Translate

Saturday, December 20, 2014

ግርማ ሠይፉ፣ ሠራዊት ፍቅሬና ቴዎድሮስ አድሐኖም ያልመረጥናቸው የህዝብ ልዑካን (ሁኔ አበሲኒያ)

Girma Seifu the only opposition representative in Ethiopian parliament ሁኔ አበሲኒያ
ከሠሞኑ ወደግብፅ የሚያቀና ህወሀታዊ የልዑካን ቡድን ሲቋቋም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ሊጠብቀው በማይችለው መልኩ የልኡካን ቡድኑ ውስጥ የአንድ ሠው ስም ተሠማ “ግርማ ሠይፉ” የሚል በርካቶች ተገረሙ ወይ አንቺ ሐገር ሲሉም አዘኑ፡፡ ከዚህ ቀደም ብቸኛ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል በፓርላማ ተብለው በተቀመጡባቸው ያለፉት 4 ዓመታት ለሐገራችን ፖለቲካ ያንን ያህል ለውጥ ባያመጡም፤ የህሊና እስረኞቹ ይፈቱ ዘንድ አሁንም ያንን ያህል ጠንከር ያለ ስረ ባይሠሩም አቶ ግርማ ሠይፉን ሌሎች አካላት ሲተቿቸው ግርማ ሠይፉን ደግፈው ከሚቆሙ አካላት መካከል አንዱ እኔ ነበርኩኝ ብዬ አስባለው፤ አስባለው ያልኩት ስለግርማ ሠይፉ ከኔ በላይም የሚያስብ ሌላ ህወሀት የተሠኘ የሠዎች ስብስብ መኖሩን ስላልተረዳሁና በቅርቡ እየታዩ ያሉትን የግርማን መንሸራተቶች ባለመመልከቴ ነበር፡፡

በሐገራችን ፖለቲካ ማየት ከማንፈልጋቸው ነገሮች የከዳተኝነት ፖለቲካ አንዱ እና ዋነኛው ነው፤ ይህ ህዝብ ለፍቶ ከሚያገኘው የወር ገቢው ላይ ግብር ተወስዶበት ፓርላማ ለሚገኙ የህዝብ ተወካዮች በአበል እና በደመወዝ መልክ ይሠጣል ህዝቡ ይህንን የሚያደርገው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በተሠኘው የሚገኙ አባላት መብቴን የሚያስከብር ህግ ያወጡልኛል፤ ስለእኔ መብት ስለቆሙ የታሠሩ የህሊና እስረኞችን የበላይ አካል እንደመሆኑ ያስፈታልኛል ብሎ አለመሆኑ እሙን ነው ምክንያቱም በህወሀት ፓርላማ ውሳኔ ችግሬ ይፈታልኛል ብሎ የሚያስብ ኢትዮጵያዊ ካለ እርሱ የህወሀት አባል መሆን አለበት ሆኖም ተባራሪ ሆነው ፓርላማ ውስጥ የሚታዩ አንዳንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የህዝብ ችግር ያሏቸውን ጉዳዮች ነቅሰው አውጥተው ለፓርላማው ሲያቀርቡ እንመለከት ነበር እነዚህ ሠዎችም ሲከዱ ተመልክተናል እውን ግርማ ሠይፉ ካዳ? ግርማ ሠይፉ ካዳ ወይስ አሁንም ለህዝቡ እንደቆመ ነው የሚሉትን ጉዳዮች ከማንሳታችን በፊት ከግርማ ሠይፉ ጋር የልዑካን ቡድኑ አባላት ውስጥ የሚገኙ አባላት እነማን ናቸው የሚሉትን መመልከት ተገቢ ይመስለኛል፡፡
የህዝብ ልዑካን ቡድን ሲቋቋም መታሠብ ካለበት መካከል አንደኛው እና ዋናው ነገር የልዑካን ቡድኑ አባላት በህዝብ የታመኑ፣ በመልካም ስነምግባራቸው አርዓያ የሆኑ እና ለሌሎች ምሳሌ የሚሆኑ መሆን ይኖርባቸዋል ወደግብፅ ባቀናው የልዑካን ቡድን ውስጥ የተካተቱት ግን በየትኛውም መለኪያ የህወሀት ጉዳይ አስፈፃሚ ከመሆን ውጪ የህዝብ አመኔታ ያላቸው ግለሠቦች አይደሉም፡፡ ከልዑካን ቡድኑ ውስጥ መካከል አንዱ ሠራዊት ፍቅሬ የተሠኘው ግለሠብ ነው፡፡ ይህ ግለሠብ ልክ እንደሌሎቹ የህወሀት አባላት እና አመራሮች ከወታደር ቤት ወጥቶ ሚሊየነር የሆነ ግለሠብ ነው፡፡ ሠራዊት ፍቅሬ የህዝብ ተወካይ መሆን የማይችልባቸውን ምክንያች ለማንሳት ያህል ከዛሬ ሁለት አመት በፊት በአንድ ተማሪ ላይ በማን አለብኝነት የፈፀመውን የአስገድዶ መድፈር ሙከራ ማየቱ ተገቢ ነው፡፡ ሠራዊት ፍቅሬ አስገድዶ ሊደፍረኝ ሲል አመለጥኩኝ ያለችውን ግለሠብ አዲስ አድማስ የተሠኘው ሐገር ቤት የሚታተም ጋዜጣ አነጋግሯት እንደነበረና ከጥቂት ቀናት በኋላ በሠራዊት ፍቅሬ የመድፈር ሙከራ የተደረገባት ተማሪ ሁኔታ ተደባብሶ ቀረ ወጣቷ አሁን የት እንዳለች እንኳን አይታወቅም አዲስ አድማስም ከህወሀት ሠዎች ሊደርስበት የሚችለውን ዛቻ በማሠብ ተወው ይህንን ድርጊት የፈፀመው ሰራዊት ፍቅሬ ነው አንዱ የዚህ ልዑክ አባል፡፡ ሌላኛው የልዑካኑ ቡድን አባል ቴዎድሮስ አድሐኖም ወይም እንደሱ አጠራር ቴድሮስ አድሐኖም ነው፡፡ ይህ ግለሠብ አምና በዚህ ሠዓት ሣውዲ አረቢያ ይገኙ ለነበሩ ሠዎች ሞት እና እንግልት ተጠያቂ ሊሆን የሚችል ሠው ነው፡፡ ቴዎድሮስ አድሐኖም የውጪ ጉዳይ ሚኒስተሩነቱን እና የህወሀት አባልነቱን ተጠቅሞ ለሳውዲአረቢያ የንጉሳውያን ቤተሠቦች በላከው ደብዳቤ ኢትዮጵያውያኑ ከሳውዲ ኢሠብዓዊ ድርጊት ተፈፅሞባቸው እንዲወጡ ማድረጉ ይታወሳል ይህ ግለሠብ ስለእውነት እና ስለህዝብ የቆመ ቢሆን ኖሮ የሳውዲ ንጉሶችን አሳምኖ የኢትዮጵያውያን መውጫ ቀን በማስረዘም ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንን ከእልቂት እና ከግፍ ያድን ነበር ሆኖም ዛሬ ይህ ግለሠብ የሠራቸው ወንጀሎች ተደብቀውለት ዛሬ የህዝብ ልዑካን ተብሎ ተሠይሞ ይገኛል፡፡ ግርማ ሠይፉም ከእነዚህ ሠዎች መካከል ይገኛል የህዝብ ልዑካን ቡድን ተብሎ፡፡ ከሠራዊት ፍቅሬ እና ከቴዎድሮስ አድሐኖም ጋር አብሮ መስራትን የመሠለ ምን ከዳተኝነት ይኖር ይሆን?
ግርማ ሠይፉ የልዑካን ቡድኑ ውስጥ መካተቱን ሳይነግረን ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ “ይህ የአሁኑ ሠንደቅ ዓላማ ለእኔ ከበፊቶቹ ይሻለኛል፤ ሁሉም የታሠሩት ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች ንፁህ ናቸው ብዬ አላምንም” ምናምን የሚሉ በህዝብ ላይ የተቀለዱ መጥፎ ንግግሮችን በኢንተርቪው እና በብሎጉ ላይ አሰምቶናል በተጨማሪም አምና አንድነት ጠርቶት በነበረው ሠላማዊ ሰልፍ ላይ ሠልፈኛው ሲግናል አካባቢ ሲደርስ ሲግናል ለአንድ ጎሳ አባላት ብቻ የተሠሩትን ህንፃዎች ተመልክቶ ዝም ብሎ ማለፍ ያልቻለው ሠልፈኛ ሌባ ሙሰኛ እያለ ሲጮህ ዝም በሉ እያለ ሠልፈኛውን ከሀብታሙ አያሌው ለመነጠል ሲሞክር እንኳን በግርማ ላይ ተስፋ አልቆረጥኩም ነበር አሁን ግን ከኢትዮጵያ የምንም ጊዜ ጠላቶች ጋር አበረ፡፡ የልዑካን ቡድኑ ውስጥ ያሉት ሠዎች እኮ በበደኖ እና በአርባጉ የአማራውን ጎሳ የጨፈጨፉ፤ በአምቦ ንፁሐን የኦሮሞ ተማሪዎችን የገደሉ፤ ፤ በጋምቤላ ንፁሀንን ያስፈጁ፤ ፕ/ር አስራትን እና አሠፋ ማሩን የመሳሰሉ ድንቅ የሐገራንን ምሁራን ያስገደሉ፤ እስክንድርን፤ ርዕዮትን፤ በቀለ ገርባን፤ ኤርባና ሌሊሳን፤ የሺዋስ አሠፋን፤ አብርሐ ደስታን፤ ዳንኤል ሺበሺን፤ አበበ ቀስቶን፤ ናትናኤልን፤ ሐብታሙን፤ እና ሌሎችንም ያሠሩ፤ ከጥቂት ቀናት በፊት እንኳን የሠማያዊ ፓርቲን እና የትብብሩ አባላትን ቶርች ያደረጉ፤ በትላንትናው እለት ባህርዳር ላይ ህዝብን ያስፈጁ ሠዎች ጥርቅም ውስጥ ግርማ ዘው ብሎ የገባው፡፡
ግርማ ቆም ብሎ አስቦ ህዝቡን ይቅርታ ብሎ ጠይቆ እራሱን ከፖለቲካ ከማግለል ውጪ ሌላ አማራጭ ይኖረዋል ብዬ አላስብም ፓርቲው አንድነትም ቢሆን እንደግርማ ሠይፉ ያሉ አባላትን ይዞ መቀጠሉ ለፓርቲው አደጋ መሆኑን ተገንዝቦ ህዝቡን ይቅርታ ሊጠይቅ እና ግርማ ሠይፉን ሊቀጣው ይገባል ይህ ካልሆነ ግን ለወትሮውም በሐገራችን ፖለቲካ ተስፋ ለቆረጠው ህዝባችን ጭራሹኑ ፊቱን እንዲያዞር የሚያደርግ ታሪክ ሲወቅሠው የሚኖር ተግባር ከዛም አልፎ ሌሎች እየለፉ ያሉ ፓርቲዎች ላይ ህዝቡ እምነት እንዳይኖረው የሚያደርግ አስወቃሽ ስራ ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ በፊት ከግርማ እና ከፓርቲው መልስ ያስፈልጋል::

No comments:

Post a Comment