Translate

Wednesday, September 16, 2015

” ከእንካሰላንታው ባሻገር” ኤርሚያስ ለገሰ

የሰሞኑን የኢትዬጲያ ፓለቲካ ለተከታተለ ሰው የትግሉ ጫፍ ወዴት እየሔደ እንደሆነ ለመገመት አያዳግተውም። …በአንድ በኩል ላለፋት ሁለት አስርተ አመታት የበላይነቱን ያስጠበቀው አናሳ እና ዘረኛ ቡድን አሁንም ከማንም በላይ የደም ሀረጉን በመምዘዝ ለመሰባሰብ እየተጋ ያለበት ነው። …በሌላ በኩል ሁሉን አቀፍ ትግል የመረጡ በብሔርም ሆነ በሕብረ ብሔራዊነት የተደራጁ ሀይሎች ሀይላቸውን በማቀናጀት በጋራ ለመስራት እየተመካከሩ ያለበት ሁኔታ ነው። እነዚህ ሁለት እንቅስቃሴዎች ከፓለቲካ ፓርቲ እና የድርጅት ህልውና ባሻገር ከኢትዬጲያ ህዝብ የነጳነት ትግል መቀጠልና ወደ ኃላ መመለስ ጋር የተቆራኙ ናቸው። ርግጥም የእነዚህ ሁለት አካላት የፍልሚያ ውጤት የወደፊቱን የኢትዬጲያ እጣ ፋንታ የመወሰን እድሉ ከፍተኛ ነው።

1• ” አናሳ እና ዘረኛው ቡድን”
የመጀመሪያው እድል ከፓለቲካ ፕሮግራም እና ብቃት ይልቅ የማንነት ደም ያስተሳሰራቸው አናሳ ቡድኖች በኢትዬጲያ ህዝብ ጫንቃ ላይ እንደ መዥገር ተጣብቀው፣ እንደ በረሮ(?) ከክብደታቸው በላይ የሚበሉበት ሁኔታ መፈጠሩ ነው። ያለማጋነን የዛሬይቱ ኢትዬጲያ በጥቁር ደም በተሞሉ መዥገሮችና ቁንጣን በያዛቸው በረሮዎች ተወራለች። የአናሳው ቡድን ተስፈኞችም ህዝባችን ላይ የተጋረጠ አደጋ በማለት ወደዚህ ቡድን እየተሰባሰቡ ነው። የትግራይን ህዝብ ካባ በማጥለቅ የራስን የስልጣን ፍላጐት ለማርካት ጥረት እየተደረገ ነው። በተባራሪ እንደሰማነው የተቃዋሚ አመራሮች ነን የሚሉና ብሄራዊ ማንነታቸው ሁሌም የበላይ እንደሆነ እንዲቀጥል የሚፈልጉትም በዚህ ጐራ የሚካተቱ ናቸው። አንዳንድ ምልክቶችም እየታዩ ነው።በህውሀት ጉባኤ አንዱ ተነስቶ ውይይት የተደረገበት እነዚህን ተቃዋሚዎች ( አቤ ቶኪቻው “የስጋ ዘመዶች ” ይላቸዋል) በመለየት ቢያንስ የማለዘብ ስራ የመስራት አስፈላጊነት መሆኑ የውስጥ መረጃዎች ያመላክታሉ። መጀመሪያ በሀገር ውስጥ ያሉ የተቃዋሚ ስያሜ የተሰጣቸው ቡድኖች የቅድሚያ ትኩረት አግኝተዋል። በማስከተል ወደ ተለያዩ ሀገሮችም አማላይ ቡድኖችን ለመላክ ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ ያለበት ሁኔታ ነው። በቅርቡ ወደ ሰሜን አሜሪካ መጥተው የነበሩ ግብረሀይሎች አንዱ ተልእኮ ይህ እንደነበረ ይገመታል። ወደ አውሮፓም የሚሄዱ ( በተለይም የቀድሞ ህውሀት አመራሮችን የሚያናግሩ) የህውሀት ቡጅሌዎች እንደሚኖሩ ይጠበቃል።
ይሔ በአናሳ ብሔር ስም የተሰባሰበ ቡድን በአሁን ሰአት እየተከተለ ያለው ስትራቴጂ ዋነኛ ማጠንጠኛ የትግራይ ህዝብ እና ሌላው የኢትዬጲያ ማህበረሰብ በባላንጣነት እና ጠላትነት እንዲተያይ ማድረግ ነው። ይሄ ቡድን ለዘር ማጥፋት እንደ አንድ ምልክት ተደርጐ የሚቆጠረውን ” እኛ እና እነሱ!” የሚለውን አባባል ወደ ተግባር ለመለወጥ ወገቡን ታጥቆ እየሰራ ነው። ይህ አናሳ ቡድን ኃላቀር በሆነ የፓለቲካ ባህል የተተበተበ በመሆኑ የትግራይን ህዝብ ለማደናገር በዘረኝነት እየቀሰቀሰ ነው። የትግራይን ህዝብ ከሌላው ኢትዬጲያዊ በመለያየት እና በማናቆር አገዛዛቸውን ለማራዘም ወገባቸወን ጠበቅ አድርገው እየሰሩ ነው። ይህ አናሳ ቡድን የተቀረው የኢትዬጲያ ህዝብ እንዲያውቅላቸው የሚፈልጉት ነገር አለ። ይኸውም እርስ በእርሳቸው ቅራኔ ቢፈጠር እንኳን ” በአንድ ጐጆ ስር” የተፈጠረ ልዩነት አድርጐ የኢትዬጲያ ህዝብ እንዲወስድ ይፈልጋሉ። ለዚህም ነው ከአስርተ አመታት በላይ በኤርትራ የመሸገውን የትግራይ ንቅናቄ በአሸባሪነት በፓርላማ እንዲፈረጅ ያላደረገው። በተቃራኒው ከእሱ ያነሰ እድሜ ያለው ግንቦት ሰባት በአሸባሪነት እንዲመደብ ያደረገው። …
…ለዚህም ነው ኤርትራ የመሸገውን ደህሚት “የኤርትራ ሀይል ( የኢሳያስ ጠባቂ)” የሚል ስያሜ እንዲሰጠው ያደረገው። …ለዚህም ነው ደህሚት ያሉት አባላት ከ300 አይበልጡም የሚል አሰልቺ ፕሮፐጋንዳ ለተራዘመ አመታት እንዲስተጋባ ያደረገው።…ለዚህም ነው አይኑን በጨው አጥቦ በግላጭ የተናገረውን በማጠፍ ዛሬ ደግሞ በሶስት እጥፍ ቁጥራቸውን አሳድጐና አጀግኖ ነገሪት እየጐሰመ ተቀበልኳቸው የሚለን። …ለዚህም ነው እነዚህ ትግሉን ወደ ተሻለ ደረጃ ማሻገር ያቃታቸው ” የጦጣ ዘር አቀባዬች” መንገዋለላቸውን አውቀው ቅሬታ ሲያዝሉ መንገድ ላይ አፈፍ አድርጐ ” ለእኛ እና እነሱ” የውድመት ስትራቴጂው የተጠቀመበት። …
…ለዚህም ነው በተቀረው ኢትዬጲያውያን ዘንድ ” ዘሮች ሁሉ እኩል ናቸው፣ አንዳንድ ዘሮች ግን የበለጠ እኩል ናቸው” የሚለው አባባል ገዥ አስተሳሰብ እንዲሆን ያደረገው። …ለዚህም ነው ” ፕሮፌሰሩ ወደ ጫካ እንዲገባ ያደረግነው እኛ ነን!” ያለው አንደበታቸው ሳይዘጋ ” ኢሳያስ ፕሮፌሰሩን ወደ ሜዳ እንዲወርድ አደረገው” የሚል ቅጥፈት ሲናገሩ የማይሸማቀቁት። እኔ እምለው ኢሳያስ አፈወርቂና አባይ ወልዱ (ዶክተር ደብረጲዬን) እየተመካከሩ መስራት ጀመሩ እንዴ?…መቼስ ” የአህያ በሬ!” የሆነው “ደ -ሳአ -ለ -ኝ!” እና ሌሎች ባለሟሎች የዚህ አካል ነው ብሎ ማመን ከቧልት አይዘልም ብዬ ነው።
ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ አንዳንድ በሚኒስትር እና ፓርላማ ደረጃ ያሉትን ባለሟሎች ሁለት ጥያቄ ልጠይቅ። ክቡር ሚኒስትሮች! ለመሆኑ ” የፀረ ሽብርተኝነት ግብረሀይል አባላት” እነማን እንደሆኑ ታውቃላችሁ?… ክቡራን ሚኒስትሮች እና የሸንጐ አባላት ደእሚት የሽብርተኝነት አዋጁ ከመውጣቱ ስድስት እና ሰባት አመት በፊት የተቋቋመ እንደሆነ መንገር ለቀባሪው ማርዳት ይሆንብኛል። ታዲያ በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅራቢነት፣ በወይዘሮ አስቴር ማሞ አንባቢነት፣ በተከበረው ፓርላማ አጵዳቂነት ለምን በሽብርተኝነት አልተፈረጀም??
2• ” The Law of the Few!”
ሁለተኛው እድል አምባገነናዊ ስርአቱ እየደቀነ ያለውን አደጋ በአግባቡ በመረዳት የስርአት ለውጥ መምጣት እንዳለበት ያመኑ ሀይሎች ቅሌን ጨርቄን ሳይሉ በትብብር የሚሰሩበት ሁኔታ መፍጠር ነው። ትብብርም እንበለው ንቅናቄ የመጨረሻው ግቡ በጠመንጃ ስልጣን ያለመያዝ፣… በኢትዬጲያ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ለመገንባት መደላድል መፍጠር፣ …ሁሉን የሚያቅፍ ምቹ ሁኔታ መፍጠር እስከሆነ ድረስ በጋራ ለመስራት የሚያስቸግረው አይደለም። የትብብር አላማ እና ግቡ ግልጵ እስከሆነ ድረስ በጥቂቶች ቢጀመርም (“The Law of the few”) ነገ እልፎችን የሚያሰልፍ ጥቂቶችን እያራገፈ የሚሄድ መሆኑ ሳይንሳዊ ነው። በተጨባጭም እየታየ ያለው እውነታ የዚህን ሳይንሳዊ አባባል የሚያፀና ነው።
እንደ እውነቱ ከሆነ የሰሞኑን የጥቂት የለውጥ ሀይሎች እንቅስቃሴ ስመለከት የሚያስታውሰኝ የማልኮም ግላድዌል የሚባለው ፀሀፊ የጳፈው የሊደርሺፕ መጵሀፍ ነው። ማልኮም ” Tipping point: How little Things make Big Differences” በሚለው መጵሀፋ ህዝባዊ ንቅናቄ (ማእበል) የሚቀሰቀሰው በጥቂት የቆረጡ ሰዎች እንደሆነ ያስረዳል። በእሱ እምነት መሰረት መሰረታዊ የለውጥ ሂደት ( ህዝባዊ ንቅናቄ) ለማቀጣጠል ወሳኞቹ ጥቂቶች ናቸው። ርግጥ እነዚህ ህዝባዊ ንቅናቄ ፈጣሪዎች ራእይ ያላቸው፣ ራእያቸውን ለማስፈፀም ስትራቴጂና አቅጣጫ የመንደፍ ክህሎት፣ የማደራጀት ብቃት፣ በህዝባዊ ማእበል ሊያነሷሷቸው ከሚፈልጉት ማህበረሰብ ጋር የተሻለ ተቀባይነት፣ እንዲሁም አለም አቀፍ እና አገራዊ ሁኔታውን ለመተንተን የሚያስችላቸው ብቃት ያላቸው ሊሆን ይገባል።
ከላይ የተቀመጠውን ሀልዬት መሰረት በማድረግ እነዚህ ጥቂት የለውጥ ሀይሎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ሶስት አበረታች ውጤቶችን ያስመዘገቡ ይመስለኛል። እነዚህም፣
2•1 ምን አይነት ትግል
በእነዚህ ጥቂት የለውጥ ሀይሎች ከአመታት በፊት ሲቀነቀን የነበረው ” በኢትዬጲያ ውስጥ መሰረታዊ ለውጥ ለማምጣት ሁሉን አቀፍ ትግል መካሔድ አለበት” የሚለው የፀና አቋማቸው በኢትዬጲያ ምድር ላይ ገዥ መሬት ተቆናጦ የአብዛኛው አስተሳሰብ ወደ መሆን ተቀይሯል። በዛሬይቱ ኢትዬጲያ አናሳው ዘረኛ ቡድን የበላይነቱን እስከያዘ ድረስ የምርጫ ፓለቲካ እንደ እባብ አፈር ልሶ የመነሳት እድሉ አልቦን በአልቦ የማባዛት ያህል ሆኗል። ከእንግዲህ በኃላ ብረት እና ህዝባዊ እንቢተኝነት ተዋህደው (Synergy) ፈጥረው እስካልተንቀሳቀሱ ድረስ በሌላ መንገድ ለውጥ አመጣለው የሚለው አካሄድ የተዘጋ ፋይል ሆኗል። እንደ እውነቱ ከሆነ በአሁኑ ጊዜ ” ብሔራዊ መግባባት”፣ ” ህገ መንግስት”፣ ” ምርጫ ቦርድ”፣ ” ተፎካካሪ ፓርቲ” …ወዘተ የሚሉ አባባሎችና ተቋማት ” ከኢቲቪ እና የመለስ አካዳሚ” ከሚባሉት ስፍራዎች የዘለለ ቦታ የላቸውም። ዛሬ በኢትዬጲያውያን ዘንድ ያለው አስተሳሰብ በጉልበት ረግጦ የሚገዛ ሀይል የሚወገደው በጉልበት ብቻ እንደሆነ መግባባት ላይ ተደርሷል።
2•2 የለውጥ ሀይሎችን ማብዛት
እነዚህ ጥቂት የለውጥ ሀዋርያዎች በወሰዱት እርምጃ ባልተጠበቀ ሁኔታ የደጋፊያቸውን ሀይል ማሳደግ ችለዋል። በርካታው ህዝብ ( የሚቃወሟቸውን ሳይቀር) በወሰዱት እርምጃ አክብሮት እንዳለው ማሳየት ችለዋል። እነዚህ የለውጥ ሀይሎች የሚታመኑ እና የሚሰሙ በመሆናቸው መላውን ኔትወርክ ለመቆጣጠር ችለዋል። ዛሬ አብዛኛው ማህበራዊ ድረገጶችና ሚዲያዎች የተሸፈኑት በእነዚህ ሰዎች የእለት እንቅስቃሴ ሆኗል። በመላው አለም እነሱን ለመደገፍ የሚጠሩ ስብሰባዎች የህዝብ ማእበል እያጋጠማቸው ነው። እናቶች የጣት ወርቃቸውን አውልቀው እስከመስጠት ደርሰዋል። በየአህጉሩ ጠንካራ ተከታዬችን በማፍራት ላይ ናቸው። ባጭሩ ትንሹ መዘውር ትልቁን ማንቀሳቀስ ጀምሯል። ትልቁ መዘውር በተሟላ ሁኔታ መንቀሳቀስ ከጀመረ የሚያቆመው አይኖርም…The law of few!
እዚህ ላይ አንድ ነገር ላንሳ። እነዚህ በአናሳ ብሔር ገዥ መደብ ዙሪያ የተሰባሰቡ ዘረኞች እና ባለሟሎቻቸው ዘወትር ከአፋቸው የማትጠፋ የፕሮፐጋንዳ ቃል አለች። ይህቺም ” የዲያስፓራወን ገንዘብ አታሎ ለመውሰድ! ” ትላለች። እንደ እውነቱ ከሆነ ይሕቺን ቃል ከድሮ የትግል ጓደኞቼ አፍ ስሰማ ከመጠን በላይ እሸማቀቃለሁ። በአንድ በኩል አዳራሽ እየሞላ የሚፈሰውን ዲያስፓራ (በውጭ የሚኖር ኢትዬጲያዊ) ማገናዘብ የማይችል በነዱት የሚነዳ ማህበረሰብ አድረገው እየቆጠሩት ነው። ርግጥ ነው አዲሳአባን ተራራ ላይ ሆኖ ሲያያት በምሽት ፀሀይ የወደቀችበት መሰለኛ ያለው የትላንት ታጋይ ( የዛሬው በአሜሪካ ኤምባሲ ንግግር ለማድረግ የሚጋበዝ ኮረኔል) ይህንን ቢል የሚያስከፋ አይደለም። ነገር ግን የውጭውን አለም ከሚያውቁት እነ አምባሳደር ግርማ ብሩ አፍ ሲወጣ ግን ያሸማቅቃል። በነገራችን ላይ በቅርብ ጊዜ የለውጥ ሀይሎቹን ለመደገፍ በተጠራ ህዝባዊ ስብሰባ ተገኝቼ ነበር። እናም በስብሰባው ላይ የለውጥ ሀይሉን ለመደገፍ ከመጡት ኢትዬጲያውያን ሁለቱ የህግ ዶክትሬት ነበራቸው።… ሁኔታው ስለገረምኝ ወደ አዱገነት በሀሳብ ሄድኩኝ። መልስ ባጣ አምባሳደሬን መጠየቅ ፈለኩ። እንዲህ በማለት ብጠይቅስ፣
ጋሽ አምባሳደር ግርማ ብሩ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ስንት የህግ ዶክትሬት ያላቸው መምህራን እንዳሉ እንድትነግረን ከማክበር ጋር እጠይቃለሁ!!
2•3 የለውጥ ተውሳኮችን ማንገዋለል
ጥቂቶቹ የለውጥ ሀይሎች ያስመዘገቡት ሁለተኛ ውጤት ትግሉን ወደ ፊት ማራመድ የተሳናቸውን የበረሀ አመራሮች በአጭር ጊዜ ማንገዋለል መቻላቸው ነው። ሞላ አስክዶም እንደነገረን ላለፋት አስራ ምናምን አመታት በወር ሀያ ምናምን ሺህ ብር እየተከፈለው፣ የፈለገውን ምግብ እየበላ፣ ከአንደኛው አልጋ ወደ ሌላኛው እየተዘዋወረ ( ስንት ጊዜ ከአልጋ እንደወደቀ የህማማት እለት እንደምንሰማ ተስፋ አድርጌ!) የኖረ ሰው ነው። በሌላ በኩል በእሱ ስር ባሉት ሰፊ ጦር ምክንያት በሌለው አቅሙ የወታደራዊነት (Militarism) አመለካከት እንዲያዳብር አድርጐታል። በመሆኑም ትግሉን ፈቀቅ ማድረግ ተስኖት በቁጥር ተኮፍሶ የመኖር ሂደቱትን ገፍቶበታል። የዘር ምንጩም ሆነ አስተዳደጉ ከህውሀት ነውና ለእሱ የትምህርት፣ችሎታና ብቃት ጉዳይ ከግምት የሚገባ አይደለም። ሁሉም ዘሮች እኩል ናቸው፣ ሌሎች የበለጠ እኩል ናቸው እንዲሉ!…እንግዲህ ይህ የጓድ ሞላ አይብን( cheese) ጠብቆ የመኖር ህልውና በለውጥ ሀይሎች ተሰናከለ። የእሱን አባባል እንደ ወረደ ልውሰደውና ሀያ ምናምንቴ ሺህ ብር የነበረችው ደሞዝ ልትቀር ሆነ! …በየጊዜው የምትታረደው ጥቦት ልትቀር ነው!…ከአልጋ አልጋ እየተገላበጡ መውደቅ ልትቀር ነው! …ታዲያ ምን ይዋጠው!…ለማንኛውም “Who moved Molla’s cheese?” ብዬ ብሰናበት ምን ይለኛል??

No comments:

Post a Comment