችን መንግሥት ግጭቶች ባሉባቸው አካባቢዎች ሰላዊን እንዲያረጋግጡ ተልዕኮ ሰጥቷቸው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፤ የጨለንቆን ግጭት ጨምሮ ተልዕኳቸውን እየፈጸሙ ባሉበት ወቅት ያጋጠሙ ክፍተቶች ካሉ አሰራሩን ተከትሎ መንግሥት የሚጣራ ሲሆን የማጣራቱ ሂደት እንደተጠናቀቀም ውጤቱን ለሕዝቡ በዝርዝር ይፋ የምናደርግ መሆኑን ለመግለጽ እወዳለሁ።
በተጨማሪም በአማራ፣ በትግራይ እና በኦሮሚያ ክልሎች በሚገኙ አንዳንድ የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት፤ እንዲሁም በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች በተለያዩ ጊዜያት በተከሰቱ ግጭቶች ሳቢያ ክቡር የሰው ህይወት መጥፋቱ፤ ዜጎች ከመኖሪያ ቀያቸው መፈናቀላቸው እና የዜጎች ሐብት እና ንብረት መውደሙ ብቻ ሳይሆን፤ ችግሩ በፍጥነት ካልተወገደ እንደ ሐገር አሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ ሊጥለን የሚችል ነው።
በመሆኑም፤ በምሥራቅ ሐረርጌ፣ በቦረና፣ በጉጂና በባሌ የተለያዩ አካባቢዎች እና በቅርቡም ጨለንቆ አካባቢ በተከሰተው ግጭት፤ እንዲሁም በአዲግራት፣ በወለጋ፣ በደብረ ታቦር፣ በወልድያ፣ በባህርዳር፣ በጎንደር እና በአምቦ ዩኒቨርስቲዎች በተከሰቱ ግጭቶች ሳቢያ በተማሪዎች የአካል ጉዳት መድረሱ እና በአንዳንዶቹም የሰው ህይወት መጥፋቱ በእጅጉ አሳዛኝ ነው።
በዚህ አጋጣሚ ህይወታቸውን ባጡ ተማሪዎች የተሰማኝን ጥልቅ ሐዘን እየገለጽኩ ለተማሪ ወላጆችም መጽናናትን እመኛለሁ።
ባለፉት ሃያ አምስት ዓመታት ትምህርትን በፍትሐዊነት ለማዳረስ እና የተማሩ ዜጎችን ቁጥር ለማሳደግ የሚያስችሉ በርካታ ሥራዎች ተሰርተዋል፤ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ከ50 በላይ ዩኒቨርስቲዎች ተገንብተው፤ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ገብተው ትምህርታቸውን መከታተል የሚችሉበት ሁኔታ ተፈጥሯል።
እነዚህ የሐገር ተስፋ ተደርገው የሚታዩ የትምህርት ተቋማት የሚታዩ አስተዳደራዊ ችግሮችን እና ተማሪዎች የሚያነሷቸውን ሌሎች ችግሮችን በማዳመጥ መፍትሔ ለማስቀመጥ የተለያዩ ጥረቶችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት በተጠቀሱት ዩኒቨርስቲዎች ተከስቶ የነበረው ችግር የክልል እና የፌዴራል መንግስታት፤ እንዲሁም የየዩኒቨርስቲዎች አመራሮች እና የየአካባቢው የመስተዳድር አካላት፤ ከተማሪዎች፣ ከሐገር ሽማግሌዎች፣ የሐይማኖት መሪዎች እና የጸጥታ አካላትን ባሳተፈ ሁኔታ ችግሩ ተወግዶ፤ ሁኔታዎች ተረጋግተው የመማር ማስተማር ሂደቱ እንዲቀጥል ለማድረግ ተችሏል።
በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተፈጠረውን ይህን ችግር ሙሉ ለሙሉ ለማስወገድ መንግስት የተለያዩ እርምጃዎችን ወስዷል።
ችግር በተፈጠረባቸው የትምህርት ተቋማት በተማሪዎች ዘንድ የተፈጠረውን የደህንነት ሥጋት ለማስወገድ እና ለመማር ማስተማሩ ሂደት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር በተቋማቱ የሰዓት እላፊ ገደብ እንዲኖር፣ የተቋማቱን ሰላም ለማስከበር የጸጥታ ኃይሎች ጥበቃ እንዲኖር ተደርጓል።
በአጠቃላይ በክፍተኛ ትምህርት ተቋማትም ሆነ በሌሎች አካባቢዎች የጸጥታ መደፍረስ ችግር አንዳይኖር፤ የዜጎች ህይወት ዋስትና እንዲያገኝ እና በዜጎች ሐብት እና ንብረት ላይ የሚደርስ ውድመት እንዳይኖር ለማድረግ አስፈላጊው ሁሉ ይደረጋል።
በተለያዩ አካባቢዎች በሚገኙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንዲሁም በኦሮሚያ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልላዊ መንግስት አዋሳኝ አካባቢዎች የተከሰቱት ግጭቶች የሰላም፣ የልማት እና የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ትግላችንን የሚጎዱ፤ ሐገረችንን ወዳልተፈለገ አለመረጋጋት ውስጥ የሚከቱ እና በመራራ ትግል የተገኘውን ብሩህ ተስፋ የሚያጨናግፉ ክስተቶች ናቸው፤ ለዘመናት የቆየ የአብሮ መኖር እሴቶቻችን የሚጎዱ ችግሮች በመሆናቸው መንግስት ከሕዝቡ ጋር በመሆን ችግሮቹን በማያዳግም ሁኔታ ለመፍታት በቁርጠኝነት ይሰራል።
ለዘመናት በድህነት የኖረውን ህዝባችንን ከድህነት አረንቋ ለማውጣት እና ከኋላ ቀርነት ለማለቀቅ፤ እንዲሁም የሰላም፣ የልማት እና የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ጥረታችን ለማጠናከር በማሰብ፤ በከፍተኛ ወጪ በተለያዩ የሐገሪቱ አካባቢዎች የተገነቡት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፤ የሐገራችንን ህዝብ ችግር ለመፍታት በጥናት እና ምርምር ዘርፍ ተሰልፈው የበኩላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ ታስበው ከፍተኛ ገንዘብ ፈሶባቸው የተቋቋሙ ናቸው።
በመሆኑም በእነዚህ ተቋማት ገብተው የሚማሩ እና ሐገሪቱ በከፍተኛ ተስፋ የምትጠብቃቸው ተማሪዎች ምክንያታዊ አስተሳሰብን በመከተል፣ ከግጭት በመራቅ ለሐገራቸው ተስፋ ይሆኑ ዘንድ ለትምህርታቸው ልዩ ትኩረት ሰጥተው ጠንክረው መማር ይኖርባቸዋል።
በሌላ በኩል፤ መረጃን በማሰራጨት ተግባር የተሰማሩ የተለያዩ አካላት የሚያሰራጯቸውን መረጃዎች ትክክለኛነት ለማረጋገጥ ልዩ ትኩረት መስጠት እና በኃላፊነት መንፈስ መሥራት ይጠበቅባቸዋል።
በተጨማሪም ህዝቡ ከተለያዩ የመረጃ ምንጮች የሚያገኛቸውን መረጃዎች ትክክለኛነት ለማረጋገጥና መረጃዎቹን በተለያየ አግባብ ለማጣራት የበኩሉን ጥረት ማድረግ ይኖርበታል።
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ በመደበኛው የሚዲያ ዘርፍም ሆነ በሌሎች የመረጃ ማሰራጫ አግባቦች በመጠቀም መረጃን የሚያሰራጩ ተቋማት ህግን አክብረው ሊንቀሳቀሱ ይገባል።
ሐሰተኛ እና የተጋነኑ መረጃዎችን በማሰራጨት የህዝቡን ሰላም፣ ደህንነት እና አኩሪ የአብሮ መኖር እሴቶች የሚንዱ እና ህግን በሚያስተላልፉ የግልም ሆነ የህዝብ የመገናኛ ብዙሃን ከዚህ መሰል ተግባራት መራቅ ይኖርባቸዋል፡፡
መንግስት እንዲህ ያሉ ችግሮችን በሚፈጽሙት ላይ ተከታትሎ እርምጃ የሚወስድ መሆኑም በግልጽ መታወቅ ይኖርበታል።
የኢፌዴሪ መንግሥትና ገዢው ፓርቲ በአገራችን በተለያዩ ቦታዎች እያጋጠሙ ያሉትን ግጭቶች መሰረታዊ መንስኤን በመለየት ችግሩን ከሥር መሰረቱ የሚፈታ እርምጃ የሚወስድ ሲሆን መላ የአገራችን ሕዝቦችም እንደ ወትሮው ከመንግሥት ጎን በመቆም ያልተቆጠበ ድጋፋችሁን እንዲትቸሩን በመንግሥትና በራሴ ስም ጥሪዬን አስተላልፋለሁ።
በተለይም ግጭቱ በሚከሰትባቸው የኦሮሚያና የኢትዮጰያ ሶማሌ ክልል ነዋሪ የሆኑት ወንድማማች ሕዝቦች ለሰላምና ለወንድማማችነት ቅድሚያ በመስጠትና ለግጭት ጥሪዎች ጆሮ ዳባ ልበስ በማለት በጋራ በመንቀሳቀስ ሰላማቸውን እንዲያስከብሩ በኢፌዴሪ መንግሥት ስም ጥሪዬን እያቀረብኩ የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥታት በቅንጅት ችግሩን ለመቅረፍ በመረባረብ ላይ ይገኛሉ።
በድጋሚ በተለያዩ አካባቢዎች ባጋጠሙ ግጭቶች ሳቢያ በዜጎቻችን ላይ በደረሰው የሞት አደጋ የተሰማኝን መራር ሐዘን እየገለጽኩ፣ ለመላ ቤተሰቦቻቸው፣ ዘመድ አዝማዶቻቸውና ለአገራችን ሕዝቦች መጽናናትን እመኛለሁ።
ታህሳስ 8/2010 ዓ.ም /ኤፍቢሲ/

No comments:

Post a Comment