Translate

Tuesday, November 3, 2015

ለጥቅምት 22 ሰማዕታት የመታሰቢያ ፕሮግራም ተካሄደ (ነገረ ኢትዮጵያ)

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

The Ethiopian police massacre 2005
ምርጫ 1997 ዓ.ምን ተከትሎ ጥቅምት 22/1998 ዓ.ም በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ቀጥታ ትዕዛዝ በ‹‹ፀጥታ ሀይሎች›› በጭቃኔ ለተገደሉት ሰማዕታት እና ለቆሰሉት ኢትዮጵያውያን በሰማያዊ ፓርቲ ፅ/ቤት መታሰቢያ ተደረገ፡፡ የፕሮግራሙ ተሳታፊዎች ጥቅምት 22/1998 ዓ.ም በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የገጠማቸውን በተለይም ኢትዮጵያውያን ሲገደሉ ያዩትንና የራሳቸውን ገጠመኝም አካፍለዋል፡፡

የፕሮግራሙ ተሳታፊዎቹ የተገደሉትን በክብር መቅበር እንዳልቻሉ እና ታፍሰው በተለያዩ እስር ቤቶች መታሰራቸውን አስታውሰዋል፡፡ አዛውንቶችንና ህፃናትን በጭካኔ ተገድለው ባንክ ሊዘርፉ ነው የተባለበትና የሥርዓቱን የህግና ሞራል የማይገድበው መሆኑን ያሳየበት ነውም ብለዋል፡፡ ሥርዓቱ ካለፈው ስህተቱ ሳይማር ዛሬም ለመግደል ዝግጁ እንደሆነ መቀጠሉንም ገልፀዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ሥርዓቱ ወደ ባሰ አምባገነንነት በመግባቱም ትግሉን መቀላቀላቸውን ገልፀው፣ ዘላቂው አማራጭ የሰማዕታቱን የትግል መንፈስ ፅናት ይዞ መታገል ነው ብለዋል፡፡ እነሱ አላማ ያደረጉትን ተጉዘው በአንድነት የኢትዮጵያን እጣ ፋንታ መወሰን እንደሚገባቸውም ገልፀዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በ1997 ዓ.ም በኋላ የሥርዓቱ ሁኔታ እየተባባሰ እንደመጣና ለዚህም ዋናው ምክንያት ኢትዮጵያውያን ሥርዓቱ የሚያደርስብንን በደል ችለን ወደ ውስጥ የምናለቅስ መሆናችን ነው ብለዋል፡፡ ሥርዓቱ ይቅር የማይደረግለት ሆኖ፣ ፖለቲካው በመነታረክ መቀጠሉን ትክክል እንዳልሆነም ገልፀዋል፡፡
‹‹ሥርዓቱ ታሪክና የጋራ ነገር የላችሁም ብሎናል፡፡ መናናቅንና ሀይማኖትን ማቃለልን በተግባር አሳይቶናል፡፡ የወደፊት ኢትዮጵያ በእኛ እጅ እንድትሆን ከፈለግን የነበረውን የሀገራችን እሴት ማናናቅ የለብንም፡፡›› ያሉት ኢ/ር ይልቃል ኢትዮጵያውያን የገነቧቸው እሴቶች ሁሉ በወጣቱ ልብ ውስጥ ማደር እንዳለባቸው፣ ሰማዕታቱ የሞቱለት አላማና ኢትዮጵያውያን የገነቡት እሴት መጠበቅ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

No comments:

Post a Comment