Translate

Monday, December 22, 2014

በምርጫ ቦርድ ደባ አንድነት አይደናገጥም! ሲል አንድነት ፓርቲ መግለጫ ሰጠ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የ2ዐዐ7 ዓ.ም አገራዊ ምርጫ እንደሚሳተፍና ለዚህም መተማመኛው ሕዝቡ መሆኑን ገልፀ «ተደራጅ 2007 ለለውጥ» በሚል መፈክር አንግቦ አገራዊና ሕዝባዊ ኃላፊነቱን ለመወጣትና ኢህአዴግን በቃህ ለማለት ሌት፣ ከቀን በንቃትና በትጋት እየሠራ ይገኛል።
በአሁኑ ወቅት ነፃ ሚዲያ በታፈነበትና በተዘጋበት አንድነት የራሱን የማተሚያ ማሽን ገዝቶ በየጊዜው ሆን ተብሎ በሚመስል መልኩ በሚጠፋው የኤሌክትሪክ ችግርን ለማሸነፍ የራሱን ከፍተኛ ኃይል ያለው ጀነሬተር በመግዛት በሣምንት የራሱን ጋዜጦችን እያተመ እያንዲያሰራጭ ተገዷል። ምሁራን፣ ወጣቶች፣ ጋዜጠኞችና ልዩ ልዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ለወሳኑ የ2007 ምርጫ ትግል እየተቀላቀሉት ይገኛሉ። አንድነት በአሁኑ ሰዓት ከመቼውም ጊዜ በላይ ትግሉን በአግባቡ ለመምራትና ለውጥ ለማምጣት በተሻለ ቆመና ላይ ነው ያለው።
በምርጫ ቦርድ በአንድት ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ ሆነ በገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ መተዳደሪያ ደንብ ውስጥ የሌለውን የጠቅላላ ጉባኤ አባላትና የምላተ-ጉባኤ ቁጥር በተሻሻለው ደንባችን ውስጥ እንድናካትት የተወሰነብንን ፈርድ ገምድል ድርጊት ሕገ-ወጥ መሆኑን ብናውቀውም ጠቅላላ ጉባኤ መጠራትን እንደ ጉዳት ሳይሆን አንደ ልዩ እድል በመቁጠር፣ 320 የጠቅላላ ጉባኤ አባላት በመጥራት የምርጫ ቦርድ ተወካይ በተገኘበት የተሳካና አንፀባራቂ ጠቅላላ ጉባኤ አካሄደናል። የጠቅላላ ጉባኤውንም ሰነድ ታህሣሥ 10 ቀን 2007 ዓ.ም ለምርጫ ቦርድ ገቢ ተደርጓል።

ሁሉ እንደሚገነዘበው በአሁኑ ሰዓት ሕዝቡ በኑሮ ውድነትና በሥራ እጦት ከመሰቃየቱም በላይ ሙስና ሰፍኗል፤ መልካም አስተዳደር የሕግ የበላይነት ከቶውንም ጠፍቷል። የሕዝብ የነፃነትና የዴሞክራሲ ጥያቄ ገዝፎና አፍጥጦ እየመጣ ነው። በመሆኑም ኢህአዴግ በፍርሃትና በጭንቀት እየራደ ነው። ምረጡኝ ብሎ ሕዝብ ፊት ለመቅረብ የሚያስችለው የፖለቲካና የሞራል ኃይል ስለሌለው ውሸት፣ ማስፈራራት ማሰር መግደል ማሸነፊያ መሣሪያዎች እንዳልሆኑትም በግልጽና በትክክል ተደራጅቷል። አሁን የቀረው ማሸነፊያው መንገድ አንድነት ፓርቲን በመዝጋት ነው የሚል ድምዳሜ ላይ በመድረሱ ጥንቱንም የአንድ ሣንቲም ሁለት ገጽታዎች የሆነውን ወኪሉን በመጠቀም በአንድነት ላይ ዘመቻ ከፍቷል።
ታህሣሥ 10 ቀን 2007 ዓ.ም በምርጫ ቦርድ ከፍተኛ አመራር የተሰጠው በቅጥፈትና በውሸት የተሞላው መግለጫም የሚያሳየውና የሚመሰክረው ይህንኑ ነው። ነገር ግን እውነቱን በአጭሩ እንደሚከተለው እናስቀምጣለን፡፡ አንድነት ፓርቲ ታህሣሥ 19 እና 20 ቀን 2006 ዓ.ም ያካሄደውን የጠቅላላ ጉባኤ ሰነድ ለምርጫ ቦርድ ካስገባ በኋላ ምርጫ ቦርድ ሐምሌ 20 ቀን 2006 ዓ.ም በተፃፈ ደብዳቤ በዘጠኝ ነጥቦች ላይ ማብራሪያ እንድንሰጥ ጠይቄን መልስ ሰጠን፤ በመቀጠልም ጥቅምት 2ዐ ቀን 2ዐዐ7 ዓም በተፃፈ ደብዳቤ ጥያቄ ከዘጠኝ ወደ ሦስት አውርዶ ላከልን ለዚህም አንድነት መልስ ሰጠ፡፡ ቀጥሎም ቦርዱ ህዳር 10 ቀን 2007 በተፃፈ ደብዳቤ ጥያቄውን ወደ አንድ አወረደው እንዲያውም በመጨረሻ ህዳር 19 ቀን 2007 ዓም በተፃፈ ደብዳቤ። «ፓርቲው በሰጠው ምላሽ የጠቅላላ ጉባኤ አባላት ብዛት 320 እንደሆነ አሳውቋል። ይሁን እንዷ በተሻሻለው መተዳደሪያ ደንብ ውስጥ አካቶ ያላቀረበ በመሆኑ ይህንኑ አሟልታችሁ እንድታቀርቡ በአክብሮት እናሳውቃለን» የሚል ነው። እኛም ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተን ይህንኑ ጥያቄ እንዲሟላ ከማድረጋችንም ባሻገር በሕገ-ደንባችን መሠረት በብሔራዊ ም/ቤት ተመርጠው የነበሩት የፓርቲውን ፕሬዚደንት ሹመት በጠቅላላው ጉባኤ አፀድቀናል። እንጂ አይነቱን በሕገ-ደንቡና በሥነ-ሥርዓት ለተከናወኑ ጉዳዮች ያልተገባና የተሳሳተ መግለጫ መስጠት በጣም አሳኝ ነው። በተለይም የሕዝብ ታዛቢዎች ታህሣሥ 12 ቀን 2007 ዓ.ም እንደሚመረጡ እየታወቀ ይህን ዓይነት መግለጫ መስጠት ሕዝቡ በጥንቃቄና በተደራጀ ምልኩ ትክክለኛነትና ሀቀኞች የሆኑ ታዛቢዎችን እንዳይመርጥ ለማሰናከል የታቀደ ይመስላል። በመሆኑም ዛሬም ሆነ ነገ አንድነት ፓርቲ ከሕዝብ ጋር ሆኖ ትግሉን አጠንክሮ ይቀጥላል አባላትም ሆነ ሕዝቡ ከፓርቲያችን ጎን ተሰልፎ ትግሉን እንዲያጧጡፈው ከአክብሮት ጋር እንጠይቃለን።
ድል የህዝብ ነው!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

No comments:

Post a Comment