Translate

Thursday, February 25, 2016

ኣድርባይ በበዛበት ዘመን ታማኝ ለኣላማው ፥ ታማኝ ላ’ገሩ ( ሄኖክ የሺጥላ )

ስለ ኢትዮጵያዊነት የማውቀን ፅፌያለሁ ፥ እፅፋለሁ ። ሃገር ማለት እንዲህ ማለት ነው ብዬ በኣጭር ቋንቋ መግለፅ ግን እስከዛሬ ኣልቻልኩም ፥ ወደፊትም ኣልችልም ፥ ለመቻልም ኣልሞክርም ! ምክንያቱም ሃገር የሚለው ሃሳብ ከመንፈስነትም ፥ ከእምነትም ፥ ከምንነትም በላይ ነውና ። ሃገር እንደ ኣንድ ትልቅ የሰውነት መሃፀን ነውና ፥ ረቂቅም ነውና ።

«ሀገር ረቂቅ ነው ቃሉ
ሀገር ውስብስብ ነው ውሉ »
ያለው ባለ ተባ ብእሩ በድሉ ዋቅጂራ ለዚያም ኣይደል ?
ሃገሬን ሳስብ ፥ የሃገሬ ጀግኖች ትዝ ይሉኛል ፥ የሃገሬ ጠላቶች በቁጭት ጥርሴን እንዳፋጭ የሚያደርጉኝን ያህል ፥ ለሃገሬ ጠበቃ ሆነው የሚሟገቱላት ፥ የሚሞቱላት ሰዎች ሳስታውስ ደሞ ጉልበት ኣገኛለሁ ፥ ለመንፈሴ ስንቅ ፥ «ለመንገዴ መብራት » የሚሆነኝ በነዚህ ሰዎች ልብ ውስጥ የተፃፈው ማንነት ነው ። እርግጥም ሃገር ውስብስብ ነው ቃሉ ።

ስለ ሃገሬ ሳስብ ፥ ኣድር ባዮች እንደ ኣሸን በፈሉበት ዘመን ፥ ሆድ ኣደሮች በሚርመሰመሱበት እለት ፥ ላገራቸው ራሳቸውን ፥ ህይወታቸውን የሰጡትን ሰዎች በማሰብ ፥ በማስታወስ ነው የምኖረው ። ሩቅ ኣሻግሬ ታሪካቸውን ከታሪክ ክታብ ቀፍፌ ፥ ኣሉላ ፥ ባልቻ እንደምለው ሁሉ ፥ ቴዎድሮስ ፥ ራስ ጎበና ብዬ እንደምመካ ሁሉ ፥ በዘመኔ የተፈጠሩ ፥ ከኔው ጋ የሚኖሩ ጎበናዎችንም ሳስብ ልቤ በደስታ ይሞላል ፥ ነብሴ ሃሴትን ያደርጋል ። ኣዎ ታማኝ በጠፋበት ዘመን ታማኝ ላገሩ ፥ ለወገኑ ተጠሪ እና ተቆርቋሪ መሆን ምንኛ መታደል እንደሆነ ሳስብ ፥ ከፍቅር ያለፈ መንፈሳዊ ቅናት ሰውነቴን ይወረዋል ። ዛሬ ስለ ታማኝ በየነ ትንሽ ልፃፍ
ታማኝን የማውቀው ልጅ ሆኜ ነው ። ቤተሰቦቼ ታማኝን ደጋግመው የሚያነሱበት ሁለት የታሪክ ኣጋጣሚዎች ነበሩ ። ኣንደኛው በፈረንጆች ኣቆጣጠር በ 1996 ( ወይም በ 1988 ) በኣዲስ ኣበባ በመስቀል ( ኣብዮት ) ኣደባባይ ላይ ባደረገው ንግግር ሲሆን ፥ ሁለተኛው ደሞ ቆየት ብሎ በ 1996 በኢትዮጵያን ኣቆጣጠር በለቀቀው ኣንድ የለበጣ እና የተግሳፅ ሲዲ ነው ። ኣያቴ ስለታማኝ ብዙ ጊዜ ሲናገሩ እሰማ ነበር ። ልክ ይሁን ወይ ኣይሁን ባላውቅም « የደብረታቦር ኣንበሳ » በማለት ሲያሞካሹት ሰምቼለሁ ። ምናልባት ኣያቴ ይህንን ያሉበት ምክንያት ታማኝን በደንብ ካለማወቅ ይሆናል ። ምክንያቱም ታማኝን ስረዳው እና ሳውቀው የኢትዮጵያ ኣንበሳ የሚለው የተሻለ ሊገልጠው እንደሚችል ስለተረዳሁ ።
ታማኝ የኢትዮጵያዊነት ኣድባር ( ቆሌ ) ያረፈበት ሰው ነው ። በዘመኔ እንደሱ ኣይነት ባለ ሰፊ ትከሻ ሰው ብዙ ኣልውቅም ። ታማኝ ልቡ ንፁህ ነው ፥ እያንዳንዱ የነብሱ ክር በኢትዮጵያዊነት የተፈተለ ሰው ነው። ከልጅነት እስከ እውቀት ስላገራቸው ሲጮሁ ፥ ሲያለቅሱ ፥ ሲቆጩ ፥ ሲቆረቆሩ ከማውቃቸው ሰዎች ውስጥ ታማኝ ከፊት ከሚቆሙት ጥቂት ሰዎች ውስጥ ኣንዱ ነው ። ለታማኝ ኢትዮጵያዊነትን ለድርድር የምታቀርብለት ጉዳይ ኣይደለም፥ ኣይሆንምም !!! በንዋይ ፥ በምቾት ፥ እና መሰል ወጥመዶች ተፈትኖ ያልወደቀ ማነው ብትሉኝ ኣሁንም ከጥቂቶቹ ኣንዱ ታማኝ ነው ። ለሸፋፋ ኣጋጣሚዎች ያልተንበረከከ ፥ ለመርዘኛ መሰናክሎች እጁን ያልሰጠ ፥ እንደ እስስት የማይለዋወጥ ባለ ወጥ ቁመና ኢትዮጵያ ማነው ብትሉ መልሱ ብዙም ግር ኣይልም ፥ ታማኝ ነው! ታማኝ ምሳሌያችን ነው ፥ ታማኝ ኣስተውሎ ለተመለከተ ፥ እውነት ተውኔት በሆነባት ሃገር የማንነት ኣድባራችን ነው ፥ የፅናት ምኩራባችን ነው ፥ የኣልገዛም ባይነት ታሪካችንን ይዞ ያቆየልን ተንቀሳቃሽ የታሪክ ሙዚየምም ጭምር ነው ። ታማኝ እውነተኛው ወንድም ጋሻችን ነው ፥ ኣንገት መድፋት ስልጣኔ በሚመስልበት ሃገር ፥ ባርነት መዋረድ መሆኑን ፊት ለፊት ውጥቶ የተናገረ ፥ ጎጆ መቀለስ ቁም ነገሩ የሆነበት ምሁር በበዛበት ሃገር ሃገር መቀለስ የተሻለ እንደሆነ የመሰከረልን የነብሳችን ቃል ፥ የልቦናችን ፅሁፍ ነው ታማኝ ! ታማኝ ህልውናችን ነው ፥ ታማኝ የሃገራዊ እምነታችን ኣትሩኖስ ነው ፥ የነፃነታችን መቅረዝ ነው ፥ የኣልገዛም ባይነታችን ብርሃን ነው፥ ሰይፋችን ነው ታማኝ ፥ የዘራያቆብ ኣይነት የሰው ጎራዴ! በታማኝ ውስጥ ኢትዮጵያን ታያለህ ፥ በታማኝ ፍቅር ውስጥ ምህረት እና ሩህሩህነትን ትመለከታለህ ፥ በታማኝ ውስጥ የቀደሙ ኣባቶቻችንን መንፈስ ታያለህ ። ምንኛ መባረክ ነው ? ምንኛ መታደል ነው ፥ ሰው ሆኖ መኖር መቻል?
ምንኛ!
የታማኝ ኢትዮጵያዊነት ምንጩ ኣፈ ታሪክ ኣይደለም ፥ የታማኝ የማንነት መሰረቱ ጎንደሬነቱ ላይ ኣይደለም ፥ የታማኝ ማንነት እና ምንነት ዋልታው ያለው ስለራሱ ያለው ክብር ላይ ነው ፥ ስለ ሃገሩ ያለው ስሜት ላይ ነው ፥ ስለ ህዝቦቿ ያለው ፍቅር ላይ ነው። ለታማኝ ሃገር ማለት በወንዝ ልጅነት ላይ የተመሰረተ ፥ ጎሳ ተኮር ፖለቲካን ማሾር ኣይደለም ። ለታማኝ ማንነት ማለት በቂም እነሱ ብሎ መቃወም ኣይደለም ። የታማኝ ትከሻ የጎጃም እስክስታን ፥ የኣፋር ጭፈራን ፥ የወለጋ በለው የወላይታ ውዝዋዜን የኔ እና እኔ ብሎ የተሸከመ ነው ። ታማኝ ከውሃው ማዶ፥ ከንቅፈ ክበቡ ባሻገር፥ እለት እለት የሚያያት ፥ የሚጮህላት ሃገር ኣለችው ። ታማኝ በእሳት የተቃጠሉት ፥ በኣረብ የተገረፉት ፥ በረሃብ ኣለንጋ የተገረፉት ፥ በየበርሃ ወድቀው የቀሩት ወንድሞቹን ለማንሳት ወገቡን የሰበረ ወንድም ጋሻዬ ነው !
ታማኝ እንወድሃለን! ታማኝ እናፈቅርሃለን ፥ ታማኝ የክብራችን መነሳንስ ፥ የኣልበገርም ባይነታችን ኣታሞ ኣንተ ነህ !

No comments:

Post a Comment