Translate

Saturday, March 7, 2015

ምርጫ እና ምርጫ በ2007!

ዕጣ! ጣጣ! . . . የምር ይውጣ

election 2015
ምርጫ 2007ን ከሌሎች ምርጫዎች ሁሉ ልዩ የሚደርገው ምርጫ ቦርድ ከምርጫው በፊት ፓርቲዎችን (ተፎካካሪ) በማፍረስ ጀምሮ የሰማያዊ ፓርቲ እጩ ተወዳዳሪዎችን (ከ200 በላይ) አልመዘግብም ማለቱ እና በአዲስ አበባ ምርጫ ክልል ደግሞ ወደ ምርጫው ለመግባት ተወዳዳሪው በዕጣ መለየት አለበት ማለቱ ነው፡፡ ዕጣው ደግሞ ለሁሉም ፓርቲዎች ሳይሆን ሰማያዊን ጨምሮ ጥቂቶች ላይ የተደረገ ነው፡፡ ይኸውም በማፍረስ እና በመከልከል ተጀምሮ ”ምርጫ በሎተሪ” መሆኑ ነው፡፡

በዓለም ላይ በታሪክ ዴሞክራሲ በዕጣ ይረጋገጣል ሲባል ኢትዮጵያ ብቸኛ እና የመጀመርያ አገር ስትሆን በኢትዮጵያም ለመጀመርያ ጊዜ ሰማያዊ ፓርቲ በመወዳደሩ እና እንደሚያሸንፍ ስለታመነ እንጅ በ2002 በአንድ የምርጫ ክልል ከ18 በላይ ፓርቲዎች መወዳደራቸው አይካድም፡፡ እርግጥ ነው ህግ ከተባለ አዋ/ቁ 532/99 አንቀጽ 49 እንደ ተደነገገው ፡-
(1) “በአንድ የምርጫ ክልል ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለመመረጥ የሚወዳደሩ እጩዎች ከ12 መብለጥ የለባቸውም፡፡”
(2) “የእጩ ብዛት ከ12 ከበለጠ የፖለቲካ ድርጅቶች በቅድሚያ በእጩነት እንዲመዘገቡ ይደረጋል::”
(3) “በፖለቲካ ድርጅቶች የቀረቡት እጪዎች ከ12 በላይ ከሆኑ ባለፈው ምርጫ ከፍተኛ ድምጽ ላገኙ ከ6 ለማይበልጡ ድርጅቶች ቅድሚያ ይሰጣል፡፡ ቀሪዎች የፖለቲካ ድርጅቶች በእጣ ይለያሉ፡”
እንግዲህ ጉዱ ያለው እዚህ ላይ ነው፡፡ ሲጀመር ይህን ህግ ኢህ-አዴግ በምርጫ አምባገነናዊነት ስልቱ የህዝብ ተወካዮችን ም/ቤት በትልቁ የኢህአዴግ ም/ቤት ከመሰለ በኋላ ከአብዮታዊ ዲሞክራሲ የተቀዳውን የአፈና እና የስልጣን ማራዘሚያ ህግ ያወጣል፡፡ በህግ ቋንቋ የህዝቦች ህግ (justice law) እና የአምባ ገነኖች የአፈና ህግ (unjust law) የሚባሉ ህጎች አሉ፡፡ ኢህአዴግ የሚጠቀምበት በህግ መያዝ (rule by law) ስርዓት ሲሆን የህዝቦች ህግ ግን ሁሉን አቀፍ እኩል ፍትሀዊ… (Rule of law) የህግ የበላይነት ስርዓት ነው፡፡
ስለዚህ የአዋጅ አንቀጽ 49 የፓርቲዎች ለምርጫ እንዳይወዳደሩ እና ህዝቡን መሪውን በድምጽ እንዳይመርጥ መገደብ እና የዕጣ ስርዓት ከዴሞክራሲያዊ መርህ እና ከመድበለ ፓርቲ ስርዓት ያፈነገጠ ገደብ (rule by law) ማለትም ምርጫን በዜጎች ፍላጎት ሳይሆን በጭቆና ህግ መገደብ እና ሳንሱር ማድረጊያ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም፡፡
ፓርቲዎች ለምን በምርጫ ቦርድ ፈቃድ ይሰጣቸዋል?
በመጀመርያ ደረጃ ፓርቲዎች ተደራጅተው በምርጫ ቦርድ ተመዝግበው የሚታገሉት ስልጣን በህዝብ ድምጽ ለመያዝ እና በምርጫ ተወዳድረው ለማሸነፍ ነው፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ ከዚህ በፊት የተወዳደሩ ቅድሚያ …ምናምን የሚለው ገዳቢ እና እኩልነትን የተጻረረ የአፈና እና የምርጫ ሳንሱር ህግ ነው፡፡ አዲስ ፓርቲዎች በዕጣ እየተለዩ የሚቀሩ ከሆነ መደራጀታቸው ለምን ያስፈልጋል? ስለዚህ ይህ ህግ ከወጣ በኋላ የተመዘገቡ ፓርቲዎች በሳንሱር ውድቅ ይደረጋሉ፡፡ ይገደባሉ፡፡ ሜዳውም እኩል አይደለም፡፡ ህጉም የምርጫ አምባ ገነናዊ ስርአት ለመመስረት የሚያስችል አፋኝ ህግ ነው፡፡
ተወዳደዳሪ ፓርቲዎችን በምርጫ እንዳይወዳሩ እና መራጮችም የፈለጉትን መሪ በድምጽ እንዳይመርጡ መገደብ ህጋዊ ስላለመሆኑ ፓርቲዎች ለምርጫ ውድድር ሥልጣን ለመያዝ ከተመዘገቡ በኋላ በአገሪቱ እንደ አሽን የፈላ ፓርቲ አላት እየተባለ 6 ፓርቲ 12 ምና ምን መገደብ ለምን አመጣው? ተመዝገቡ ግን በምርጫ አትወዳደሩም ማለት ነው፡፡ ይህም ከአለም አቀፍ የምርጫ ህግና ከህገ-መንግስቱ ጋር የተቃረነ ነው፡፡
ህጉ የአሰራር ደንብና መመሪያ የሌለው ስለመሆኑ
የህጉ ኢ ህጋዊነት እንደተጠበቀ ሆኖ ሥራ ላይ ይዋል ቢባል እንኳ የዕጣ አመጣጥ ሥርአቱ ምን መምሰል እንዳለበት ደንብ የለውም፡፡ የፊልም ወይም ድራማ ተዋናይ እንኳ ለመሸለም ተወዳዳሪዎችን (አሸናፊውን) ለመለየት የድራማው ተከታታዮች አሸናፊዎችን እንዲለዩ የተለያዩ ዘዴዎችን ማለትም በስልክ መልክት፣ በፖስታ፣ በሳጥን ድምጽ በደጋፊዎች እንደሚሰጥ ከመታወቁም በላይ 8100A የተባለው ስልትም በራሱ አንድ ማሳያ ይሆናል፡፡vote 2015
ለመሆኑ የምርጫ ክልሉ ህዝብ በተለይም ለመምረጥ ካርድ ያወጣው ህዝብ ማን ለምርጫ ውድድር በእጩነት መቅረብ እንዳለበት የመራጩን የህዝብ መብት እንጅ የምርጫ ቦርድ መብት መሆኑ ፈር የለቀቀ አፈና ነው፡፡ ምክንያቱም የሚፈለገውን መሪ የመለየት እና የመምረጥ ስልጣን የመራጩ ህዝብ እንጅ የምርጫ ቦርድ ስልጣን ሊሆን አይችልም፡፡ ማለትም ምርጫ ቦርድ አስፈጻሚ እንጅ መራጭ ሊሆን አይችልምና፡፡ አሁን ግን የተደገረው በመጀመርያ እጩዎችን መርጦ የለየው ምርጫ ቦርድ እንጅ ሉአላዊ ስልጣን ያለው ህዝቡ አይደለም፡፡ የምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልሉን መራጮች መሪያቸውን በቀጥታ የመምረጥ እና መመረጥ መብት ለማክበር ቢሳነው እንኳ የምርጫ ክልሉ መራጭ ዜጎች በዕጣው ላይ የሚሳተፉበትን ስልት አለመዘርጋቱ እና አለማሳተፉ መሪዎችን ለመምረጥ ካርድ ባወጣው ህዝብ ላይ ድራማ እንደመስራት ይቆጠራል፡፡ ይህም ምርጫ ቦርድ በህዝብ ሉአላዊነት እና የስልጣን ባለቤትነት ላይ ከባድ ጫና መፍጠሩ የሚያሳይ ምርጫም በሎተሪና በቅድመ ሳንሱር መኖኑን ያረጋግጣል፡፡
የኢህአዴግ ልዩ የአፈና ስልትና ዕጣው
ኢህአዴግ እንደለመደው ምርጫውን አፍኖ ሥልጣኑን ለማራዘም የአፈና ስትራቴጅ የቀየሰ ሲሆን አዲስ ራዕይ በተባለው ልሳኑ በሆነው ቅጽ 4 ቁ 7 ከጥር -የካቲት 2007 ዓ.ም እትሙ በገጽ 57 እና ተከታዮቹ እንዳስነበበው ምርጫን በህዝብ ፍላጎት ሳይሆን በአገዛዙ የአፈና ስልት አቀናብሮ ተወዳዳሪ ፓርቲዎችን እና መራጩን ህዝብ ለማፈን የተለየ ስልት ነድፏል፡፡ ይኸውም የስነ-ምግባር ደንቡን ከፈረሙት ታማኝ ተቀዋሚዎች፣ የፍትህ አካላት፣ ምርጫ ቦርድ እና የጸጥታ አካላት ጋር በመተባበር በተዋቀረው የምርጫ ሰራዊቱ ህዝቡን አፍኖ ለመግዛት በምርጫው ተመርጫለሁ ለማለት እና የይስሙላ ምርጫ በማካሄድ የምርጫ አምባገነን ስርአት ለመመስረት ብቃት ባለው ስልት ብሎ ካስቀመጠው የአሸንፊያለሁ ልማዱ ውስጥ አንዱ ምርጫ በሎተሪ የመሆኑ ነገር ነው፡፡ ይኸውም በጥብቅ የአፈና መመሪያ እየተከናወነ ለመሆኑ የዘንድሮውን ምርጫ ለየት የሚያደርገው የተፎካካሪ ፓርቲ እጩዎችን እንዳይመዘገቡ መክልከል፣ ከተመዘገቡ በኋላ መሰረዝ፣ ማዋከብ እና ምርጦችን ያለ እጣ ተፎካካሪዎችን ደግሞ በእጣ ሳንሱር ማድረግ እና አልፎም ፓርቲዎችን በማፍረስ፣ ፕሮፖጋንጋ በማሰራጨት የፓርቲ እጩዎችን አልመዘግብም በማለት እና በመከልከል ከመጠመዱም በላይ በምርጫ ቦርዱ ድህረ ገጽ ላይ ለሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት ላይ የከፈተው ዘመቻ የስልቱ ፈጻሚ መሆኑን በልሳኑ አረጋግጧል፡፡ ስለሆነም ቦርዱ ገለልተኛ ይሆናል ብሎ መጠበቅ ሞኝነት ከመሆኑም በላይ ድንጋይ ላይ ውሀ እንደማፍሰስ ነው፡፡
ህጉ ከህገ መንግስቱ ጋር ተቃራኒ ስለመሆኑ
የኢፌድሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 9 ስለህገ-መንግስቱ የበላይነት በደነገገበት ክፍል ህገ-መንግስቱ የሁሉም ህጎች የበላይ ስለመሆናቸው ማንኛውም ህግ ልማዳዊ አሰራር… ከዚህ ህገ-መንግስት ጋር ከተቃረነ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን እና በአንቀጽ 13 ደግሞ አለም አቀፍ ድንጋጌዎች የህገ መንግስቱ አካል እንደሆኑ ይደነግጋል፡፡ እንግዲህ ኢትዮጵያ ተቀብላ ያጸደቀቻቸውን (UDHR) አለም አቀፍ የሰባዊ መብት ድንጋጌዎችን ጨምሮ በህገ መንግስቱ የተደነገገውን የመምረጥና የመመረጥ መብት፣የመደራጀት መብት፣የህዝብ ሉአላዊነት መብት የጣሰ እና ህገ-መንግስታዊ ስለመሆኑ አንድ ባንድ ማየት እንችላለን ፡፡ይኸውም፡-
(1) የኢፌዲሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 8 የህዝብ ሉአላዊነት
8 (1) የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦች ህዝቦች የኢትዮጵያ ሉአላዊ ስልጣን ባለቤቶች ናቸው፡፡
(2) ይህ ህገ መንግስት የሉአላዊነት መገለጫ ነው፡፡
(3) ሉአላዊነታቸው የሚገለጸው በዚህ ህገ መንግስት መሠረት በሚመርጧቸው ተወካዮቻውና በቀጥታ በሚያደርጉት ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ አማካኝነት ነው ይላል፡፡
እንግዲህ እዚህ ላይ በግልጽ የምንረዳው የስልጣን ባለቤት የህዝቡ ሉአላዊ መብት መሆኑን እና ይህም የሚረጋገጠው በቀጥታ በመረጧቸው ተወካዮቻቸው እና በተሳትፎ መሆኑን እንጅ ፓርቲዎች አትወዳሩም ብሎ መገደብም ሆነ በእጣው ምርጫ ይገባል ይወድቃል ማለት ይህን ሕገ-መንግስታዊ ድንጋጌ በጠራራ ፀሀይ የተላለፈ ኢህገ-መንግስታዊ ህግ እና አሰራር ነው፡፡ ውድቅ መደረግ እንዳለበትም የምርጫ ቦርድም ሆኑ የዜጎችና የመንግስት አካት ህገ-መንግስታዊ ግዴታም ነው፡፡ ስለዚህ ምርጫ ቦርድ ህገ መንግስቱን በመጣስ የህዝቡን ስልጣን በኢ-ህገመንግስታዊ ህግ አፍኗል፡፡
የኢፌድሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 25
የእኩልት መብት
“ሁሉም ሰዎች በህግ ፊት እኩል ናቸው፡፡ በመካከላቸውም ማናኛውም አይነት ልዩነት ቢደረግ በህግ እኩል ጥበቃ ይሰጣቸዋል በዚህ ረገድ በብሔር ብሔረሰብ ፣በቀለም፣ በፆታ፣ በቋንቋ፣ በሀይማት፣ በፖለቲካ፣ በማህበራዊ አመጣጥ በሀብት —-ወይም በሌላ አቋም ምክንያት ልዩነት ሳይደረግ ሰዎች ሁሉ እኩል እና ተጨባጭ የህግ ዋስትና መብት አላቸው ፡፡”
እንግዲህ እዚህ ላይ ‹‹ሰው›› ማለት በሰዎች ህግ የተፈጥሮ ሰው እና ድርጅቶችን ሲሆን ያለምንም ገደብ በእኩልነት ሊወዳደሩ ሲገባ ከዚህ በፊት ተወዳድሮ ድምጽ ያገኘ፣ ዕጣ የወጣለት፣ ከ6 ያልበለጠ፣ 12፣ምናምን የሚለው የሚገድብ እና እኩል የመወዳደር መብትን የጣሰ ነው፡፡
አንቀጽ 31፣33
የመደራጀት እና የዜግነት መብት ህገ-መንግስትዊ ሲሆን የተደራሽ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ደግሞ በኢፌድሪ ህገ-መንግስት አንቀጽ 38 መሠረት የመምረጥና የመመረጥ መብት አለው፡፡ በግልጽ የህገ መንግስቱን ድንጋጌ ማየት ይቻላል፡፡
አንቀጽ 38
የመምረጥ እና የመመረጥ መብት
ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ (አንቀጽ 33 ልብ ይሏል)
(1)ማናኛውም ኢትዮጵያ ዜጋ በቀለም፣በዘር፣በብሕር፣በብሔረሰብ በጾታ ፣በቋንቋ ፣በሀይማኖት፣ በፖለቲካ ወይም በሌላ አመለካክት ወይም በሌላ አቋም ላይ የተመሰረተ ልዩነት ሳይደረግበት የሚከለሉት መብቶት አሉት፡፡
ሀ. በቀጥታ እና በነጻነት በመረጣቸው ተወካዮች አማካኝነት በህዝብ ጉዳይ አስተዳድር የመሳተፍ፣
ለ. ዕድሜ 18 አመት ሲሞላ በህግ መሰረት የመምረጠጥ፣
ሐ. በማናቸውን የመንግስት ደረጃ በየዜው በሚካሂድ ምርጫ የመምረጥና የመመረጥ ምርጫው ሁሉ አቀፍ፣ በሁሉም እኩልነት ላይ የተመሰረተ በሚስጥር ድምጽ አሰጣጥ መራጩ ፈቃዱን በነጻነት የሚገልጽበት ዋስትና የሚሰጥ መሆን አለበት፡፡
(2) በፖለቲካ ድርጅቶች፣ በሠራተኞች፣ በንግድ፣ በአሰሪዎችና በሙያ ማህበራ ለተሳትፎ ድርጅቱ የሚጠይቀውን ጠቅላላና ልዩ የአባልነት መስፈርት የሚያሟላማናኛውም ሰው በፍላጎ አባል የመሆን መብቱ የተከበረ መሆን አለበት፡፡
(3) በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ 2 በተመለከተ ድርጅቶች ውስጥ ለኃላፊነት ቦታዎች የሚካሄዱ ምርጫዎች ነጻና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ይፈጸማል፡፡
(4) የዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ 2 እና 3 ድንጋጌዎች የህዝብን ጥቅም ሰፋ ባለሁኔታ የሚለኩ እስከሆነ ድረስ በህዝባዊ ድርጅትቶች ላይ ተፈጻሚ ይሆናሉ፡፡
በመሆኑም የሎተሪ ምርጫ ስርዓቱም ሆነ ህጉ ህገ መንግስቱን ያላከበረ የህዝቡን ሉአላዊ የስልጣን ባለቤትነት፣ መብት የመደራጀት፣ የእኩልነት መብት፣ የዜጎች መብት በቀጥታ የደረመሰ ስለሆነ ውሳኔውን የማረም የምርጫ ቦርዱ ህገመንግስታዊ ግዴታ ሲሆን ህጉም ተቀባይነት የሌለው ስለሆነ ሊተገበር የማይገባው ነው፡፡
በሳሙኤል አወቀ (የግል አስተያየት) ከነገረ ኢትዮጵያ ፌስቡክ ገጽ የተገኘ

No comments:

Post a Comment