Translate

Friday, August 23, 2013

አቶ ኤርሚያስ አመልጋ በዚህ ወር መጨረሻ እንደሚመጡ ተጠቆመ

ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት የ73.3 ሚሊዮን ብር ክስ ተመሠረተበት

ermiyas
አቶ ኤርሚያስ ከአገር ከወጡ በኋላ ሳይመለሱ በዚያው የቀሩት፣ ቤት ሊገነቡላቸው የተዋዋሉዋቸው ሰዎች ቁጣና ዛቻን ብቻ ፈርተው ሳይሆን፣ አገር ቤት በነበሩበት ጊዜ ‹‹ግንባታው ይቅርብን ገንዘባችንን መልስ›› ላሏቸው ቁጥራቸው በውል ለማይታወቅ ሰዎች በጻፉት ደረቅ ቼክ ምክንያት መሆኑን ላነጋገሯቸው የቅርብ ጓደኞቻቸውና ወዳጆቻቸው መናገራቸው ተገልጿል፡፡ አቶ ኤርሚያስ ለደንበኞቻቸው የሰጧቸው ቼኮች ደረቅ በመሆናቸው በወንጀል እንደሚያስጠይቃቸው ስለሚያውቁ፣ በራሳቸውና በጓደኞቻቸው አማካይነት ቼክ የሰጧቸውን ደንበኞች በማነጋገር፣ የተቀበሉትን ገንዘብ ለመመለስ በመመስማማት ላይ መሆናቸውንና ክፍያውንም እንዳጠናቀቁ በዚህ ወር መጨረሻ እንደሚመለሱ መናገራቸውን፣ በቅርቡ የተቋቋመው ዓብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አክሎግ ሥዩም ገልጸዋል፡፡
እንደ አቶ አክሎግ ገለጻ፣ አቶ ኤርሚያስ የሚያዋጣቸው ወደ አገር ቤት ተመልሰው ለሠሩት ጥፋት ይቅርታ በመጠየቅ፣ ለተፈጠረው ችግር ከተጎጂዎች ጋር በመሆን መፍትሔ ማፈላለግ ነው፡፡ ይኼንን ባያደርጉ ግን በኢንተርፖል በኩል ተይዘው ታስረው እንደሚመጡ እሙን ነው ይላሉ፡፡ ከሁለት ሺሕ በላይ የሚሆኑ ተጎጂዎች ለፌዴራል ፖሊስ ያስገቡት ደብዳቤ፣ በቅርቡ ለተሾሙት የፌዴራል ፖሊስ ጄነራል ዳይሬክተር አቶ አሰፋ በዩ ደርሷቸው እያዩትና በቅርቡም ተግባራዊ ሊያደርጉት እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዳያስፖራ ዴስክም (ከ130 በላይ ዳያስፖራዎች ተጎጂዎች ናቸው) ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑንና መንግሥት ልዩ ትኩረት የሰጠው በመሆኑ፣ ለአቶ ኤርሚያስ የሚያዋጣቸው ራሳቸው ተመልሰው በመምጣት የችግሩን መፍቻ መንገድ አብረው ቢፈልጉ እንደሚሻል አቶ አክሎግ አክለዋል፡፡
ሌላው አቶ አክሎግ የገለጹት፣ የተጎጂዎቹን ገንዘብ የያዙና ከአክሰስ ጋር ይሠሩ የነበሩ ድርጅቶች ገንዘቡን ለመመለስና አብረውም ችግሩን በጋራ ለመፍታት የሚፈልጉ መኖራቸው ሲሆን፣ አንዳንዶቹ ደግሞ ‹‹አያገባንም›› ያሉ መኖራቸው ነው፡፡ ነገር ግን መንግሥት ሳይቀር የዜጎችን መጉላላትና መጎዳት ተመልክቶ እየተንቀሳቀሰ ባለበት ሁኔታ፣ የዜጎችን ገንዘብ ‹‹አያገባኝም›› በሚል ለማስቀረት መሞከራቸው ስለማያዋጣቸው፣ በሰላም ከተጎጂዎቹ ጋር በመሆን የወሰዱትን ገንዘብ በመመለስ የመፍትሔው አካል እንዲሆኑ የኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ አክሎግ ጠይቀዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ለአክሰስ ሪል ስቴት 40 ከመቶ ድርሻውን የሰጠውና 60 በመቶ የሚሆነው ከፍተኛ ባለድርሻ የሆነው ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ‹‹ከአክሰስ ሪል ስቴት ጋር በመሆን ቪላና አፓርትመንት እገነባላችኋለሁ በማለት ውል ካስገባን በኋላ ውላችን ሳይፈጸምልን ገንዘባችንን ከወሰደ አንድ ዓመት ሞልቶታል፤›› በሚል፣ 137 ደንበኞች የ73,388,844 ብር ከ50 ሳንቲም ክስ መሥርተውበታል፡፡ ክሱ የተመሠረተው በፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት፣ በአክሰስ ሪል ስቴት በአቶ ነብዩ ሳሙኤልና በአቶ ኤርሚያስ አመልጋ ላይ ነው፡፡
የክሱ ዋና መነሻ ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል እስቴት በየካ ክፍለ ከተማ የቀድሞ ቀበሌ 20/21 አያት ኢስት ቪው (መሪ) አካባቢ በወሰደው 50 ሺሕ ካሬ ሜትር የሊዝ ቦታ ላይ ይገነባል የተባለው ቪላና አፓርትመንት ነው፡፡ ጉዳት እንደደረሰባቸው በመግለጽ ክስ የመሠረቱት 137 ደንበኞች ከፓስፊክ ሊንክና አክሰስ ጋር በፈጸሙት ውል መሠረት፣ በ14 ወራት ውስጥ ቤቱን ገንብተው ሊያስረክቧቸው ውል የገቡ ቢሆንም፣ እንኳን ቤት ሊገነቡ ቀርቶ ግንባታ ካቆሙ አንድ ዓመት እንደሞላቸው በክሱ ጠቅሰዋል፡፡ የተወሰኑ የተጀመሩ ቤቶችን አጠናቀው ለተወሰኑት ከማስረከብ ባለፈ ሌላውን እንደማይችሉ እንደገለጹላቸውም ከሳሾቹ አክለዋል፡፡ ሪል ስቴቶቹ በአንድነትና በነጠላም ኃላፊነት እንዳለባቸውና አቶ ነብዩ ሳሙኤልና አቶ ኤርሚያስ አመልጋ የድርጅቶቹ ሥራ አስኪያጅ በመሆናቸው ተጠያቂ እንደሚሆኑም በክሱ ተካቷል፡፡
የአክሰስ ሪል ስቴት ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ኤርሚያስ ለፍርድ ቤቱ ምላሽ ባይሰጡም፣ የፓስፊክክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ነብዩ ሳሙኤል ፍርድ ቤት ቀርበው ምላሽ መስጠታቸውን ገልጸዋል፡፡ የታዋቂው ጋዜጠኛ ሳሙኤል ፈረንጅ የመጀመሪያ ልጅና የኢትዮጵያ ብስክሌት ፌዴሬሽን የበላይ ጠባቂ የሆኑት አቶ ነብዩ፣ በአሜሪካ ለ23 ዓመታት ከቆዩ በኋላ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ዳያስፖራዎች ወደ አገራቸው ገብተው ኢንቨስት ማድረግ እንዳለባቸው ያደረጉትን ጥሪ ተከትሎ፣ እ.ኤ.አ ኦገስት 11 ቀን 2003 ወደ ትውልድ አገራቸው መመለሳቸውን ገልጸዋል፡፡
እሳቸው ወደ አገር ቤት በተመለሱበት ወቅት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ዳያስፖራዎችን ያበረታታ የነበረው በሪል ስቴት የሥራ መስክ እንዲሰማሩ ስለነበር፣ እሳቸውም ‹‹ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ሪል ስቴት›› የሚል ድርጅት አቋቁመው አያት መሪ አካባቢ 50 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ መውሰዳቸውን ገልጸዋል፡፡ ከሌሎች ከሚሠሯቸው ቢዝነሶች ጎን ለጎን የቤት ልማት ፕሮግራሙን ለማካሄድ ከአስተዳደሩ በፊት በዋነኛነት ያነሳሳቸው፣ የቢዝነስና ኮንስትራክሽን ባንክ በወቅቱ 30 በመቶ መክፈል ለሚችል ሪል ስቴት አልሚ 70 በመቶ ብድር እንደሚሰጥ በማስታወቁ መሆኑን አቶ ነብዩ አውስተዋል፡፡
ፓስፊክ ሊንክ 50 ሺሕ ካሬ ሜትሩን በካሬ ሜትር 401 ዶላር ሒሳብ 250 ሺሕ ዶላር ከፍለው ለ20 ዓመታት የሊዝ ውል መፈጸሙን  የገለጹት አቶ ነብዩ፣ የወሰዱትን ቦታ አስተካክለው ወደ ግንባታ እንደገቡ 70 በመቶ ብድር እንደሚሰጥ ቃል ገብቶ የነበረው ኮንስትራክሽንና ቢዝነስ ባንክ፣ እሰጣለሁ ያለውን ብድር መተውን በመግለጹ የፋይናንስ ችግር አጋጥሞት እንደነበር አስረድተዋል፡፡ በወቅቱ (ከሦስት ዓመት በፊት) ሊቪንግ ስቲል (አሁን ይበል ኮንስትራክሽን ተብሏል) ለሚባል ድርጅት ሙሉ ፋይናንስ የሚያቀርብለት አክሰስ ሪል ስቴት መሆኑን በጓደኞቻቸው አማካይነት ያወቁት አቶ ነብዩ፣ እሳቸውም የሪል ስቴቱን ባለቤት አቶ ኤርሚያስን አግኝተው ቢያነጋግሯቸው ሊረዷቸው እንደሚችሉ ሲነገራቸው አቶ ኤርሚያስን ሊተዋወቋቸው መቻላቸውን ተናግረዋል፡፡ ሊቪንግ ስቲል የሚባለው ድርጅትን አክሰስ ሙሉ በሙሉ ፋይናንስ አድርጎት ይሠራ ስለነበር፣ አቶ ነብዩ አቶ ኤርሚያስን ሲያነጋግሯቸው ፈቃደኛ በመሆናቸው፣ ሥራውን ለመሥራት በሕጋዊ መንገድ በውልና ማስረጃ መዋዋላቸውን አክለዋል፡፡
ፓስፊክ ሊንክና አክሰስ ያደረጉት ውል የሕንፃ ግንባታ ወጪው ስለማይታወቅ ግንባታውን ሲጨርሱ ወጪያቸውን በማስላት ትርፉን አክሰስ 40 ከመቶ እንዲወስድና ፓስፊክ ሊንክ 60 ከመቶ ሊወስድ በመስማማት ሥራ መጀመራቸውን አቶ ነብዩ ገልጸዋል፡፡ ፓስፊክ ሊንክ የባንክ ሒሳቡ ኅብረት ባንክ ቢሆንም ለሪል ስቴት ሥራው አመቺ እንዲሆን የሚል ጥያቄ አቶ ኤርሚያስ በማቅረባቸው ዘመን ባንክ ሒሳብ እንዲከፍትና በአቶ ኤርሚያስ ብቻ እንዲንቀሳቀስ ማድረጋቸውን የገለጹት አቶ ነብዩ፣ ፓስፊክ ሊንክ ከስምምነታቸው ውጭ ቤት እንዳይሸጡ ደረሰኞቻቸው በማይከፈት ካዝና ውስጥ እንዲቀመጥ ማድረጋቸውንና ለአንዳንድ ሥራ አመቺ እንዲሆን በማለት የፓስፊክ ማህተምንም በዕምነትና በፊርማ ለአቶ ኤርሚያስ መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡
ሁሉንም ውል ወይም ስምምነት ሲያደርጉ ብቻቸውን ሳይሆን አሁን ከሳሽ ለሆኑት ቤት ገዢዎች ጠበቃ የሆኑ ግለሰብን እያማከሩና እሳቸው ያሏቸውን (ቀድሞ የእሳቸው ተቀጣሪ ጠበቃ ነበሩ) ማድረጋቸውን የገለጹት አቶ ነብዩ፣ በመሀል ላይ መንግሥት የሪል ስቴት ሥራን ለጊዜው ሲያስቆም ከመቆሙ በስተቀር ያለምንም ችግር ይሠሩ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ አክሰስ ሪል ስቴት አሁን በፈጠረው ችግር ውስጥ ፓስፊክ ሊንክ ምንም የሚያውቀውና የተሳተፈበት ነገር እንደሌለ የገለጹት አቶ ነብዩ፣ አክሰስ ግንባታ ሲያቆም ‹‹ለምን?›› የሚል ጥያቄ ሲያነሱ ‹‹ግንባታው የጥራት ጉድለት ስላለበት፣ ጥራትን በሚመለከት የእኛና የመንግሥት መሀንዲሶች ቻይና ተልከው እያጠኑት ስለሆነ፣ እነሱ እስከሚመለሱ እንዲቆም ተደርጓል፤›› ሲሏቸው ዝም ብለው ማለፋቸውን አስረድተዋል፡፡
አቶ ነብዩ አብዛኛውን ጊዜያቸውን የሚያሳልፉት አሜሪካ መሆኑን ተጠቅመው አቶ ኤርሚያስ በእምነት የሰጧቸውን ደረሰኞችና ማህተም በመጠቀም ቤት ይሸጡ እንደነበር የተረዱትም ፍርድ ቤት ተከሰው ማስረጃ ሲቀርብባቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ መከሰሳቸውን ሰምተው ሲመጡ የሰሙትንና የተደረገውን ማመን ቢያቅታቸውም፣ ፍርድ ቤት ቀርበው የቀረበባቸውን ክስ ከሰሙ በኋላ ለክሳቸው ምላሽ መስጠታቸውን አስረድተዋል፡፡
ክስ ከመሠረቱባቸው የአክሰስ ደንበኞች ውስጥ አምስት በመቶ የሚሆኑት ብቻ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ነብዩ፣ ከ95 በመቶዎቹ ጋር ቀርበው በመነጋገር ፓስፊክ ከያዘው ቦታና ሌሎች የአክሰስ ቦታዎችን አንድ ላይ በማልማት ችግሩን በጋራ ለመፍታት እየሠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ አዲስ የተቋቋመው ኮሚቴና አዲሱ የአክሰስ ሪል ስቴት ቦርድም መስማማታቸውንና ችግሩን ለመፍታት አብረው ከመሥራት በዘለለ አቶ ኤርሚያስ ወደ አገር ቤት ተመልሰው ችግሩን አብረዋቸው እንዲፈቱ ጥረት እያደረጉ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
‹‹በአገሬ ላይ የቻልኩትን ያህል አስተዋጽኦ አደርጋለሁ ብዬ ከ23 ዓመታት የውጭ አገር ቆይታ በኋላ ስመለስ ስሜን በማይሆን ነገር እንዲጠፋ አልፈልግም፤›› ያሉት አቶ ነብዩ፣ ወደ ፍርድ ቤት የሄዱት ደንበኞች ክሳቸውን አቋርጠው በጋራ ሆነው ችግሩን የሚፈቱበትን መንገድ ቢፈልጉ ደስታቸው ቢሆንም፣ ‹‹ሕግን ተከትለን መሆን ያለብንን እንሆናለን›› የሚሉ ከሆነ ግን መብታቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እነሱ ከአክሰስ ጋር ያደረጉትን ውል ፓስፊክ ሊንክ ኢትዮጵያ ዕውቅና ሊሰጥ እንደማይችል የገለጹት አቶ ነብዩ፣ ተስማምቶ በመሥራት ቸግርን ማቃለል ተገቢ መሆኑን አምኖበት ከሚመጣ ጋር ለመሥራት ግን ፈቃደኛ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ (ምንጭ: ሪፖርተር)

No comments:

Post a Comment