Translate

Sunday, June 14, 2015

የስርዓቱን ብልግና ለመድነው

(ጌታቸው ሺፈራው)

sem

አሁን አሁንማ ዜና የሚሆን ነገር ጠፍቷል፡፡ መታሰር ተለምዷል፡፡ መደብደብ ተለምዷል፡፡ የሀሰት ምስክርነት ተለምዷል፡፡ ከአሁን ቀደም ‹‹ጉድ ነው!›› ያሰኙ የነበሩ ህገ-ወጥነቶች አሁን የቀን ተቀን ተግባር ሆነው ወደ ጎን እያየን እየተውናቸው ነው፡፡ በአጠቃለይ የስርዓት ነውር፣ ብልግና፣ ስርዓት አልበኝነትን ለዜናም የሚበቁ አልሆኑም፡፡ በአንድ ወቅት ‹‹እንትና ጠያቂ ተከለከለች፣ እንትና ምግብ እንዳይገባለት ተደረገ›› ተብሎ ዜና ይሰራ ነበር፡፡ እንደ ትልቅ የስርዓቱ ብልግና እና ነውርም ተደርጎ ይታይ ነበር፡፡ እንዲያውም ይህ አይነት በደል የሚፈፀምባቸው በፀረ ሽብር ህጉ ተከሰው የሚታሰሩ ኢትዮጵያውያን ብቻ ነበሩ፡፡ አሁን በሰልፍና በሌሎች ሰበቦች የሚታሰሩ ኢትዮጵያውያን ላይ ይህ በደል እየተደጋገመ ወደ ተራ አሰራርነት (የስርዓቱ ህግና ደንብ) ተቀይሯል፡፡ ነውር ቢሆንም እኛ ግን ለምደነዋል፡፡

ዛሬ በጠዋት ተነስተን ከኢ/ር ይልቃል ጌትነት ጋር ቃሊቲና ቂሊንጦ የሚገኙ እስረኞችን ለመጠየቅ አቀናን፡፡ መጀመሪያ ወደ ቃሊቲ ስንሄድ ኢ/ር ይልቃል ቃሊቲ የታሰሩትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጠያቂዎች ስም ዝርዝር ላይ ስሙ እንዳለ በማወቅ ነበር፡፡ ህገ መንግስቱ እስረኞች በዘመዶቻቸው፣ በህግ አማካሪዎቻቸው፣ በሀኪሞቻቸው፣ በጓደኞቻቸው የመጠየቅ መብት እንዳላቸው ቢደነግግም እስረኞቹ ግን ‹‹የሚጠይቃችሁን የጥቂት ሰዎች ስም ዝርዝር አስቀምጡ›› ተብለው ተገደዋል፡፡ ‹‹አይ! መብታችን ነው፡፡ ማንም ሊጠይቀን ይገባል!›› ያሉት ደግሞ ከእነአካቴው እንዳይጠየቁ ተደርገዋል፡፡ እኛ ይህንንም ስለለመድነው እስረኛ ለመጠየቅ ‹‹የጠያቂ ስም ዝርዝር ላይ ተመዝግበሃል?›› መባባል አዲስ አይደለም፡፡ ይህ ማጎሪያ ቤቶቹ ህገ መንግስቱን በአፍ ጢሙ ገልብጠው ያወጡት ‹‹ህገ አራዊት››› ነውር ቢሆንም እኛ ግን ለምደነዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶች የሚጠየቁት ከ6፡00 – 6፡30 ባለው ጊዜ ነው፡፡ በ24 ሰዓት ውስጥ ለ30 ደቂቃ ማለት ነው፡፡ ይህም ቢሆን ማረሚያ ቤቱ ያወጣው ሌላኛው ነውር ነው፡፡ ያም ሆኖ በ30 ደቂቃ ውስጥ ለመጠየቅ እንዲያውም እንዳይዘጋብን ተጣድፈን እንሄዳለን፡፡ ለዛምው እድሉን ያገኘ ‹‹ዛሬ እኮ ገባሁ!›› እያለ እንደ እድል ማውራት ሁሉ ተጀምሯል፡፡ ለ30 ደቂቃ ያህል እነ ወይንሸትን ለመጠየቅ እየተጠባበቅን ባለንበት ወቅት አንዱ መዝጋቢ እኛ የተቀመጥንበት አካባቢ ሆኖ መመዝገብ ጀመረ፡፡ ሁለት ታሳሪ ለመጠየቅ የጓጉ የሚመስሉ ወጣቶች ለመመዝገብ ቀርበዋል፡፡
‹‹ማንን ነው የምትጠይቀው?
‹‹አቡበክር አህመድን!››
‹‹ምኑ ነህ?››
‹‹ጓደኛው!›› መዝጋቢው ትንሽ ተጨነቀና ሌላ ነውሩን የሚያስቀጥልበት ጥያቄ ጠየቀ፡፡
‹‹ከአሁን ቀደም ገብተህ ታውቃልህ?››
‹‹አዎ! በቀደም ዕለት ገብቻለሁ!›› የገባበት ቀን ሩቅ ቢሆን ኖሮ ከዛ በኋላ የወጣ ህግ እንዳለ በመግለጽ እንዳይጠይቅ ለመከልከል ይመስላል፡፡ ግን ነውር ተለምዶ የለ?! ‹‹ጓደኛው ነኝ›› ብሎት ወደ ሌላ ጥያቄ አልፎ ያነሳው ጥያቄ ለመከልከል የሚያስችል ባለመሆኑ ወደ ኋላ ተመልሶ ‹‹ጓደኛ መጠየቅ አይችልም፡፡ ለመጠየቅ ዘመድ መሆን አለብህ፡፡ አባት፣ እናት፣ወንድም..››
‹‹እንዴ! በቀደምኮ ጠይቄዋለሁ!››
‹‹አይቻልም! ከላይ የመጣ ትዕዛዝ ነው!››
በእርግጥ እናት፣ አባት፣ ወንድም መሆኑን ይህን ነውር አያስቀረውም፡፡ ምክንያቱም ቂሊንጦ ታስረው የሚገኙት እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ እነ ናትናኤል ያለም ዘውድ ‹‹ማንም ሊጠይቀን ይገባል፡፡ ህገ መንግስታዊ መብታችን ነው፡፡›› በማለታቸው በቤተሰቦቻቸውም ጭምር እንዳይጠየቁ ተደርገዋል፡፡ አቡበክርን ለመጠየቅ ወደ ቃሊቲ የሄዱት ወጣቶችም ዘመድ ቢሆኑ የሆነ ምክንያት ተመዞላቸው መመለሳቸው አይቀርም ነበር፡፡ ምክንያቱም ከዛ ቤት ነውር ተለምዷል፡፡ እኛም ለምደንላቸዋል፡፡
በዚህ እየተገረምኩ እያለ አንድ እነ ወይንሸትን ለመጠየቅ እንደመጣን የገባው ወጣት ወደመዝጋቢዋ ጠቆመን፡፡ ኢ/ር ይልቃል መታወቂያውን አሳይቶ ወይንሸት ሞላን እንደሚጠይቅ ለመዝጋቢዋ ነገራት፡፡ ወይንሸት ሞላ ያስመዘገበቻቸው ጠያቂዎች ስም ዝርዝር ተፈለገ፡፡ የኢ/ር ይልቃልን ጨምሮ ወይንሸትን የሚጠይቁ ሰዎች ስም ዝርዝር ይታያል፡፡ የኢ/ር ይልቃል ስም የመጀመሪያ ተራ ቁጥር ላይ ነው፡፡ ግን በኮምፒውተር የተፃፈው የስም ዝርዝር ላይ የኢ/ር ይልቃል ስም መሃል ለመሃል አንድ ጊዜ በእስክርቢቶ ተሰርዟል፡፡ ምን አልባት የኢ/ር ይልቃልን ስም መጀመሪያ ላይ ያየው የህወሓት/ኢህአዴግ ካድሬ በንዴት የሰረዘው ይመስለኛል፡፡ መዝጋቢዋ የሆነ ደስ ያላት ትመስላለች፡፡
‹‹ተሰርዟል!›› አለች፡፡ ህግ ጠቅሳ መከራከር የምትችል ያህል በልበ ሙሉነት ነው የምትናገረው፡፡ በኮምፒውተር የተፃፈ ስም ዝርዝር ላይ በእስክርቢቶ ሰርዘው አትገባም ከሚሉ ሌላ የኢ/ር ይልቃል ስም የሌለበት ስም ዝርዝር ቢያስቀምጡ የጠያቂዎች ስም ዝርዝር ላይ የለህም ማለት ይችሉ ነበር፡፡ ግን ደግሞ ያ ነውራቸውን ሊቀንሰው ሆነ፡፡ ነገሩ ለማንስ ተጨንቀው? ምንስ ይመጣባቸዋልና?
በአንድ ወቅት ነገረ ኢትዮጵያ የህግ ባለሙያውን ተማም አባቡልጉን ይህን ለ30 ደቂቃ ብቻ መጠየቅ እና ጠያቂን መከልከልን በሚመለከት ጥያቄ አቅርባለት ነበር፡፡ ተማም እንደሚለው ይህ አሰራር ከህገ መንግስቱም፣ ከሞራልም፣ ከኢትዮጵያዊ ባህልም የሚቃረን ነውር ነው፡፡ እሱስ ብልግናም ነው ይለዋል፡፡ ተማም ‹‹በ21ኛው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያን በምታክል ትልቅ አገር እንዲህ አይነት ነገር መከሰቱ በእውነቱ ነውር ነው፡፡….እንዲያውም ለእኔ ይህ ብልግና ይመስለኛል፡፡›› ይላል፡፡
አንድ ሰው የሚታሰረው ከጥፋቱ ይታረም ዘንድ ለማስተማር ነው፡፡ ነገር ግን አሁን የሚፈፀመው በደልና ግፍ ስርዓቱ ሲያስር ከዛም በላይ ዓላማ እንዳለው የሚያሳይ ነው፡፡ ተማምም ‹‹ሰውን ካሰርከው በኋላ የግል ጉዳይ የለህም፡፡ …. የግል ካልሆነ ደግሞ በግለሰብ የሚፈጸም በቀል አይኖረውም፡፡ ምክንያቱም የግል ጉዳይ አይደለም! …የግል የሚሆነው ሰዎች ህግን ለተወሰነ ሰው አድርገው ስለሚወስዱት ነው፡፡›› ይላል፡፡
እውነት ነው! መጀመሪያ ነገር እነ እስክንድር፣ አንዱዓለም፣ ወይንሸት፣ አበበ ቀስቶ፣ ተመስገን ደሳለኝ፣ በፍቃዱ ኃይሉ፣ የሽዋስ አሰፋ ….. የታሰሩት አጥፍተው መታረም ስለሚያስፈልጋቸው አይደለም፡፡ መታረም ላቃተው ስርዓት የራስ ምታት ስለሆኑበት እንጅ፡፡ እንደ በደል ከተቆጠረ የእነዚህ ሰዎች በደል በህጋዊ መንገድ ህገ ወጥ ስራ የሚሰራውን ስርዓት በመቃወማቸው ነው፡፡ ህግ ደግሞ የስርዓቱ ቁንጮ ሰዎች የግል ንብረትና ማጥቂያ መሳሪያ ሆኗል፡፡ ለህዝብና ለሀገር ዋስትና ከሚሆን ህገ መንግስት ይልቅ የራሳቸው፣ የግላቸው ‹‹ህገ አራዊት›› ነግሷል፡፡ ይህ ህገ አራዊት ደግሞ ለበቃል እንጅ ለፍትህ ቦታ የለውም፡፡ መብቱን የጠየቀ መልሱ በቀል ነው፡፡ ስርዓቱን በህጋዊ መንገድ የጠየቀ መልሱ በቀል ነው፡፡ ምግብ እንዳይገባለት መከልከል፣ ጠያቂ እንዳይገባለት ማድረግ፣ ማሰቀየት፣ መስለብ፣ …..ስቀይ፣ ነውር….፡፡ እኛም ቢበዛ፣ ቢደጋገም…ይህንን ነውር፣ የስርዓት አልበኛውን ስርዓት ብልግና ለመድነው፡፡ (ምንጭ: ነገረ ኢትዮጵያ)

No comments:

Post a Comment