Translate

Monday, May 30, 2016

“የራስን ዕድል በራስ የመወሰን ጥያቄን በመጀመሪያ ለክልል ማቅረብ እንደ ግዴታ ሊቀመጥ ነው”

21241-paarlaa1
ሪፖርተር ላይ የወጣው ጽሁፍ “የራስን ዕድል በራስ የመወሰን ጥያቄ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ከመቅረቡ በፊት፣ የክልል መፍትሔን አሟጦ የመጨረስ ሕጋዊ ግዴታ ሊቀመጥ ነው” ይላል፡፡
ረቂቅ ድንጋጌው አክሎም ይህ የሚሆነው ‹‹የራስን ዕድል በራስ የመወሰን የመብት ጥያቄ ወደ ምክር ቤቱ የሚቀርበው በክልሉ በሚገኙት የተለያዩ የመስተዳደር እርከኖች ቀርቦ አጥጋቢ መፍትሔ ያልተሰጠው መሆኑ ሲረጋገጥ ብቻ ነው፤›› ይላል፡፡ በክልሎች ፖለቲካዊ ሁናቴዎች መብቴ አልተሟላም የሚል የራስን እድል በራስ የመወሰን ጥያቄ አቅራቢ “ክልላዊ አስተዳደሩን ጠብቆ ለፌዴሬሽን ምክር ቤትም ሊቀርብ” ይችላል፡፡ ከዚህ በፊት በጥያቄ አቅራቢው ፍላጎት ወይ ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት አልያም ወደክልል ይቀርቡ እንደነበርም ሪፖርተር አትቷል፡፡ አዲስ ረቂቅ ድንጋጌ የተወጠነበትም ምክንያት “የተጭበረበረ ወይም እውነተኛ ያልሆነ የራስን ዕድል በራስ የመወሰን ጥያቄ በአሁኑ ወቅት እየተበራከተ” በመምጣቱ ነው ይላል፡፡

ከላይ የሰፈረው ሀሳብ ለወልቃይት አማራ ምን መልእክት ያስተላልፋል? የወልቃይት የአማራ ብሄረተኝነት የማንነት ጥያቄ ለትግራይ ክልል ይቀርባል፡፡ በክልሉ ቀርቦም ድንጋጌው እንዳስቀመጠው እስከሁለት አመት ድረስ ይታሻል፡፡ ምንም እንኳ የፌዴሬሽን ምክርቤትም የወያኔ ቢሆንም ምናልባት በግለሰብ ደረጃ አንዳንድ የአማራ ሰዎች ሊኖሩበት ስለሚችሉ ለወልቃይት የአማራነት መከበር ጥያቄ ቀና አመለካከት ሊኖራቸው ይችላል፡፡ በተጨማሪም ጥያቄው ከትግራይ ክልል ወጥቶ በፌዴሬሽን ምክብር ቤት መስተናገዱ ከመዋቅር አንጻር የተሻለ እድልን ይፈጥራል፡፡ ነገር ግን ይህንን ለመዝጋት የወልቃይትን ጉዳይ ሙሉ በሙሉ በትግራይ ክልላዊ አስተዳደር ሙሉ ተጽእኖ ማሳደር አስፈለገ፡፡ ይህም ሁለቱን ተቃራኒ ፍላጎቶች አንድ ላይ ጨፍልቆ ተከሳሽን ዳኛ አድርጎ የሚያቀርብ ፍርደገምድል ስራ ነው፡፡ የወልቃይት አማሮች “ጥያቄ በትግራይ ክልላዊ አስተዳደር መኖር በቃን፤ እኛ አማራ ነን፤ መኖር የምንፈልገውም ከወገናችን አማራ ጋር ነው” የሚል ነው፡፡ ይህንን ጥያቄ ዋና የበደልና ግፍ ምንጭ ወደሆነው የትግራይ ክልላዊ አስተዳደር ወስዶ በህግ አስሮ ማስቀመጥ ማለት በወልቃይት አማሮች ላይ የሞት ፍርድ እንደመበየን የሚቆጠር ነው፡፡ የትግራይ ተስፋፊ አስተዳደር የወልቃይትን አማራነት ጥያቄ አምኖ ይቀበላል፤ ጥያቄያቸውን ይመልሳል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ይህ ረቂቅ ህግ ከፋም ለማም ድምጻቸውን ሊሰማ ከሚችለው የአማራ ክልላዊ አስተዳደር ተጽእኖ ውጭ ለማድረግ እና ብቻቸውን ለማፈን የተሸረበ ሴራ ነው፡፡ ባጠቃላይ ረቂቅ ህጉ የወልቃይት አማሮችን ጉዳይ ከፌዴሬሽን ምክርቤትም ከአማራ ህዝብና ክልላዊ አስተዳደርም በመነጠል ዘራቸውን ሲያጠፋ በኖረው የትግራይ ክልል አስተዳደር ስር በማናለብኝነት መጨፍለቅ ነው፡፡
ይህ ረቂቅ ህግ የቅማንት አማራን ጥያቄም ሙሉ በሙሉ በአማራ ክልላዊ አስተዳደር ስር የሚያስቀምጥ ነው፡፡ የቅማት አማራ ጥያቄ ወደፌዴሬሽን ምክር ቤት ከመሄዱ በፊት በአማራ ክልላዊ አስተዳደር ስር ይታያል ማለት ነው፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው ከረቂቅ ህጉ ላይ ተጠቅሶ ሪፖርተር ላይ የሰፈረው “የክልል መስተዳድር አካላት ውስጥ በኃላፊነት ተመድበው ሲሠሩ የነበሩ ግለሰቦች ከኃላፊነት በሚነሱበት ጊዜ እውነተኛ ያልሆነ የማንነት ጥያቄን በማንሳት አገርን የማወክ፣ ማኅበረሰቦችንም የመበጥበጥ ሁኔታ እየተለመደ መምጣቱ ሌላኛው ምክንያት ተደርጐ ተወስዷል” የሚለው ክፍል ነው፡፡ ከዚህ በፊት እንደሚታወቀው ከቅማንት አማራ ጋር ተያይዞ የተነሳው ችግር “በሰሜን” ጎንደር “ዞን” የነበረው የቅማንት አማራ አስተዳደራዊ የበላይነት የተነካባቸው ሰዎች የፈጠሩት ነው ተብሎ ይታሰባል፡፡ ስለዚህም ይህንን ጥያቄ የማፈን አዝማሚያ ያለ ይመስላል እንደረቂቅ ህጉ፡፡
ጠለቅ አድርገን ስናየው ነገርየው የወያኔ የተጠና ቁማር መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ ወያኔ በፌዴሬሽን ምክርቤት አማካኝነት ይህንን ረቂቅ ህግ መጻፍ ለምን አስፈለገው? እንደሚገመተው የወልቃይትን ጥያቄ ለማብረድ የቅማንትን ጉዳይ እንደማጫወቻ ካርድ ሲጠቀሙበት ቆይተዋል፡፡ ምንም እኳ የወያኔ የሩቅ ጊዜ ተጨባጭ አላማ መላ ጎንደርን ወደትግራይ መጠቅለል ቢሆንም ለጊዜው እየጋመ የመጣው የአማራ ብሄረተኝነት እና ህዝባዊ ብሶት ከወልቃይት የአማራነት ጥያቄ ጋር ተያይዞ አጣብቂኝ ውስጥ ከቶአቸዋል፡፡ እንደአጭር ጊዜ መፍትሄ ሊያስቡት የሚችሉት ታዲያ የቅማንት አማራን ጉዳይ ለአማራ ክልላዊ አስተዳደር እንደ እጅ መንሻ በማቅረብ በልዋጩ ወልቃይትን ከላይ በተዘረዘረው መንገድ ወደትግራይ መጠቅለል ነው፡፡ ወያኔ ለብአዴን “ቅማንትን ስለምሰጥህ እኔ ደግሞ ወልቃይትን በይዞታየ ስር አጸናለሁ” የሚል ሊሆን ይችላል፡፡ ይህም አማራን በአማራ ለውጦ የትግራይን ጥቅም ማስከበር ነው፡፡ ማለትም በቅማንት አሳቦ የወልቃይትን ጥያቄ መደፍጠጥ፡፡ ልብ ብሎ ላስተዋለው ወያኔዎች የወልቃይት ጉዳይ ሲጋጋል ነው የቅማንትን ችግር የሚያባብሱት፡፡
ባጭሩ በዚህ ረቂቅ ህግ እይታ የወልቃይት ጥያቄ የተጭበረበረ ሲሆን የቅማንት ደግሞ ጥቅማቸው የተነካባቸው ሹመኞች ያነሳሱት ረብሻ ነው ማለት ነው፡፡ የወያኔው ቁማር ስሌት እግዲህ ይህ ነው ጠለቅ ተደርጎ ሲመረመር፡፡ በዚህ መንፈስ ስናየው አዲሱ ረቂቅ ህግ የወልቃይትን የአማራነት ይከበር ጥያቄ በጉልበት አካሄዱን በማወሳሰብ ማፈን ነው፡፡
ይህንን ከባድ ሴራ ያዘለ ህግ ተግባራዊ እንዳይሆን እና የወገኖቻችን ወልቃይት አማሮች ጥያቄ በአስቸኳይ ተገቢውን ምላሽ እንዲያገኝ እንዲሁም ቅማንት አማራን መላውን አማራ ለማተራመስ እና የወልቃይትን ወላፈን ለማዳፈን እንደመጫወቻ ካርድ መጠቀማቸውን እንዲያቆሙ መረባረብ አለብን፡፡
ድል ለአማራ
መለክ ሐራ

No comments:

Post a Comment