Translate

Thursday, September 11, 2014

ህወሃት “በህወሃት ወዳጆች” ለእርቅ እንዲነሳሳ እየተሸመገለ ነው!

ራስ መንገሻ ስዩም ጉልህ ሚና ይዘዋል

tplf recon

በኢትዮጵያ ከቀን ወደ ቀን እየከረረ የሚሄደው የጥላቻ ደረጃ ያሳሰባቸው “የህወሃት ወዳጆች” ህወሃት ለእርቅ እንዲነሳሳ የማግባባት ስራ እየሰሩ መሆናቸው ተሰማ። የአቶ መለስና “የህወሃት ወዳጅ” ወይም ቅርብ ናቸው የሚባሉት ራስ መንገሻ ስዩም ጉልህ ሚና ይዘዋል።

የጎልጉል የአዲስ አበባ ተባባሪዎች እንደዘገቡት ከሆነ በህወሃት መንደር እርቅ አስፈላጊ እንደሆነ የሚያምኑ ወገኖች በህወሃትና በተቀረው ህዝብ መካከል እየሰፋ የሄደው ጥላቻ መልኩን እንዳይቀይር ከፍተኛ ስጋት አላቸው። በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች የሚሰማው ቅሬታና የተቋጠረው ቂም ማየሉ ያሳሰባቸው እኚህ ወገኖች ህወሃት ደጁን ለእርቅ መክፈት እንዳለበት በማሳሰብ መጎትጎታቸው እንጂ የእርቁ መሰረትና እርቁ የሚያካትታቸውን ወገኖች በዝርዝር አልገለጹም።
“ኢህአዴግ ናቸው” በሚል የሚታሙት ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅና ፓስተር ዳንኤል ገብረሥላሴ እንደሌሉበት ያረጋገጡት የጎልጉል ተባባሪዎች ከእነ ራስ መንገሻ ስዩምን በተጨማሪ የሜሪላንድ ዩኒቨርስቲ መምህር ዶ/ር ጥላሁን በየነ፣ ፓስተር ዳንኤል መኮንን በዋናነት እንደሚገኙበትጠቁመዋል። ወያኔን በስሙ ከነግብሩ በመጥራት በአገር ውስጥ ሆነው ያለአንዳች ዕረፍት ስለአገራቸው ቀንተሌት የሚለፉት ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያምን ለማካተት እቅድ እንዳለም አመልክተዋል።
ከሌሎች ምሁራኖች እጅግ በተለየ የሚሰማቸውን ስሜት ያለማቋረጥ፣ ሃላፊነታቸውን ያለድካም፣ እውቀታቸውን ያለገደብ፣ ልምዳቸውን ያለንፍገት በነጻነት ከብሎግ እስከ ፌስቡክ ድረስ ዘመናዊውን ቴክኖሎጂ ሁሉ በመጠቀም እያካፈሉ ያሉት ፕሮፌሰር መስፍን በተባለው እርቅ ተሳታፊ ለመሆን ፈቃደኛ ስለመሆንና አለመሆናቸው የዜናው ተባባሪዎቻችን ማረጋገጥ አልቻሉም። ሆኖም ግን እውነተኛ እርቅ ሂደት ከተጀመረ ሊያቅማሙ የሚችሉበት ጉዳይ እንደማኖር የዜናው ምንጮች አስረድተዋል። ለዘመናት ካዳበሩት ልምድና በሰላማዊ ትግል ካላቸው ጽኑዕ እምነት አኳያ የፕሮፌሰር መስፍን በዚህ ዕቅድ ውስጥ መግባት ጉልህ ጥቅም አለው፤ ለብዙዎችም በሂደቱ ላይ እምነት እንዲኖራቸው ያደርጋል የሚለው አስተሳሰብ ብዙዎች ይጋሩታል። በዚህ ጉዳይ ላይ ስማቸው የተጠቀሰው ግለሰቦች በሙሉ አስተያየት ካላቸው ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ ለማስተናገድ ዝግጁ መሆኑንን ይገልጻል።
“በህይወቴ አንዲህ ያለ ጥላቻ አጋጥሞኝ አያውቅም። ህዝብ በጥላቻ ተሞልቷል። ይህ ጥላቻ መልኩን ሳይቀይር ሊመክን ይገባዋል” ሲሉ ለጎልጉል ዘጋቢዎች አስተያየት የሰጡ ምሁር “ኢትዮጵያዊያን በየአቅጣጫው ሊተባበሩና ይህንን አደገኛ ጥላቻ በሰላማዊ መንገድ በእርቅ ሊሰብሩት ይገባል”ብለዋል
ቀደም ሲል ስለ እርቅ ሲጠየቁ “ማንና ማን ተጣላ” በሚል መልስ የሚሰጡት አቶ ስብሀት ነጋ ለጀርመን ሬዲዮ “ተቃዋሚዎች አንድ ሆነው ይምጡ፤ ጥያቄያቸውን በጽሁፍ ያቅረቡ” በማለት እርቅ አስፈላጊ እንደሆነ መናገራቸው አይዘነጋም። አቶ ስብሃት ያለ ምንም ምክንያት እርቅን ደጋፊ ሆነው ሊቀርቡ እንደሚችሉ አስተያየት ሰጪዎችን ጠቅሰው የጠቆሙት የጎልጉል ተባባሪዎች “የኢትዮጵያ ህልውና አሁን ካለበት አሳሳቢ አደጋ ስለመድረሱ አቶ ስብሃትና ህወሃት ጠንቅቀው ያውቁታል። የህወሃት ደጋፊዎችና ህወሃት በስማቸው በደል እየሰራ ለጥላቻ የዳረጋቸው ሁሉ ጉዳዩ ዕረፍት ነስቷቸዋል። አሸባሪ፣ ሽብርተኛ፣ ሳይባል ሁሉንም ያካተተ የእርቅ ድርድር ሊዘጋጅ ይገባል” ብለዋል። ዝርዝሩ ብዙ ሥራ የሚጠይቅ መሆኑንም አልሸሸጉም፡፡
ከተቃዋሚው ዘንድ በተደጋጋሚ የትግራይ ልሒቃንም ሆኑ ሌሎች ባለው አጠቃላይ የአገሪቱ ሁኔታ ላይ ተሳትፎ አያሳዩም፣ በተገቢው ሁኔታ የሚያደርጉት ነገር የለም፣ ከወያኔ ጋር ተሞዳሙደው ነው የሚሠሩት፣ … ሲባል የመኖሩን ያህል አሁን በተጀመረው ሂደት ውስጥ በእንቅስቃሴ ላይ ያሉትን በጭፍን መቃወም ለአገር የሚበጀውን በውል ካለማወቅ የሚመነጭ ጭፍን አስተሳሰብ እንደሆነ የዜናው ተባባሪዎች አስረድተዋል፡፡ እርቅ ለመፈጸም ሁሉም ወገን በሚያምነው መወከል አለበት፤ ይህ ደግሞ በአገራችን አሠራር የተለመደ አካሄድ ነው፡፡
በማናቸውም የፖለቲካ እምነት ውስጥ የሚገኙ፣ በየትኛውም የብሄርና የጎሳ ከለላ ውስጥ የታቀፉ፣ አገሪቱ ከገባችበት አስከፊ የጥላቻ አደጋ እንድትጸዳ ከሥሩ ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ፤ አለበለዚያም የሙከራቸው መጨረሻው ሳይታወቅ ተቃውሞ ሊሰነዘርባቸው እንደማይገባ የዜናው ምንጮች አስታውቀዋል። ከጅምሩ የማጨናገፍና በጭፍን የመቃወም አሠራር መለመዱ ብዙ የእርቅ ሃሳብና የማስታረቅ አቅም ያላቸውን እያሸማቀቀ ስለሄደ ቢያንስ ጉዳዩን በትዕግስት መመልከት ተገቢ እንደሆነ ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑት ለጎልጉል ተባባሪዎች አመልክተዋል። አሜሪካ ተቃዋሚዎች ወደ አንድ ህብረት እንዲመጡ ፍላጎት እንዳላት፣ በተለያዩ አገራት በኩልም እርቅ አስፈላጊ እንደሆነ መናገራቸው ይታወሳል።

ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (http://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ በእርቅ ጉዳይ ላይ ሲዘግብ ሰንብቷል፡፡ ከዚህ ዜና ጋር አግባብነት ስላላቸው ባለፈው ያተምናቸውን ሁለት ዘገባዎች ከዚህ በታች በድጋሚ አቅርበናል፡፡

ስብሃት “እርቅን” እንሞክራለን፤ ከባልደረቦቼ ጋር እመክራለሁ አሉ

እርቅ ላይ የምትሰሩ የት አላችሁ?

reconciliation
May 23, 2014 11:31 pm
ባለፈው ሳምንት የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ የተቃዋሚ ፓርቲ ወኪሎችንና አቶ ስብሃትን ባንድነት በየተራ አናግሮ ነበር። ከውይይቱ የተለመደ ክርክር በዘለለ አቶ ስብሃት እርቅ አስፈላጊ መሆኑንን ማመናቸው የተለየ ጉዳይ ነበር። እንደ እርሳቸው አነጋገር አሁን የተጀመረውን መልካም የልማት ስራ ለማስቀጠል እርቅ አስፈላጊ ነው። የእርቅን አስፈላጊነት በማመን ከባልደረቦቻቸው ጋር በመምከር የእርቅ ጉባኤ ለማዘጋጀት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
አቶ ስብሃት “የተቃዋሚ ፓርቲ አለ ብዬ አላምንም” በማለት ተቃዋሚዎችን እንደወትሮው ሁሉ ዘልፈዋል። “መደብ የላቸውም” ሲሉ ተቃዋሚዎችን ጭራሽ እንደ ፓርቲ እንደማይቆጥሯቸው የተናገሩት አቶ ስብሃት ከዘለፋቸው በኋላ ስለ እርቅ አግባብ መናገራቸውን፣ ጠያቂው እሳቸው ባነሱት አዲስ ሃሳብ ላይ በመንተራስ ማረጋገጫ ሲጠይቃቸው “ከጓደኞቼ ጋር መክሬ” በማለት በቅርቡ የእርቅ መድረክ እንዲፈጠር እንደሚተጉ መናገራቸውን ተከትሎ እርቅ ላይ እንሰራለን ከሚሉ ወገኖች ምላሽ አልተሰማም።
አሁን ባለው ውጥረት የነገሰበት የኢትዮጵያ ፖለቲካ አብዛኞችን ስጋት ውስጥ የከተተ ነው። በስዊድን አገር በአንድ የእራት ግብዣ ላይ ተገኙ የትግራይ ተወላጅ ለጎልጉል እንደተናገሩት “በጎሳና በክልል ተለይቶ የሚንቦገቦገው የጥላቻ ፖለቲካ መጠኑ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ አስግቶኛል። እርቅ ብቸኛ መፍትሔ ነው። በዚህ ሃሳብ ላይ መስራት ግድ ነው” የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።
በፍርሃቻ ከሁሉም ያጣ ላለመሆን ኢህአዴግን የሚደግፉ እንዳሉ ያመለከቱት እኚሁ ሰው የኢትዮጵያ ጉዳይ በእጅጉ ዕረፍት እንደነሳቸው አልሸሸጉም። “ስብሃት ነጋ እርቅ ላይ ለመስራት ከልብ ያሰቡ ይመስልዎታል?” በሚል አስተያየታቸውን የተጠየቁት እኚሁ ሰው “ኢህአዴግም ሆነ ህወሃት እኮ የሰዎች ጥርቅም እንጂ ሌላ ግዑዝ ነገር አይደሉም። ችግሩን ከሁላችንም በላይ ይረዱታል። እንደውም እነሱ የሚያውቁትን ያህል የችግሩን አሳሳቢነት ተራው ነዋሪ ቢረዳ ልቡ በድንጋጤ ሊቆም ይችላል” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። አያያዘውም ኢህአዴግ ችግሮች ገንፍለው እንዳይወጡ የሰጋበት ደረጃ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በሁሉም አቅጣጫ የሚያገኟቸው ወገኖች የሚነግሯቸው ይህንኑ የስጋት ጉዳይ እንደሆነም ተናግረዋል።
ኢህአዴግ የሚነሳበትን ተቃውሞ በጥይት እያረገበ መዝለቅ እንደማይችል ብዙዎች እየተናገሩ ነው። ኢህአዴግ ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ ከማስወገድ ይልቅ ጥይትን መምረጡ የበቀሉን ደረጃ እያናረው ስለመሆኑም ክርክር የለም። ኢህአዴግ የገደላቸው ወገኖች በሙሉ ወገን አላቸው፣ ዘር አላቸው፣ ተቆርቋሪ አላቸው፣ ጎሳ አላቸው፣ ምድር አላቸው፣ ቀበሌና ቀዬ አላቸው፣ ወዳጆችና ተከራካሪዎች አሏቸው በሚል ኢህአዴግ ያልተመከረበት ወቅትና ጊዜ ለም። እንደውም ባንድ ወቅት ለጎልጉል አስተያየት የሰጡ “ብሶት ህወሃትን ብቻ አይወልድም፣ የብሶት የበኩር ልጅ ህወሃት ብቻም ሊሆን አይችልም” ብለው ነበር።
ከግድያው፣ ከእስሩ፣ ከአፈናው፣ ከድብዳው፣ ከማስፈራራቱ በተጨማሪ በአገሪቱ ሃብት ላይ ኢህአዴግ እየፈጸመ ያለው ፍትሃዊነት የጎደለው የንግድ ስምምነትና የንግድ ውድድር ያስቀየማቸው ወገኖች ቁጥርም ቀላል አይደለም። አብዛኞች በተለያዩ ወቅቶች ሲገልጹት እንደነበረው ኢህአዴግ ባለስልጣናቱ የህዝብን ሃብት በሽርክና በመቸብቸብ ሃብት አፍርተዋል። እነርሱ እንዳሻቸው እየዘረፉ ምስኪን አርሶ አደሮች ለእለት ጉርስ እየጫሩ ከሚኖሩበት ቀዬ ከነቤተሰቦቻቸው እንደ ባዕድ በጎሳ እየተለዩ እንዲፈናቀሉ ተደርጓል። ኢህአዴግ ካለበት ፍርሃቻ በመነሳት በየጊዜው በደልን እያበዛ ጠላቶቹን በማብዛቱ ስጋት የገባቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ሰላማቸውን አጥተዋል።
በበዳዩ ወገኖች ተርታ በተሰለፉና በተበዳዩ ወገኖች ጎን ባሉት ዜጎች መካከል እየታየ ያለው የበቀል ስሜት ልክ እንዳጣ የሚናገሩ ክፍሎች አሁን አገሪቱ ላለችበት አጣብቂኝ ወቅት መፍትሔው እርቅ እንደሆነ ሲወተውቱ ዓመታት ተቆጥረዋል። አቶ ስብሃት የተናገሩት እርቅ ሃሳብ እውነተኛ ይሁን ከምርጫ ጋር በተያያዘ የተቃዋሚዎችንና የህዝቡን ስሜት “ለማቀዛቀዝ” ኢህአዴግ እንደለመደው ሊጠቀምበት የፈለገው ማደናገሪያ ይሁን በእርግጠኝነት ለመናገር አይቻልም፡፡ ሆኖም ግን ስብሃት ለተናገሩት የእርቅ ሃሳብ ድጋፍ በመስጠት አገሪቱ ላይ የነገሰውን የጥላቻና የቁጣ ፖለቲካ ማምከን አስፈላጊ ቢሆንም እስካሁን ከሌሎች ወገኖች የተሰማ ነገር አለመኖሩ አስገራሚ ሆኗል። በወቅቱ የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ ዘጋቢ ነጋሽ መሐመድ የጋበዛቸው የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ግን ኢህአዴግ የእርቅ ጥሪ ካቀረበ እንደሚስማሙ ተናግረዋል።
ጥቅምት 25፤2006 ዓም (November 4, 2013) ላይ ጎልጉል “በህወሃት ውስጥ የዕርቅ ሃሳብ መነሳቱ ተሰማ” በሚል ርዕስ ባሰፈረው ዜና ላይ ምንጭ አድርጎ የጠቀሳቸው “የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራርና ዲፕሎማት እንዳሉት ህወሃት ውስጥ “እርቅ አስፈላጊ ነው” በሚል እቅድ እንዲያዝና እንዲሰራበት ሃሳብ ቀርቧል። በድርጅቱ ውስጥ በተፈጠረ አለመተማመን ሳቢያ ስጋት የገባቸው የህወሃት ሰዎች የእርቅ ሃሳብ እንዲሰራበት ያቀረቡት ሃሳብ ግን በመደበኛ ስብሰባ አይደለም” ማለታቸውን ዘግበን ነበር፡፡
የዕርቁን ሃሳብ እንዲነሳ ያደረጉ ምክንያቶች በርካታ ቢሆኑም በዜና ዘገባው ላይ የቀረበው ቀዳሚ ሃሳብ “በህወሃትና ህወሃት በሚያዛቸው አቻ ፓርቲዎች መካከል ያለው የመከባበርና የመገዛት ስሜት ከመለስ ሞት በኋላ መበላሸቱ፣ በኢህአዴግም ሆነ በህወሃት ደረጃ የተፈጠረው ልዩነትና በሙስና ስም የተጀመረውን ዘመቻ ተከትሎ የተነሳው አለመግባባት አደጋ እንዳያስከትል መፈራቱ” ጎልጉል እንደ ምክንያት ጠቅሶ ነበር፡፡
ጎልጉል በዝርዝር ባሰፈረው በዚህ የዜና ዘገባ ላይ ምንጭ አድርጎ የጠቀሳቸው የኢህአዴግ አመራርና ዲፕሎማት በሰጡት አስተያየት ዕርቅ “በቅርብ ጊዜ ውስጥ የሚታይ ነው” ማለታቸውን ዘግቦ ነበር፡፡ ዲፕሎማቱ ሲቀጥሉም “አንዱ እኔ ነኝ። ሌሎችም አሉ። ብዙዎች ሰላማዊ ህይወት ናፍቆናል። የተወሳሰበውን አገራችንን ፖለቲካ አካሄድ ለመተንበይ ተቸግረናል። መፍትሔው የእርቅ ሃሳብ ብቻ ነው” ብለው ነበር።
አስተያየታቸውን ሲያጠናቅቁም “በድርጅታቸው ውስጥ የበላይና የበታች መጥፋቱን፣ የበታቹ የበላዩን እንደሚያዘው፣ አንዳንዴ የበላይ መስለው ምንም ዓይነት የውሳኔ ሰጪነት ሚና የሌላቸው ክፍሎች መኖራቸው የአደባባይ ምስጢር” መሆኑን አልሸሸጉም ነበር፡፡
በመጨረሻም በዕርቅ ሃሳብ ላይ ቀዳሚውን ቦታ የሚወስዱት ስብሃት መሆናቸውን ሲገልጹ “እርቅና ዋስትና የሚሰጥ አግባብ ቢያገኝ የመጀመሪያው ስምምነት ፈራሚና ደጋፊ ስብሃት ነው። ቀሪውን የጡረታ ዘመኑንን በትዝታ ያለውን እየበላ መኖር ይፈልጋል። እሱ ብቻ ሳይሆን ብዙዎች ተመሳሳይ ፍላጎት አለን። አስከማውቀው ድረስ ችግሩ ከራስ ምግባርና ከድርጅት ተልዕኮ በመነጨ የተሰሩት ጥፋቶችና ሃጢያቶች መብዛታቸው ከለውጥ በኋላ የሚያመጣቸው የተጠያቂነት ጣጣዎች ናቸው” ብለዋል፡፡

በህወሃት ውስጥ የዕርቅ ሃሳብ መነሳቱ ተሰማ

“የኢህአዴግ የአፈና ገመድ ነትቧል፣ ድርጅቱ ተናግቷል”

tplf1
November 4, 2013 10:19 pm
ኢትዮጵያ ግራ በሚያጋባና ሊተነበይ በማይችል የፖለቲካ ቀውስ ውስጥ መገኘቷን ያመኑ የህወሃት ሰዎች መካካል የእርቅ ሃሳብ ላይ ለማተኮር እቅድ እንዲያዝ ሃሳብ ማንሳታቸው ተሰማ። ኢህአዴግ የቀድሞው የአፈና ገመዱ መንተቡን የሚያሳዩ ምልክቶች መታየታቸውና አለመተማመን መንገሱ ተጠቆመ።
ጎልጉል መረጃ በመስጠት የሚታወቁ የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራርና ዲፕሎማት እንዳሉት ህወሃት ውስጥ “እርቅ አስፈላጊ ነው” በሚል እቅድ እንዲያዝና እንዲሰራበት ሃሳብ ቀርቧል። በድርጅቱ ውስጥ በተፈጠረ አለመተማመን ሳቢያ ስጋት የገባቸው የህወሃት ሰዎች የእርቅ ሃሳብ እንዲሰራበት ያቀረቡት ሃሳብ ግን በመደበኛ ስብሰባ አይደለም።
በህወሃትና ህወሃት በሚያዛቸው አቻ ፓርቲዎች መካከል ያለው የመከባበርና የመገዛት ስሜት ከመለስ ሞት በኋላ መበላሸቱ፣ በኢህአዴግም ሆነ በህወሃት ደረጃ የተፈጠረው ልዩነትና በሙስና ስም የተጀመረውን ዘመቻ ተከትሎ የተነሳው አለመግባባት አደጋ እንዳያስከትል ተፈርቷል። የመረጃው ምንጭ እንደሚሉት በጣም ጥቂት ካልሆኑ በስተቀር ከሙስና የጸዱ አለመኖራቸው “ማን ንጹህ ሆኖ ማንን ይጠይቃል?” የሚል ቅሬታ አስነስቷል።
ህወሃት ባሰበው በሁሉም መንገድ የበላይ ሆኖ ሊቀጥል እንደማይችል ከየድርጅቶቹ በቀጥታና በተዘዋዋሪ በስፋት እየተነገረ መሆኑንን ያነሱት እኚሁ ሰው፣ ይፋ ባልሆነ መንገድ የቀረበው እርቅን የመቀበል ጥያቄ በኦርቶዶክስ ሃይማኖት የሲኖዶስ ጉባኤ ላይ የተነሱት አስደንጋጭ ችግሮች ተከትሎ መሆኑን አልሸሸጉም።
ሊታመን በማይችልና ባልተለመደ መልኩ የሃይማኖት አባቶች ኢህአዴግን አንደበታቸውን ከፍተው በግልጽ ማውገዛቸውን፣ “አገሪቷን ገደላችኋት” በማለት መኮነናቸውን ተከትሎ በኢህአዴግ ዘንድ መደናገጥ እንደተፈጠረ ለማወቅ ተችሏል። የእምነት ጉዳይ ጥንቃቄ የሚያሻው በመሆኑ ዝርዝር መረጃ ከመስጠት የተቆጠቡት ዲፕሎማት “ኢህአዴግ በቀድሞው ፓትሪያርክ ፈቃድና ውዴታ ያደርግ እንደነበረው አሁንም በደኅንነት ሃይሎች ቤተክርስቲያኒቱን መቆጣጠርና አመራሮቹን አንደበታቸውን ማፈን የማይችልበት ደረጃ መድረሱን አምኖ ተቀብሏል። በዚህ ላይ ደግሞ እስካሁን ምላሽ ያላገኘ የድምጻችን ይሰማ ጉዳይ አለ” ኢህአዴግ እንደተምታታበት አመላክተዋል።
ሲኖዶሱ በጉባኤው ያነሳቸው ነጥቦች ኢህአዴግ ነገሮች ቀስ በቀስ ከእጁ እንደወጡበት የሚያሳይ እንደሆነ ያመለከቱት የኢህአዴግ ሰው “ቁጥራቸው ቀላል የማይባል የኢህአዴግ አባላት በልብ ከድርጅቱ ጋር እንደሌሉ ሪፖርት ቀርቧል። አብዛኛው አባልና ደጋፊ ባለሃብቶች የሚባሉትን ጨምሮ ሰላማዊ ለውጥ እንዲካሄድ ኢህአዴግ ወደ እርቅ መንገድ እንዲሄድ ይፋ (ኦፊሴላዊ) ባልሆነ መልኩ ያነሳሉ” በማለት ድርጅቱ የገባውን ስጋትና መሸርሸር ያስረዳሉ።
እርቅ ከተፈለገ ለምን በግልጽ አይቀርብም በሚል ለቀረበላቸው ሃሳብ ዲፕሎማቱ ምላሽ ለመስጠት አልፈለጉም። ይሁን እንጂ “ከማን ጋር ነው የምንታረቀው? እነማንን ነው ለእርቅ የምንጋብዘው? እርቅ ጠያቂ መሆን ያለበትስ ማን ነው?” የሚሉት በግልጽ ባይቀርቡም ተመሳሳይ የስጋት ጥያቄዎች እንዳሉ ሳይገልጹ አላለፉም።
በቅንጅት ጊዜም በተመሳሳይ የዕርቅ ፍላጎትና “ሥልጣን እናስረክብ” የሚል አቋም ተነስቶ እንደነበር ያስታወሱት ምንጫችን፤ በወቅቱ ሃሳቡ ተግባራዊ ያልሆነው “ወያኔዎችን ወደመጡበት ጠራርገን እንመልሳቸዋለን” በማለት አንድ የቅንጅት አመራር ለሕዝብ መፈክር ሲያወርዱ ከተሰማ በኋላ ነበር፡፡
በመከላከያ አዛዦችና በደህንነት የተለያዩ መምሪያዎች የሃላፊዎች ለውጥ እያካሄደ ያለው ኢህአዴግ ከአቻ ፓርቲዎች ጋር ውህደት በማድረግ ብሔራዊ ፓርቲ ለማቋቋም በሁለት ጉባኤዎች ሃሳብ ቢቀርብም ተግባራዊ አላደረገውም። ፓርቲው ህብረ ብሔር ከሆነ ህወሃት የገነባቸው የንግድ ድርጅቶችና በሞኖፖል የያዘውን ቁልፍ ስልጣን እንዲያጣ ስለሚያደርገው ጊዜ ሲያጓትት መቆየቱን ያመለከቱት የመረጃው አቀባይ “ይህ ፍርሃቻ አሁንም ሆነ ወደፊት ለሚፈለገው በሃሳብ ደረጃ ያለ እርቅ እንቅፋት ሊሆን እንደሚችል የውስጥ ለውስጥ ሃሜት አለ” ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል። ሆኖም እጅግ የተወሳሰበ የፖለቲካ ትወና ውስጥ ያሉት ካልሆኑ በስተቀር በማናቸውም መልኩ እርቅን ለመቀበል የማያቅማሙ እንደሚበዙ ግን አልሸሸጉም፡፡
በኢህአዴግ ውስጥ አለመተማመን መንገሱን የሚናገሩ ወገኖች “ለራሳቸው መተማመን ያቃታቸው ክፍሎች እንዴት ሌላውን አስማምተው ይመራሉ” በማለት መጠየቅ ከጀመሩ ቆይተዋል። በተለይም አዲሱ ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ወደ መንበሩ ከመጡ በኋላ አገሪቱ በደቦ መመራቷ የኢህአዴግን መሽመድመድ የሚያሳይ እንደሆነም እየተቹ ነው።
sebhat negaሁሉም ሰላም ነው፤ ልማት ነው፤ ዕድገት ነው፤ ህዳሴ ነው … በማለት አንድም ችግር የሌለበት ለመምሰል የሚሞክረው ህወሃት ደግሞ በውስጡ የመከፈል አደጋ አጋጥሞት እንደማያውቅ ምንነታቸውና የስራ ደርዛቸው በውል በማይታወቀው አቶ ስብሃት አማካይነት እያስታወቀ ነው። እሳቸው እንደሚሉት ችግር የህወሃት “ሰማያዊ ስጦታውና በረከቱ ነው” አቶ ሃይለማርያምም በበኩላቸው “ኢህአዴግ መካከል መከፋፈል አለ የሚሉ የዋሆች ናቸው” ሲሉ አንድነት የሰፈነበት አመራር እንዳለ ለማስተጋባት ሞክረዋል።
የእርቅ ሃሳብ ተሰንዝሯል በማለት መረጃውን የሰጡን ዲፕሎማት ግን ይህንን አይቀበሉም። “በቅርብ ጊዜ ውስጥ የሚታይ ነው። አንዱ እኔ ነኝ። ሌሎችም አሉ። ብዙዎች ሰላማዊ ህይወት ናፍቆናል። የተወሳሰበውን አገራችንን ፖለቲካ አካሄድ ለመተንበይ ተቸግረናል። መፍትሔው የእርቅ ሃሳብ ብቻ ነው” በሚል ተከራክረዋል።
በድርጅታቸው ውስጥ የበላይና የበታች መጥፋቱን፣ የበታቹ የበላዩን እንደሚያዘው፣ አንዳንዴ የበላይ መስለው ምንም ዓይነት የውሳኔ ሰጪነት ሚና የሌላቸው ክፍሎች መኖራቸው የአደባባይ ምስጢር እንደሆነ የሚናገሩት እኚሁ ሰው፣ “እርቅና ዋስትና የሚሰጥ አግባብ ቢያገኝ የመጀመሪያው ስምምነት ፈራሚና ደጋፊ ስብሃት ነው። ቀሪውን የጡረታ ዘመኑንን በትዝታ ያለውን እየበላ መኖር ይፈልጋል። እሱ ብቻ ሳይሆን ብዙዎች ተመሳሳይ ፍላጎት አለን። አስከማውቀው ድረስ ችግሩ ከራስ ምግባርና ከድርጅት ተልዕኮ በመነጨ የተሰሩት ጥፋቶችና ሃጢያቶች መብዛታቸው ከለውጥ በኋላ የሚያመጣቸው የተጠያቂነት ጣጣዎች ናቸው” ብለዋል፡፡
በኢህአዴግ ውስጥ ንጹህ ሰዎች አሉ ለማለት የማይቻልበት ደረጃ መደረሱን የሚያመለክቱት ዲፕሎማት፣ ህወሃትም ሆነ ኢህአዴግ አሁን የጋራ ነጠብ የሌላቸው፣ የርስ በርስ ትስስራቸው የላላና የተለያየ፣ አንዱ ሌላውን ለመንካትና ለመገምገም የሞራል ብቃት ያጣበት፣ እርስ በርሱ በወንጀል የሚጠቋቆምበት የውድቀት ጫፍ ላይ መድረሱን የውጪ አገር ወዳጆቹም ተረድተውለታል፤ አሁን ለእነርሱም ችግር የሆነባቸው ቁጭ ብለው ሥልጣን ላይ የሰቀሉትን ህወሃት አሁን ቆመው እንዴት ማውረድ እንደሚቻል መቸገራቸው ነው ብለዋል። የእርቅ ሃሳቡ ከውጪ አገር ወዳጆቻቸው ጋር የተያያዘ ስለመሆኑ ግን ፍንጭ አልሰጡም።
በህወሃትም ሆነ በኢህአዴግ ደረጃ የውስጥ ስጋት ቢኖርም “ሕዝብ እስኪ ዛሬን ልደር” በሚል የሞራል ውድቅት ውስጥ በከተተው ድህነት የተመታ በመሆኑ ለጊዜው ያምጻል የሚል ግምገማ አለመኖሩን ዲፕሎማቱ አመልክተዋል። ይሁን እንጂ ህዝብ በኢህአዴግ ደስተኛ አለመሆኑ፣ የጥበቃና የቁጥጥር መረቡ እንደወትሮው ትጋት ማጣቱ፣ የአካባቢ ስሜትና “ወገኔን ለምንና እስከመቼ አሳልፌ እሰጣለሁ?” የሚል አስተሳሰብ መበራከቱ፣ አጋጣሚ ተቃውሞ ቢነሳ መቋቋም እንደማይቻል፣ ረብሻ ከተነሳ የስርዓቱ ባለሟሎች ህልውና ጉዳይ አስጨናቂ እንደሚሆን ግንዛቤ ስለመኖሩ አላስተባበሉም። በማያያዝም እሳቸው በዚህ ደረጃ ስርዓቱን ከገመገሙና ችግሩን ከተረዱ በይፋ የማይከዱበትን ምክንያት ተጠይቀው “ለጊዜው በምስጢር ጠባቂነት የዝግጅት ክፍሉ ቃሉን ይጠብቅ። የቀረውን ወደፊት እናየዋለን” የሚል ድፍን መልስ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሰጥተዋል።

No comments:

Post a Comment