Translate

Tuesday, September 30, 2014

የዋሽግተኑ ተቃውሞ ኢሳትን በዓለም ዓቀፍ ስመጥር የዜና አውታሮች ዝናው ገንኖ እንዲወጣ አደረገ፣ኤምባሲው ጉዳዩን ለፖሊስ አሳውቆ እርዳታ ከመጠየቅ ይልቅ አራት ኪሎ ያለ ይመስል ዋሽግተንን በተኩስ መናጡ አሜሪካኖችን ማናደዱ አልቀረም (የዋሽግተኑን የኢትዮጵያ ኤምባሲ በተመለከተ የጉዳያችን አጭር ዘገባ)


ፎቶ www.csnwashigton.com 

''መሣርያውን ወደሚከራከሩት ሰዎች ደገነ እና ተኮሰ'' ''He points the weapon at others who argue with him and fires'' ሮይተርስ ከዋሽግተን ዲሲ ዛሬ የዘገበው። 

ዛሬ መስከረም 19፣2007 ዓም ዋሽግተን ዲሲ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በተቃዋሚ ኢትዮጵያውያን ቁጥጥር ስር ውሎ ባለ ኮከቡ ሰንደቅ ዓላማ በነፃው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ተቀይሯል። ተቃውሞውን አስመልክቶ ኢሳት ዘግይቶ በለቀቀው ተጨማሪ ዘገባ ተቃዋሚዎቹ በኢምባሲው ውስጥ ዘልቀው የአቶ አንዳርጋቸውን እና የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ይዘው ''ነፃነት! ነፃነት!'' ሲሉ አሳይቷል።

ቀደም ብሎ አምባሳደር ግርማ ብሩ በሸሚዝ እንደሆኑ ከሌሎቹ የኢምባሲው ሰራተኞች ጋር ቆመው ሲመለክቱም ሌላው የታየው ትዕይንት ነበር።ተቃውሞውን ተከትሎ የዓለም ስመጥር የዜና አገልግሎት ድርጅቶች ሮይተርስ እና የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ኤ ኤፍ ፒን ጨምሮ የቪድዮ ምንጫቸው ኢሳት የኢትዮጵያውያን ቴሌቭዥን መሆኑን ከመጥቀሳቸውም በላይ የኢሳትን ሰበር ዜና የያዘ ቪድዮ በቀጥታ ለጥፈው ታይተዋል።በመሆኑም በዛሬው እለት ኢሳት በመላው ዓለም የዜና አውታሮች የመወሳቱን ያህል ከእዚህ በፊት በእዚህ አይነት ስፋት በመላው ዓለም በሚገኙ ታላላቅ የዜና አውታሮች የተጠቀሰ አይመስለኝም።

በሌላ በኩል በአሜሪካን ሕግ ሽጉጥ ተኩሶ ማስፈራራት አይደለም በአንደበቱ ለማስፈራራት የሞከረ የሚደርስበት ቅጣት ከፍተኛ እንደሆነ ይታወቃል።ሆኖም ግን የኢምባሲው ሰራተኛ በተኮሰው ጥይት አካባቢውን በማሸበር እና በሰላማዊ መንገድ ተቃውሞ ባሰሙ ዜጎችን በማስፈራራት ሕግ መጣሱን ለማወቅ ተችሏል።በአሁኑ ሰዓት ግን ግለሰቡ በቁጥጥር ስር መሆኑን በርካታ ዓለም አቀፍ የዜና አውታሮች እየጠቀሱ ይገኛሉ።ሆኖም ግን ግለሰቡ የዲፕሎማቲክ ከለላ ካለው አሜሪካ በአጭር ጊዜ ከሀገር እንዲወጣ ልታደርግ ትችላለች።በመሆኑም NBC የዜና አገልግሎት የተኮሰው የኢምባሲ  ሰራተኛ መታሰሩን ገልጧል።ዜናውን ይህንን በመጫን ማንበብ ይችላሉ።

ጉዳዩን ተከትሎ በነገው እለት ከኢትዮጵያ የሚወጣው  መግለጫ ይዘት ከወዲሁ መገመት አያስቸግርም።ሆኖም ግን ምንም አይነት መግለጫ እና ማብራርያ ቢሰጥ በአሜሪካውያንም ሆነ በምዕራቡ ዓለም ፅንሰ ሃሳብ አንፃር  ከጠቅላላ ጉዳዩ ውስጥ የኢምባሲ ሰራተኛው  ምንም አይነት የጦር መሳርያ  ባልያዙ በባዶ እጃቸው ተቃውሞ ባሰሙ ኢትዮጵያውያን ላይ  የጦር መሳርያ በመደገን የማስፈራራቱ እና በኃላም የመተኮሱን ያህል የጎላ እና አናዳጅ ነገር ነጥሮ አይወጣም። በመሰረቱ ዜጎች የሀገራቸውን ኢምባሲ ሲቃወሙ ይህ አዲስ አይደለም።እራሷ አሜሪካ የእራሷ ዜጎች ባልሆኑ ግን በሌሎች ሀገሮች ዜጎች ኤምባሲዋ ተውሯል።

በዲፕሎማሲው ዓለም ደግሞ አንድ ኢምባሲ በራሱ ሀገር ተወላጆች በተቃውሞ ቢናጥ ጉዳዩ የዓለም ዓቀፉን የቬና ስምምነት ከመመልከት  ይልቅ የአንዲት ሀገር የውስጥ ጉዳይ ገንፍሎ የመውጣት አይነተኛ አመላካች ጉዳይ ከመሆን አያልፍም።ከእዚህ በዘለለ ኢምባሲው ጉዳዩን ለፖሊስ ደውሎ እርዳታ ከመጠየቅ ይልቅ አራት ኪሎ ያለ ይመስል ዋሽግተንን በተኩስ መናጡ ነው አሜሪካኖችን የሚያናድደው።

በመጨረሻም አንድ ነገር ማንሳት ይቻላል።ባራክ ኦባማ ከአቶ ኃይለማርያም እና ከከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ቁጭ ብለው ካወሩ ገና  ሳምንት ሊሆነው ነው።የዛሬው በመዲናቸው ውስጥ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ተቃውሞ ያሰሙ ኢትዮጵያውያን ጉዳይ ለኦባማም ጭምር የሚያስደነግጥ ነው። የኦባማ የአፍሪካ ፖሊሲ ዕውን በጥናት ላይ የተመሰረተ ነው? ላለመሆኑ ማሳያው የዛሬው ጠንካራ ተቃውሞ ነዋ!

ጉዳያችን
መስከረም 20/2007 ዓም (ሴፕቴምበር 30/2014)

No comments:

Post a Comment