Translate

Tuesday, May 12, 2015

ኃይለማርያም ደሳለኝ እምባ እስኪተናነቃቸው ድረስ በአርከበ እቁባይና ስብሃት ነጋ ተተቹ

ኢሳት ዜና :- ጠ/ሚኒስትሩ ሚኒስትሮችንና የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናትን በሙሉ ሲያስገመግሙ ከከረሙ በሁዋላ በመጨረሻ ራሳቸው 15 ሰአታት በፈጀ ግምገማ ተገምግመዋል። አብዛኞቹ በአቶ ሃይለማርያም የስራ ችሎታና አመራር ላይ ዘለፋ ቀረሽ ሂስ አቅርበውባቸዋል። አቶ ሃይለማሪያም የቀረበባቸውን ሂስ ለመቀበል ዝግጁ አለመሆናቸው ግምገማው ረጅም ጊዜ እንዲወስድ አድርጓል። ግምገማው ከምርጫው በሁዋላ የሚቀጥሉና የማይቀጥሉ ባለስልጣናትን ለመለየት እና ግድፈታቸውን አርመው ሰርተው እንዲጠብቁ ለማድረግ ያለመ መሆኑ ተነግሯል።
HaileMariam
አቶ ሃይለማርያም ከህወሃቶቹ ከአቶ አርከበ እቁባይ፣ አቶ ስብሃት ነጋና አስመላሽ ወልደስላሴ የሰላ ትችት ሲቀርብባቸው፣ ከራሳቸው የደህዴን አባላት ከሆኑት ከአቶ ሬድዋን ሁሴንና ሙፈሪያት ከሚልም ዘለፋ ቀረሽ ትችት አስተናግደዋል። አብዛኞቹ ብአዴኖች፣ አቶ በረከት ሳይቀሩ የአቶ ሃይለማርያምን ቁርጠኝነት ጥያቄ ውስጥ አስገብተዋል። በመጠኑም ቢሆን የራሩላቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ብቻ ናቸው።
አቶ ሃይለማርያም እንቅስቃሴያቸውንና የሌሎችን ሰዎች እንቅስቃሴዎች የሚቆጣጠሩ የስለላ ካሜራዎች እንዳይተከሉ፣ በጽህፈት ቤታቸው ያለውም እንዲነሳ ማድረጋቸው ከደህንነት ሃይሉ ጋር አጋጭቷቸው እንደቆየና ውዝግቡ አሁንም ድረስ እንደቀጠለ መሆኑ ተወስቷል።
አቶ ሃይለማርያም አንዳንድ መልሶችን ሲሰጡ እንባ ይተናናቃቸው ነበር። በተወሰኑ ቦታዎች ላይ ደግሞ በእልህና በወኔ ተሟግተዋል። አቶ ስብሃት ነጋ በአቶ ሃይለማርያም ላይ ለሰነዘሩት ትችት፣ አቶ ሃይለማርያም ” ስብሃት በጣም ይጮሃል፣ እንዳሞራ ሁሉ ይዞረኛል፣ እዚህ ሳወያይም ይጮሃል፣ አለቃ መሆን ችግር ነው ብየ ዝም አልኩ። ንግግር ከመልክ ያምራል ይባላልና ያሳሳትኩት ነገር ካለ አርማለሁ። በአባባል ክፍተት ካለ ይቅርታ” በማለት መልሰዋል።
የግምገማውን ዝርዝር ሪፖርት በነገው ዘገባ የምናቀርብ መሆኑን ለመግለጽ እናወዳለን።

No comments:

Post a Comment