Translate

Saturday, October 31, 2015

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የለሊቱ የቪኦኤ ሚስጥራዊ ጉባኤ (በአበበ ገላው)

በአበበ ገላው (ትርጉም በታኬ)
Tedros Adhanom and Ambassador Girma Birruበቅርቡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድኃኖም እና አምባሳደር ግርማ ብሩ በዩናይትድ ሰቴትስ አሜሪካ ዋሽንግተን ዲ.ሲ በሚገኘው የቪኦኤ ሬዲዮ ጣቢያ በሌሊት በድብቅ በመግባት ሕጋዊ ስልጣኑ ሳይኖራቸው ስለስርጭቱ ለጥቂት የድርጅቱ ሠራተኞች የኢዲቶሪያል መመሪያ ከሰጡ በኋላ በአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት (ቪኦኤ) እና በህወሀት የበላይነት በሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት መካከል ያለው የሻከረ ግንኙነት ያልተጠበቀ አቅጣጫ ይዟል፡፡ ስብሰባው በሚስጥር በተካሄደበት ጊዜ የአምባገነኑ አገዛዝ ባለስልጣኖች ለሬዲዮ ስርጭቱ ሰራተኞች ስለዜና አዘጋገብ፣ እንደዚሁም ደግሞ ወደ ኢትዮጵያ ስለሚተላለፈው የስርጭት ጥራት ሁኔታ መመሪያ የመስጠት ሙከራ ያደረጉ ለመሆናቸው ከታመኑ ምንጮች በተገኙ መረጃዎች ተረጋግጧል፡፡

ከቪኦኤ ባለስልጣኖች ዕውቅና ውጭ በሚስጥር እንዲከናወን የተደረገው ይህ ስብሰባ የተካሄደው በዋሽንግተን ዲ.ሲ 330 ኢንዲፔንደንስ አቬኑ በሚገኘው በቪኦኤ የአፍሪካ ቀንድ ክፍል የኢዲቶሪያል የስብሰባ ቢሮ ውስጥ ነው፡፡ ይህ ድብቅ ስብሰባ እንዲካሄድ የተደረገው ባልተለመደ እና እንግዳ በሆነ መልኩ በሰንበት፣ እ.ኤ.አ መስከረም 26 ቅዳሜ ዕለት ከስራ ሰዓት ውጭ ከምሽቱ 1 ሰዓት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ድረስ ነበር፡፡
የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት ፕሮግራም ስርጭት ባልደረባ በሆነው በሰለሞን አባተ ግንባር ቀደም አደራጅ እና አስተባባሪነት እንዲሁም በአሜሪካ ድምጽ የትግርኛው ፕሮግራም ስርጭት ባልደረባ በሆነው በበትረ ስልጣን ተባባሪነት በዲፕሎማቶቹን እና ሁለት ቴክኒሸኖችን ጨምሮ ሰባት የቪኦኤ የስራ ባልደረቦችን ባካተተው ቡድን መካከል የተካሄደው ስብሰባ ተገቢነት የሌለው እና አግባብ ያልሆነ ተብሎ ተፈርጇል፡፡
አገዛዙ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ጠንካራ ትችት የሚያቀርቡትን ብዙሀን መገናኛዎች ጸጥ ለማድረግ እና የስርጭት አድማሳቸውን ለመገደብ እያራመደ ካለው አውን ያወጣ ስልት አንጻር ከፍተኛ በሆኑ የአምባገነኑ አገዛዝ ባለስልጣኖች እንደዚህ ያለ ስብሰባ መካሄዱ እና ስለቪኦኤ እያራገቡት ያለው የጥላቻ አጀንዳ በሕጋዊ መልኩ ስልጣን የተሰጠውን የመተዳደሪያ ደንብ እና የጋዜጠኝነት ስነምግባርን የሚጥስ ዕኩይ ድርጊት እንደሆነ ተደርጎ ይታሰባል፡፡
ይህ በቅሌት የታጀበ ስብሰባ እንዲካሄድ የተፈለገበት ዋናው ምክንያት አገዛዙን በየዓመቱ የፕሬስ ነጻነትን በመደፍጠጥ የቀዳሚነቱን ቦታ ከሚይዙት የፕሬስ ደፍጣጮች መካከል እያስመደበው የመጣ ስለሆነ ይህንን ሁነት ለማደብዘዝ ሲባል በጋዜጠኞች እና በጨቋኙ መንግስት መካከል መተማመን እና ትብብር እንዲኖር ለማድረግ ከመፈለግ የመነጨ ክስተት ነው፡፡ በስብሰባው ወቅት በተደረገው ንግግር የህወሀት ተወካይ ይህንን አጋጣሚ በመጠቀም ወደ ኢትዮጵያ የሚደረገውን የሬዲዮ ስርጭት ጥያቄ በማቅረብ እና በድብቅ የማስፈራሪያ ድርጊቶችን በመፈጸም በስርጭቱ ላይ ከፍተኛ የሆነ ተጽዕኖ መፍጠር እና የስርጭቱንም ይዘት ማስቀየር እንደሚቻል የቀረበውን ሀሳብ ለደህንነታቸው ሲባል አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ ሰው ይፋ አድርገዋል፡፡
እየተካሄደ የነበረው ስብሰባ ውይይት በመቅረጸ ድምጽ እንዳይቀዳ እግድ የጣለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በማያያዝም ቪኦኤ ጠንካራ የሆኑ ትችቶችን ለሚያቀርቡት የአየር ጊዜ በመስጠት እና ዓላማቸውን በኃይል ለማስፈጸም የሚንቀሳቀሱትን አመጸኞች ግንቦት ሰባትን ጨምሮ መንግስትን ለመገልበጥ ለሚደረገው እንቅስቃሴ ድጋፍ ያደርጋሉ በማለት ቅሬታውን አሰምቷል፡፡ ሚኒስትሩ በመቀጠልም ቪኦኤ “አሉታዊ ትረካ” ላይ ትኩረት በማድረግ የሚሰራ ሜዲያ ነው በማለት ቅሬታውን ገልጿል፡፡
የአምባገነን ምልከታ፣
ጥቂት ጥያቄዎችን ከወሰደ በኋላ ሚኒስትሩ ባለፈው ሐምሌ ወር ለቪኦኤ የሰጠው ቃለመጠይቅ የመንግስትን ፖሊሲ በሚተቹ ትችት አቅራቢዎች በቪኦኤ በኩል ትችት የቀረበ በመሆኑ ቅሬታ የተሰማው መሆኑን ግልጽ አድርጓል፡፡ እንደዚህ ያሉ ተሞክሮዎች ስህተት ናቸው፣ እናም መደረግ አልነበረባቸውም በማለት ለተሰብሳቢዎቹ ተናግሯል፡፡
አወዛጋቢ በነበረው የቪኦኤ ቃለመጠይቅ የህወሀት ሚኒስትር ካለው እውነታ በተጻረረ መልኩ ፕሬዚዳንት ኦባማ የኢትዮጵያ የመጨረሻው ምርጫ ዴሞክራሲያዊ ስለሆነ አጽድቆታል በማለት የተዛባ መረጃ አሰራጭቷል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ባለፈው ዓመት የመን ላይ የታፈነው እና በኢትዮጵያ ውስጥ ስቃይ እየተፈጸመበት ያለው ታዋቂው አመጸኛ አንዳርጋቸው ጽጌ መልካም የሆነ አያያዝ እየተደረገለት እንደሆነ እና እንዲያውም የልማት ፕሮጀክቶችን በማድነቅ ላይ እንደሚገኝ ይፋ አድርጓል፡፡ እንደዚሁም ደግሞ አንዳርጋቸው መጽሐፍ እንዲጽፍ ላፕቶፕ የተሰጠው መሆኑን ተናግሯል፡፡
ሚኒስትሩ እና አምባሳደሩ ሁለቱም መንግስት ከቪኦኤ ጋር ተቀራርቦ ለመስራት ያለውን ዝግጁነት እና ጋዜጠኞች አዎንታዊ ትረካ እና ስዕሎችን አጉልተው ማውጣት እንዳለባቸው እና አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ ድጋፍ እና እገዛ እንደሚያደርግላቸው ግልጽ ያደረጉ መሆናቸውን ምንጮቹ ይፋ አድርገዋል፡፡
ባለስልጣኖቹ ሰባት የቪኦኤ የስራ ባልደረቦች ያሉበትን ስብሰባ እየመሩ ባሉበት ጊዜ ሲሰጡት በነበረው መመሪያ ቪኦኤ ወደ ኢትዮጵያ በሚያስተላልፈው የሬዲዮ ስርጭት ላይ ልዩ ትኩረት አድርጎ መዘገብ ያለበት ከአሉታዊ ትረካዎች እና አስተያየቶች፣ እንዲሁም አንገብጋቢ ከሆኑ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች፣ ስልጣንን ከሕግ አግባብ ውጭ መጠቀም እና ከሙስና ይልቅ አዎንታዊ እና የልማት ስራዎችን መዘገብ እንደሚያስፈልግ አስረግጠው ተናግረዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በዚህ ብቻ ሳያቆም ንግግሩን ቀጥሎ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ተገኙ ያላቸውን ጥቂት ዕድገት እና መሻሻሎች ከዘረዘረ በኋላ ጋዜጠኞቹ እራሳቸው እውነታውን በግንባር ወደ ሀገር ቤት በመሄድ ማየት እንዳለባቸው የግብዣ ጥሪ አስተላልፎላቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ስለቪኦኤ ውስጣዊ የስራ እንቅስቃሴ ቀጣይነት ባለው መልኩ መረጃ እንደሚቀበል ቀጥታ ባልሆነ መንገድ ይፋ አድርገዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ለጋዜጠኞቹ በየስራ ክፍሎቻቸው ማን ምን እንደሚሰራ እያንዳንዱን ነገር እንደሚያውቁ እና እነዚህ ጋዜጠኞችም ከዚህ አንጻር እራሳቸውን እንደገና በጥንቃቄ መመርመር እንዳለባቸው በይፋ የተናገረ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
አንድ ስሙ እንዳይታወቅ የፈለገ የስብሰባው ተሳታፊ የሆነ የቪኦኤ የስራ ባልደረባ እንዲህ በማለት ሀሳቡን ገልጿል፣ “በእንደዚህ ዓይነት ስራዎች ላይ ልንከተላቸው የሚገቡ ሕጎች፣ የአሰራር ሂደቶች እና የሙያ ስነምግባሮች አሉ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ምሽት ከመሆኑ አንጻር ሰራተኛው ሁሉ ለመኝታ ወደየቤቱ በሄደበት ሁኔታ አንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በድርጅቱ ኢዲቶሪያል ክፍል ውስጥ በመገኘት ጥቂት የድርጅቱ ሰራተኞችን በመያዝ እንደዚህ ያለ ስብሰባ ማካሄድ በድርጅቱ ታሪክ ውስጥ ተደርጎ የማያውቅ አዲስ እና ያልተለመደ ነገር ነው“ በማለት ሀሳቡን ግልጽ አድርጎ አቅርቧል፡፡ ምንጩ ከዚህ ጋር በማያያዝ እንደገለጸው የአሰራር የዕዝ ሰንሰለቶችን በመጣስ የቪኦኤን ነጻነት በገደበ መልኩ እየተካሄደ ባለው በዚህ ስብሰባ ላይ እኔ እና መሰል ባልደረቦቼ በእጅጉ አዝነናል የሚል መልዕክት እንዳስተላለፈ ምንጮች ዘግበዋል፡፡
የስብሰባ ምንጮች እንዲህ የሚል ግልጽ የሆነ መልዕክት የተላለፈ መሆኑን ጠቁመዋል፣ “ስለቪኦኤ የአዘጋገብ ፕሮግራም እና ስለሌሎች ማናቸውም ጉዳዮች ለመወያየት እና ቅሬታን ለማቅረብ ሲፈለግ ባለስልጣኖች የኢዲቶሪያል ስብሰባ ለማድረግ የዩኤስ ፌዴራል መንግስት ሰራተኛ የሆኑትን የተመረጡ ጥቂት የቪኦኤ ጋዜጠኞች ቡድንን በምሽት ስብሰባ ከመጥራት ይልቅ የተለመደውን የአሰራር ስርዓት እና የዕዝ ሰንሰለት መከተል ነበረባቸው“ ብሏል፡፡
ሌላው ምንጭ በመቀጠል ከተሰብሳቢዎች የቀረበውን እንዲህ የሚለውን አስተያየት ይፋ አድርጓል፣ “እኛ ለቪኦኤ የምንሰራ ነጻ ጋዜጠኞች ነን፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ወይም አምባሳደሩ ወደ ቪኦኤ ዘልቀው በመምጣት ስራዎቻችንን እንዴት መስራት እንዳለብን የሚያስገድዱን ወይም ደግሞ መመሪያዎችን የሚሰጡን ለምንድን ነው? ይህ ዓይነት አካሄድ አግባብነት የሌለው የሙያ ጣልቃገብነት ጉዳይ ብቻ አይደለም፣ ሆኖም ግን ይህ ጉዳይ በእኛ የማሰብ ችሎታ እና ሙያዊ ብቃት ላይ የተሰነዘረ ግልጽ ዘለፋ ነው“ ብሏል፡፡ ይኸው ምንጭ፣ “ቪኦኤ ያለምንም ፍርሀት እና ከምንም ዓይነት አድልኦ በጸዳ መልኩ የመስራት ተግባሩን መቀጠል እንዳለበት ጠንካራ እምነት አለኝ“ ብሏል፡፡
ቪኦኤ እንደ ነጻ የሜዲያ ተቋም በትክክለኛ እና በእውነት ላይ የተመሰረተ ዘገባን የማቅረብ ተልዕኮን የሚያራምድ ጠንካራ የሆነ ኃላፊነትን የተሸከመ ድርጅት እንደሆነ አጽንኦ በመስጠት ግልጽ አድርገዋል፡፡ ተሰብሳቢዎቹ “ሕግን መሰረት አድርጎ የተቋቋመውን እና ሕጋዊ ስልጣን ያለውን የቪኦኤን የመተዳደሪያ ደንብ እና የሙያ ስነምግባር ማንም ድርድር ሊያደርግበት እና ሊለውጠው አይችልም“ ብለዋል፡፡ ይኸ ቅንነት የጎደለው ስብሰባ “አምባገነኑ እየተመለከታችሁ ነው“ የሚል ቀጥተኛ ያልሆነ እንደምታ ይኖረዋል በማለት ሌላው ምንጭ ጠቁሟል፡፡ ለስራ በጣም ምቹ የሆነ እና ደህንነቱ አስተማማኝ በሆነ በዚህ የፌዴራል መንግስት ህንጻ ውስጥ እንደዚህ ያለ ክስተት እንዴት እና ለምን እንደተፈጠረ ጥቂት ሰዎች በጣም ያሳሰባቸው ስለሆነ ድርጊቱ ለምን እንደተፈጸመ ሊያጣራ የሚችል አጣሪ አካል መቋቋም እንዳለበት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ባለስልጣኖቹ ለቪኦኤ የስራ ባልደረቦች የኢትዮጵያ ኤምባሲ በሮች በሰፊው ተከፍተው የቆዩ መሆናቸውን ነግረዋቸዋል፡፡ ሆኖም ግን የተወሰኑ የስብሰባው ተሳታፊዎች ባለስልጣኖቹ የመጡት በስቱዲዮ በመገኘት ቃለመጠይቅ እንዲሰጡ ነው ተብሎ የተሳሳተ መረጃ በመሰራጨቱ እና እዚህ ከገባን በኋላ እየተደረገ ያለው የኢዲቶሪያል ሕገወጥ ስብሰባ መሆኑን በመመልከቴ ወደ ስሰብሰባው ከፍል በመግባቴ ጸጸት ተሰምቶኛል በማለት ተናግሯል፡፡
የኢትዮ-አሜሪካ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት የሆኑት አበበ ኃይሉ ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ መልኩ የተሰማቸውን ሀዘን እና እምነት ማጣት እንዲህ በማለት ግልጽ አድርገዋል፣ “በአሁኑ ጊዜ በቪኦኤ ላይ እየተደረገ ያለው ድርጊት የቪኦኤን ታማዕኒነት የሚያጠፋ ስለሆነ ድርጊቱ በድርጅቱ ህልውና ላይ ያነጣጠረ በጣም አስፈሪ ሁኔታ ነው፡፡ እንደ ኢትዮ-አሜሪካውያን ዜጎች ለዚህች ታሪካዊ ለሆነች ሀገር ለዩናይትድ ስቴትስ አሜሪከ ግብር ከፋይ ሕዝቦችም ነን“ ብለው ነበር፡፡
አቶ አበበ አስተያየታቸውን በመቀጠል ቪኦኤ እና የቪኦኤ የስራ ባልደረቦች በሌላ በውጭ ኃይል ጣልቃገብነት የመጦዝ እና የመታዘዝ ዕድል እንዳይገጥማቸው የሜዴያን ነጻነት ለማስከበር ወጥተን መጠየቅ እንዳለበን ምክንያት የሚፈጥር ጉዳይ ሆኗል፡፡ በመጨረሻም ይኸ ድርጊት በጠቅላይ የምርመራ ጽ/ቤት/Inspector General መመርመር እንዳለበት ጠንካራ እምነነት አለኝ በማለት ጥቆማ አቅርበዋል፡፡
የውጥረት ታሪክ፣
በኢትዮጵያ ላይ ተንሰራፍቶ የሚገኘው አገዛዝ ከሕግ አግባብ ውጭ ግድያ በመፈጸም፣ በዜጎች ላይ ስቃይ በማድረስ፣ ስልጣንን ከሕግ አግባብ ውጭ በመጠቀም፣ በሙስና በመዘፈቅ፣ ሕዝብን በጅምላ በማፈናቀል፣ በመሬት ቅርምት ወረራ በመረባረብ፣ በዜጎች ላይ አድልኦ በመፈጸም እና በሌሎች ዓይነት ጅምላ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እና በሰዎች ልጆች ላይ በሚፈጽማቸው ሰብአዊ ወንጀሎች በሰፊው ይተቻል፡፡
እ.ኤ.አ በ2005 የተከሄደውን ሀገር አቀፍ ምርጫ ተፈጥሮ የነበረውን ውዝግብ ተከትሎ አገዛዙ በጉዳዩ ላይ የዩኤስ መንግስት ጣልቃ ገብቶ ክሱ ውድቅ እስከሚደረግ ድረስ በአራት የቪኦኤ ነባር ጋዜጠኞች ከሌሎች በርካታ ተወንጃዮች ጋር በመጨመር የሀገር ክህደት እና የዘር ማጥፋት መፈጸም የሚል የውንጀላ ክስ ተመስረቶባቸው ነበር፡፡
እ.ኤ.አ ሰኔ 2011 የቪኦኤን እና የሌሎች ዓለም አቀፍ የዩኤስ ዜና ማሰራጫዎችን የሚገመግም ሶስት አባላትን ያካተተ የሬዲዮ ስርጭቱ የቦርድ አመራሮች/Broadcasting Board Governors (BBG) ቡድን ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ሄዶ ነበር፡፡ በዚያን ጊዜ በስልጣን ላይ የነበረው አገዛዝ በቬኦኤ የስርጭት አድማስ እንዳያገኙ እና ቃለመጠይቅም እንዳይደረግላቸው የሚፈለጓቸውን ሰዎች ስም ዝርዝር እና ሌሎች አመጽ ያካሂዳሉ ብለው የፈረጇውን ድርጅቶች ዝርዝር ያካተተ ረዥም ቅሬታ አቅርበው ነበር፡፡
የቀድሞው የአፍሪካ ቀንድ የቪኦኤ ዋና ኃላፊ የነበሩት ዴቪድ አርኖልድ አገዛዙ ትችት ለሚያቀርቡት እና አመጽን ለሚያራምዱት ግለሰቦች እና ድርጅቶች ቪኦኤ መድረክ እንዳይሰጣቸው ይፈልጋል በማለት ግልጽ አድርገው ነበር፡፡ ሆኖም ግን አርኖልድ ሀሳባቸውን ግልጽ ካደረጉ በኋላ ግልጽ ባልሆነ ምክንያት ከስራቸው እንዲታገዱ ተደርገዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ2010 አሁን በህይወት የሌለው አምባገነኑ መለስ ዜናዊ ቪኦኤን ሀገሪቱን ካወደመው እና የዘር ማጥፋት ሰይጣናዊ የቅስቀሳ ድርጊት በማድረግ በመጥፎነቱ ከሚታወቀው ከሩዋንዳው ሬዲዮ ሚሌ ኮሊንስ ጋር አንድ ዓይነት ነው በማለት ድምዳሜ ሰጥቷል፡፡
ይህንንም በማስመልከት በኢትዮጵያ የሚሰራጨውን የቪኦኤን የስርጭት ሞገድ ካፈነ/ጃም ካደረገ በኋላ አምባገነኑ መለስ እንዲህ የሚል ዲስኩር አሰምቶ ነበር፣ “በብዙ መንገድ የቪኦኤ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት የመጫረሻ ዝቅተኛ የሆነውን የጋዜጠኝነት ስነምግባርን የማያሟላ እና የሁከት ፕሮፓጋንዳ የሚነዛ የሩዋንዳውን የሬዲዮ ኮሊንስን ተሞክሮ እንዳለ የሚተገብር ሜዲያ እንደሆነ ከብዙ ጊዜ ጀምሮ እምነት አድርቦብናል“ ብሎ ነበር፡፡
ይኸው የውንጀላ ክስ በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ የመንግስት መምሪያ “መሰረተ ቢስ እና ቆጥቋጭ” በሚል ውድቅ ተደርጎበታል፡፡ የአሜሪካ የመንግስት መምሪያ ለቀረበው የውንጀላ ክስ ምላሽ እንዲሆን በማሰብ ይልቁንም መንግስት የሰው ልጆች መሰረታዊ መብት የሆነውን ሀሳብን በነጻ የመግለጽ መብት እንዲያከብር ጠይቋል፡፡
የሙያ ስነምግባር መርሆዎች፣
የቪኦኤ የሙያ የስነምግባር መርሆ በግልጽ እንደሚያስቀምጠው የቪኦኤ ቋሚ ወይም ደግሞ የኮንትራት ሰራተኞች በተለዬ ምክንያት በልዩ ትዕዛዝ በተላለፈ የስልጣን ተዋረድ ካልሆነ በስተቀር ለሌላ መንግስት ወይም ደግሞ የሜዲያ ተቋም ሊያገለግሉ አይችሉም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በጨቋኝ አገዛዝ መዳፍ ስር ወድቀው ለሚሰቃዩ ህዝብች ትክክለኛ መረጃ እና ዜና በማቅረብ ረገድ ላይ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል፡፡ የቪኦኤ የጋዜጠኝነት የስነምግባር መርሆ እንዲህ በሚለው ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል፣ “ቪኦኤ በነጻነት እና በዴሞክራሲ ላይ ሙሉ እምነት እና ተስፋ ላላቸው ህዝቦች ብሄራዊ ጥቅምን ለመጠበቅ እና ለዓለም ህዝብ በተለይም ደግሞ ትክክለኛ መረጃ ለማያገኙት ህዝቦች ትክክለኛ፣ ሚዛናዊ እና የተሟላ መረጃ እንዲያገኙ ያደርጋል“ ይላል፡፡
ባለፈው ዓመት በህወሀት የበላይነት የሚመራው አገዛዝ የተሟሉ የሳቴላይት መሳሪያዎችን በመጠቀም እና ዓለም ሕጎችን በማክበር ትክክለኛ የሆኑ የአሰራር ስርዓቶችን በመከተል እና በስራ ላይ በማዋ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ መረጃዎችን እና ዜናዎችን የሚያሰራጩትን ዓለም አቀፍ ሜዲያዎች ስርጭትን ቪኦኤን ጨምሮ በማፈኑ/ጃም በማድረጉ ቢቢጂ/BBG ከቢቢሲ/BBC፣ ዶቼ ዎሌ/Deutsche Welle እና ከፍራንስ 24/France 24 ጋር በጋራ በመሆን አገዛዙ ሰብአዊ መብቶችን በሰፊው እየደፈጠጠ ነው በማለት አውግዘውታል፡፡
እነዚህ ዓለም አቀፍ የብዙሀን መገናኛ ዘዴዎች በጋራ ባወጡት መግለጫ እንዲህ የሚል ተካትቶ ይገኛል፣ “ይህ ጣልቃገብነት ዓለም አቀፍ የሬዲዮ ሞገድ የስርጭትን አጠቃቀም እና የሳቴላይት ስርዓቱ የሚመሩባቸውን ደንቦች በተጻረረ መልኩ የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብቶች ድንጋጌ አንቀጽ 19ን በመተላለፍ ግለሰቦች ነጻ የሜዲያ ሽፋን መረጃዎችን እንዳያገኙ እገዳ ጥሏል ወይም ጃም አድርጓል“ የሚል የጋራ መግለጫ አውጥተዋል፡፡
የቢቢሲ አገልግሎት ቡድን ተጠባባቂ ዳይሬክተር የሆኑት ሊሊያን ላንዶር የአገዛዙን አፋኝነት በማስመልከት እንዲህ ብለው ነበር፣ “ግልጽ ባልሆነ ምክንያት የዓለም አቀፉን የዜና ማሰራጭ አውታሮች አውከዋል፡፡“
የስትራቴጂ ለውጥ ማድረግ፣
ለጠንካራ ትችቶች እና ለሜዲያ ሽፋን ጠላት በመሆን በስልጣን ላይ ያለው አገዛዝ የቪኦኤ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት ፕሮግራምን ለሁለት አስርት ዓመታት ያህል በእራሱ ስልጣን ስርጭቱን ለማቋረጥ እና ለመዝጋት ያለ የሌለ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ይህንን ያህል ጥረት በኢትዮጵያ የቪኦኤን አጭር ሞገድ እና የሳቴላይት ስርጭት ለማፈን/ጃም ለማድረግ እንዲሁም የተለያዩ ዲፕሎማሲያዊ ተጽዕኖዎችን ሲያደርግ የቆዬ ቢሆንም ቅሉ ዓላማ አድርጎ የተነሳበትን ግብ ሳይመታ እና የታለመውን ውጤት ሳይስገኝ የውኃ ላይ ኩበት ሆኖበት ቀርቷል፡፡
እ.ኤ.አ በ2015 ዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች ተከላካይ ድርጅት/CPJ የጽሁፍ እና የሕትመት ምርመራ የሚደረግባቸውን 10 ዋና ዋና ጨቋኝ መንግስታት የደረጅ ዝርዝር ባወጣው ዓመታዊ ዘገባ ኢትዮጵያ ከኤርትራ፣ ሰሜን ኮሪያ እና ከሳውዲ አረቢያ በመቀጠል በ4ኛነት ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡ የCPJ የምርመራ ውጤት ዘገባ እንደሚያመለክተው “ከፍተኛ የሆነ የህትመት እና የሜዲያ ምርመራ ከሚያደርጉ ሀገሮች መካከል ኢትዮጵያ በ4ኛነት ደረጃ ላይ የምትገኝ በመሆኗ ምክንያት የጋዜጠኞች እስራት በገፍ የሚከናወን በመሆኑ በርካታ ጋዜጠኞች ሀገራቸውን እየተው ለመሰደድ ተገደዋል፡፡ እ.ኤአ. በ2014 በጦማሪያን እና በነጻው ፕሬስ ህትመት አዘጋጆች ላይ ከፍተኛ የሆነ የኃይል እርምጃ በመወሰዱ ምክንያት ከ30 በላይ የሚሆኑ ጋዜጦች ለስደት ተዳርገዋል፡፡“ CPJ ማንኛውንም ትችት ማቅረብ እና ሀሳብን በነጻ መግለጽ ወንጀለኛ የሚያደርገውን እ.ኤ.አ በ2009 የወጣውን የጸረ-ሽብር አዋጅ አውግዞታል፡፡
አገዛዙ ይህንኝ ያህል ጥረት እያደረገ የህወሀት የብዙሀን መገናኛ ዘዴዎችን የማፈን እና በጋዜጠኞች እና በሰላማዊ አመጸኞች ላይ የሀሰት የውንጀላ ክሶችን ቢመሰርትም ያሰበው እና የሚያደርገው ሁሉ የእምቧይ ካብ እየሆነ ፍሬ ሳያፈራ ቀርቷል፡፡ ሆኖም ግን አሁን በቅርቡ ደግሞ የእስትራቴጂ ለውጥ በማድረግ በቀጥታ ከቪኦኤ ጋዜጠኞች እና ከሌሎች ነጻ የሜዲያ ተቋማት ጋር በግንባር በመገናኘት እያደረገ ያለው ንግግር አገዛዙ ከውስጥ የግንኙነት መረብ አድማሱን እያሰፋ እና እያጠናከረ እንዲሁም ካሮት እና ዱላ እያሳየ እያስፈራራ ያለው ዕኩይ ድርጊት ያለምንም ጥርጥር በአፍሪካ ቀንድ የቪኦኤ ክፍል ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳደሩ አይቀርም፡፡ ከዚህም በላይ ከጋዜጠኝነት ስነምግባራቸው በተዛነፈ መልኩ ካሮት እየተሰጣቸው ለርካሽ ጥቅም በማጎብደድ መሳሪያ ሆነው የሚያገለግሉ ሊኖሩ ይችላሉ የሚል ግምት አለ፡፡
ቪኦኤ በሚስጥር ስለተካሄደው ስብሰባ ምንነት እና በኢትዮጵያ የቪኦኤ የሬዲዮ ስርጭት ላይ የሚኖረው አሉታዊ ተጽዕኖ ከግምት ውስጥ በማስገባት በስብሰባው ክፍልም የተደረገውን ውይይት በማስመልከት በዚህ ዘገባ አጠናቃሪ ለቀረቡለት ጥያቄዎች እስከ አሁን ድረስ ምላሽ አልሰጠም፡፡

No comments:

Post a Comment