Translate

Monday, September 14, 2015

የዴምህት ሊቀመንበር አቶ ሞላ አስግዶም ለምን ከዱ?

(ECADF) – የትግራይ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ዴምህት) ከአርበኞች ግንቦት7፣ ከአፋር ድርጅቶች የጋራ ንቅናቄ እና ከአማራ ዲሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ ጋር ጥምረት መመስረቱን ባወጀበት ማግስት የጥምረቱ ምክትል ሊቀመንበር ሆነው የተሾሙትና ዴምህትን ለዓመታት ሲመሩ የኖሩት አቶ ሞላ አስግዶም መክዳታቸው ታውቋል።Former TPDM chairman Mola Asgedom
ኢሳት በአጭር ሰበር ዜና ዘገባው እንደገለጸው ከሆነ አቶ ሞላ አስግዶም ድርጅታቸው ጥምረት እንዲመሰርት ፍላጎት አልነበራቸውም። ይሁንና አብዛኛው የዴህምህት አመራሮች ጥምረቱን በመፈለጋቸው ምክንያት ጥምረቱ እውን ሊሆን ችሏል።
ፋሲል የኔዓለም (የኢሳት ጋዜጥኛ) ወደ ኤርትራ ተጉዞ በነበረበት ወቅት ከአቶ ሞላ አስግዶም ጋር የመወያየት እድል አግኝቶ ነበር። የአቶ ሞላ አስግዶም መክዳት ከተሰማ በኋላ ፋሲል እንዲህ በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል፣

“የደሚህቱ ሞላ አስገዶም መክዳቱን ስሰማ በእጅጉ ተገርሜአለሁ። ከቀናት በፊት ሞላ ፣ ሰው አክባሪ፣ ተግባቢና አገሩን የሚወድ ሰው መሆኑን ጽፌ ነበር። ኤርትራ በነበርኩበት ጊዜ ደጋግሜ አግኝቸዋለሁ ፣ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ጊዜ ወስደን ተነጋግረናል። እስከዛሬዋ ቀን ድረስ ስለሞላ የነበረኝ አመለካከት ቀደም ብዬ የገለጽኩት ነው። ስለእውነት እመሰክራለሁ፣ ኤርትራ በነበርኩበት ወቅት አንድም ቀን በሰላይነት እንድጠረጥረው ወይም በወያኔነት እንድፈርጀው የሚያደርግ ነገር አላነበብኩም። ከህወሃት ጋር የሚጋራቸው አቋሞች ቢኖሩም፣ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ የማይናወጽ አቋም እንዳለው፣ ህወሃት ኢትዮጵያን ታሪክ አልባ በማድረጉ በጣም እንደሚያዝን ነግሮኛል።
ከእርሱ ጋር የተግባባንበት የመጨረሻው ነጥብም ይህ ነበር- ህወሃት ኢትዮጵያን ከመበታተኑ በፊት እንድረስላት። ጥምረትን በተመለከተም በተወሰነ ደረጃ አስፈላጊነቱን ያምናል። ደሚት ያለውን የሰራዊት ብዛትና ሃብት ሲያስበው ደግሞ፣ ከደሚህት ያነሰ የሰራዊት ቁጥር ካላቸው ጋር ይጣመሩ የሚለውን ለመቀበል ሲቸግረው አይቻለሁ። በሌላ በኩል ደግሞ ወደ አማራው ክልል ዘልቆ ለመግባት አርበኞች አስፈላጊ ናቸው ብሎ ያምን ነበር፤ ለዚህም ሲል መጣመሩን ይፈልገዋል።
እንደሰማሁት ከአርበኞች ግንቦት7ና ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በነበረው ድርድር፣ መጀመሪያ ላይ ባይደግፈውም፣ በራሱ አመራሮች በድምጽ ብልጫ ከተሸነፈ በሁዋላ ውሳኔውን ተቀብሎ ነበር ። ሞላ ” ጥምረቱን የደገፉት ጓደኞቼ በሂደት ያባርሩኝ ይሆናል” የሚል ስጋት ሳይገባው አልቀረም። እነ ፕ/ር ብርሃኑ ወደ ኤርትራ ወርደው ተቃዋሚዎችን ያስተባብራሉ ብሎ የጠበቀም አይመስለኝም። ምንም ይሁን ምን ሞላ የከዳው ከስልጣን ጋር በተያያዘ መሆኑን አምናለሁ። እኔ ኤርትራ በነበርኩበት ወቅት ከደሚህት ጋር የሚደረግ ድርድር ስላልነበር፣ ስለ ስልጣን ፍላጎቱ ልናገር አልችልም ። እንደሰማሁት በደሚት ውስጥ በርካታ አመራሮች አሁንም አሉ። የወጣው ሰራዊት ጥሎት ከወጣው ሰራዊት ጋር ሲነጻጸር ኢምንት መሆኑን አንዳንድ ሰዎች ነግረውኛል። ይህ ሰራዊት የአገር አድን ሰራዊቱ አካል ሆኖ የሚቀጥል ይመስለኛል።
በነገራችን ላይ የደሚህት ሰራዊት ኢትዮጵያዊ ቅርጽ አለው፤ ሁሉንም ብሄረሰቦች አቅፎ የያዘ ነው። እንዲያውም ትዝ አለኝ፣ ደሚህት የተለያዩ ብሄረሰቦችን በአባልነት ይዞ እያለ እንዴት የትግራይ ነጻ አውጭ ተብሎ መጠራቱ ትክክል አይመስለኝም፣ ስማችሁ እየጎዳችሁ ነው ብየዋለሁ። ለማንኛውም፣ ፖለቲካ እንዲህ ነው እስከመጨረሻው የጸና ብቻ እርሱ ያሸንፋል። መልካም አዲስ አመት።”
መሳይ መኮንን (የኢሳት ጋዜጠኛ) ኤርትራ በነበረበት ወቅት ከአቶ ሞላ አስግዶም ጋር የኢትዮጵያን ወቅታዊ ፖለቲካ በተመለከተ የተወያየውን ከግምት በማስገባት አቶ ሞላን እንዲህ በማለት ይገልጻቸዋል፣
“ሞላ ሌላ ደሚህት ሌላ
እንኳን አደረሳችሁ:: የሞላ አስገዶም ወደ ህወሀት ካምፕ መግባት አዲሱን አመት በተለያዩ ስሜቶች እንድንቀበል አድርጎናል:: ይህን ያህል አጀንዳ ይሆናል ብዬ አልገመትኩም:: ስለሞላ እስከማውቀው ድረስ ጥሩ ኢትዮጵያዊ: እንደ ህወሀቶች ዘረኝነት የማይነካካው: በመግባባት ለመስራት ከልቡ የሚሻ ነበር:; መቼም ሰው እንደ እህል አይቀመስም:: መለኮታዊ ሃይል ኖሮ ልብ የቀበረውን ማወቅ አይቻል:: በሞላ ደም ውስጥ የሚንተከተከውና ዛሬ ላይ አደባባይ የወጣው ማንነት የሰው ልጅን ፈጽሞ አንብቦ እንደማይጨረስ አንዱ ማሳያ ሊሆን ይችላል:: ግን አንድ የማልደብቀው ሀቅ አለ:: ይህን የምናገረው ሞላ አሁን ወደ ህወሀት ጠቅልሎ በመግባቱ የተነሳ አይደለም:: ዕውነት ስለሆነ ነው:: ያኔ ያን ዕውነት ማፈንዳቱ ለትግሉ ጉዳት እንጂ ጥቅም አይኖረውም::
አዎን! ሞላ ባህላዊ መሪ ነው:: ለ5 ደቂቃዎች ከእሱ ጋር ፖለቲካ ለመጫወት አይቻልም:: ስለ ኢትዮጵያ ውስብስብ ፖለቲካ ያለው ግንዛቤ ያስደነግጣል:: ማለት ጥልቀት የለውም:: ቀናነቱና ገራገርነቱ ፖለቲካዊ ድክመቱን ባይሸፍኑለትም አብሮ ላለመስራት የሚጎረብጥ ሰው አልነበረም:: እርጋታውና ጨዋነቱም ሌላው ድክመቱን የሚጋርዱ ባህርያቱ ናቸው::
አሁን ሞላ የለም:: ደሚህት ግን ከነሙሉ ሰራዊቱ ትግሉን ተቀላቅሏል:: በደሚህት ውስጥ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የሰራዊቱ አባል ከተለያዩ የኢትዮጵያ አከባቢዎች የመጡ ናቸው:: የትግራይ የሚለው ስያሜ ቀድሞ ስለያዘ እንጂ ሰራዊቱ ሙሉውን ኢትዮጵያ የሚወክል ነው:: እኛም በኤርትራ ቆይታችን ይህን ታዝበናል:: የሰራዊቱ ስሜት ከሞላ አመራር ጋር የሚመጣጠን አይደለም:: አንድ ቀን ሰራዊቱ ፈተና እንደሚሆንበት ሞላ የተገነዘበው ይመስለኛል:: በደሚሀት ካምፖች በነበረኝ ተከታታይ ጉብኝቶች የተረዳሁት የሞላ አመራርና የደሚሀት ሰራዊት ፍላጎት ለየቅል መሆናቸውን ነው:: ይህን ጉዳይም አንድ ምሽት ላይ ባሬንቱ ከተማ ቢራ እየተጎነጨን አንስቼበታለሁ::
” ሰራዊቱ ኢትዮጵያዊ: ስያሜው ግን የትግራይ:: ምን ማለት ነው?”
ሞላ በወቅቱ ጥሩ መልስ ሰጠኝ:: አሁን ላይ ስገምት የማያምንበትን ነው የነገረኝ
” ቀላል ነው:: ስያሜው አያስጨንቅም:: “ት” ን በ”ኢ” የመቀየር ያህል ቀላል ነው:: ዋናው ተግባብቶ መስራት ነው” አለኝ::
ሞላ መግባባት አቅቶት ወይም በሌላ ምክንያት ወደ ህወሀት ሄዷል:: ኢትዮጵያዊ መልክ የተላበሰው ደሚህት ግን ከትግሉ ጋር ነው:: ግለሰብ በራሱ ውሳኔ መንገዱን መርጧል:: ጨርቅ ያድርግለት:: የኢትዮጵያ ትግል ከባህላዊው አመራር ካልተላቀቀ ለውጥ አይኖርም:: የሚንጠባጠበውን እያራገፉ ከመጓዝ ውጭ አማራጭ የለም:: በግለሰቦች ላይ የተንጠለጠለ ትግል ወደ መቃብሩ ወርዷል:: ሞላ ለጊዜው ጭረት ሊፈጥር ይችላል:: ከዚያ ያለፈ ጉዳት የለውም:: ደሚሀት መግለጪያ ያወጣል ተብሎ ይጠበቃል:: አዲሱ ዓመት ዘመናዊውና በዕውቀት ላይ የተመሰረተው የምር የሆነው ትግል የሚጀምርበት ይሆን ዘንድ ሁሉም የሚችለውን ያድርግ:: መልካም በዓል!!!”
ታዋቂው ጋዜጠኛና የመብት ተሟጋች አበበ ገላው በበኩሉ የሚከተለውን አስተያየት ሰጥቷል፣
“አቶ ሞላ አስገዶም ጥቂት ተከታዮቹን ይዞ ተመልሶ ወደ ህወሃቶች ካምፕ መቀላቀሉን ወይንም ለመቀላቀል መንገድ ላይ መሆኑን ተከትሎ ህወሃቶች ደስታቸውን ሲገልጹ ጥቂቶች ደግሞ የተለመደውን የግነት ከበሮ በመታት ላይ ናቸው። ይሁንና ወሳኝ ቀን ሲደርስ ቁርጠኝነት የሌላቸው የውስጥ አርበኞች በየግዜው መንጠባጠባቸው አይቀሬ ጉዳይ ነው። የተጀምረው ትግል በግለሰቦች ጫንቃ ላይ የተመሰረተ ባለመሆኑ የእነሞላ ወደ መጡበት መመለስ ከጉዳቱ ጥቅሙ ያመዝናል።
ትግሉ ሲፋፋም እነሞላ የህወሃቶች የውስጥ አርበኛ በመሆን የበለጠ ብዙ ጉዳት ያደርሱ ነበር። እንደውም አሁን የመስመር አሰላለፉን ለማስተካከል ጥሩ አጋጣሚ ተፈጥሯል።
ትግል የመውደቅና የመነሳት የውጣ ውረድ ጉዞ ስለሆነ ገና ወደ ፊት መልካምም ይሁን አስከፊ ዜና በየግዜው መስማታችን አይቀሬ ነው። በዚህ አጋጣሚ እንዲህ አይነቱ ክስተት ከግለሰቦች ጋር እንጂ ከየትኛውም ህዝብ ጋር የሚገኛኝ ባለመሆኑ ጉዳዩን ባለስፈላጊ መንገድ ከማራገብ መቆጠብ ብልህነት ነው። ለማንኛውም ትግሉ ይቀጥላል። መልካም አዲስ አመት።”
በርካታ አስተያየት ሰጪዎች ዜናው ለለውጥ ናፋቂ ኢትዮጵያውያን አስደሳች ባይሆንም የኢሳት ጋዜጠኞች ከወገንተኛነት በጸዳ መልኩ የሞያ ግዴታቸውን (ፕሮፌሽናሊዝም) በሚገባ ተወጥተዋል ብለው ሲያደንቁ አንዳንዶች ደግሞ ኢሳት ዜናውን ያቀረበበትን መንገድ ተችተዋል።
ሳሙኤል ዳዲ የተባሉ አስተያየት ሰጪ እንዲህ ብለዋል፣
“እኔ ግን አንድ ነገር ልበል ኢሳት ኢቢሲ ቢሆን ኖሮ ከዱ ስይሆን ተባረሩን እንሰማ ነበር።”
ታሪኩ አባዳማ በጉዳዩ ግራ ተጋብቻለው ላሉ አስተያየት ሰጪ ሲመልሱ ደግሞ፣
“ግራ አጋብቶኛል? I understand your frustration Achame. The way these news were presented to us lacks professionalism in every way. But do not be confused about the content of the news in this piece. Political struggle is full of tricks, betrayals, sabotages, infiltration, spying, murders, and violations of all types of human dignity… its ugly. I was not confused, but I was amazed by the speed of this switch of political position and also by the way it was presented on ESAT. Do they have any news caster who can tell us NEWS – JUST NEWS – Not f*** breaking news.”
የትግራይ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ዴምህት) የድርጅቱ መሪ መክዳታቸውን በተመለከተ እስካሁን ያለው ነገር የለም።

No comments:

Post a Comment