Translate

Tuesday, October 21, 2014

ዘጠኝ የፖለቲካ ፓርቲዎች የትብብር ስምምነት ተፈራረሙ

ነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ከአዲስ አበባ እንዘገበው ዘጠኝ የኢትዮጵያ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች ዛሬ ጥቅምት 11/2007 ዓ.ም በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት የትብብር ስምምነት ተፈራረሙ፡፡

ፓርቲዎቹ ለረዥም ጊዜ ስለ ትብብር ሲመካከሩ የቆዩ መሆኑ የታወቀ ሲሆን፣ ዛሬ ሰባት ገጽ ያለው ሰነድ ላይ የትብብር ፊርማቸውን በማኖር ትብብሩን ሊመሩ የሚችሉ አመራሮችንም መምረጣቸው ታውቋል፡፡
ዘጠኙ ፓርቲዎች የትብብር ስምምነቱ ያስፈለገበትን ምክንያት በሰነዱ ላይ ገልጸዋል፤ በዚህም ‹‹ነጻ አሳታፊና ታአማኒ ምርጫ እንዲካሄድ በትብብር ለመስራት፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋትና የዜጎችን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩ በጋራ መታገል››ን በተመለከተ በጋራ ለመስራት ተስማምተዋል፡፡
በዚህም መሰረት ፈራሚዎቹ ፓርቲዎች የሚከተሉትን አመራሮች ትብብሩን እንዲመሩ መርጠዋል፡-
1. ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት ከሰማያዊ ፓርቲ
2. ምክትል ሊቀመንበር አቶ ኤርጫፎ ኤርጌሎ ከከንባታ ህዝቦች ኮንግረንስ
3 ዋና ፀኃፊ አቶ ግርማ በቀለ ከኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት
4. ምክትል ፀኃፊ አቶ ካሳሁን አበባው ከመኢአድ
5. ገንዘብ ያዥ አቶ ኑሪ ሙደሂር ከመኢዴፓ ሆነው ተመርጠዋል፡፡
በትብብር ለመስራት ሲወያዩ ከነበሩት 14 ፓርቲዎች መካከል አንድነትና መድረክ ውስጥ የታቀፉት ፓርቲዎች ትብብሩን ለመፈረም በየ ድርጅቶቻቸው ውሳኔ ባለመተላለፉ ያልፈረሙ ሲሆን ትብብሩ እስከ ቅዳሜ እንዲጠብቃቸው ጠይቀዋል፡፡ በመሆኑም በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ ይፈርማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ትብብሩ ስለ ቀጣይ የትግል ሂደትና ስለ ትብብሩ አጠቃላይ ሂደት ላይ ነገ ጥቅምት 12/2007 ዓ.ም ከጠዋቱ አራት ሰዓት በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት መግለጫ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

No comments:

Post a Comment