Translate

Wednesday, June 25, 2014

በደቡብ ክልል እየታየ ያለው መንግስታዊ አፈናና ፀረ-ሕግ አቋም እንዲገታ ትግላችንን አጠናክረን እንቀጥላለን! (UDJ)

UDJ
June 24, 2014
ከአንድነት ፓርቲ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
ባለፉት 23 ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ ስርዓቱ አምጦ የወለዳቸው ሀገራዊ አፈና፣ ማዋከብ፣ የመኖር ዋስትናን መንፈግ፤ ዜጎችን ማሰደድና ማሰር የተለመዱ ድርጊቶ ሆነው ኖረዋል፡፡ አሁንም በዚህ አስከፊ የአፈና መንገድ ጉዞውን ቀጥሏል፡፡ የስርዓቱ መንግስታዊ አፈናና ፀረ-ሕዝብ አቋም በመላ ኢትዮጵያ የተዘረጋ ቢሆንም ፓርቲያችን በእንቅስቃሴዎቹ ውስጥ እንደታዘበው በደቡብ ክልል በተለየ ሁኔታ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በተለይም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በክልሉ የሚገኙ የተለያዩ ሹማምንቶች ባደረባቸው የገዥነት መንፈስ ሰላማዊ እንቅስቃሴዎችን በማፈንና ብሎም ያለምንም ማስረጃና ምክንያት ሰላማዊ ታጋዮችን ወደ እስር ቤት በመክተት ተግባራዊ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡UDJ/Andinet party logo
ከዚህ በፊት በክልሉ በወላይታ ዞን ሶዶ ከተማ የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች ከዞኑ አመራሮች ጋር ውይይት ሲያካሂዱ ድንገተኛ ወረራ ተደርጎና የግቢ በር ተሰብሮ ወደ እስር ቤት ተወስደው ነበር፤ ቁጫ ላይ ጠርተነው የነበረው ሰላማዊ ሰልፍም እንዲሁ በጉልበት፣ በእስርና አፈና እንዳይካሄድ ተደርጓል፤ ይባስ ብሎ ደግሞ የክልሉ ዋና ከተማ በሆነችው አዋሳ የጠራነው ሰላማዊ ሰልፍ ተገቢውን ህጋዊ ሂደት ቢያልፍም በህገ-ወጥ እስር እንዲጠናቀቅ ሆኗል፡፡ ይህ እውነትም በክልሉ በተለየ ሁኔታ መንግስታዊ አፈናና ፀረ-ሕግ አቋም እንዳለ ያረጋገጠ ነው፡፡

አዋሳ ከተማ ላይ የጠራነው የተቃውሞ ሰልፍ በሚካሄድበት ማግስት ከ30 በላይ አባሎቻችንን፣ የዞኑን አመራሮችና ከአዲስ አበባ ለቅስቀሳ የሄደውን ቡድን ከነ መኪናው ወደ እስር ቤት በመውሰድ መንግስታዊ አፈናውን በገሀድ አሳይተዋል፡፡ በደቡብ የተፈጠረው የገዥነት መጥፎ መንፈስ የተጠናወታቸው የታች ባለስልጣናት ህግ በአደባባይ እንደረገጡ ታይቶበታል፡፡ አሳሪዎቹ በቅስቀሳ ላይ የነበሩት አባላትና አመራሮቻችን ‹‹ህጉን ጠብቀን አሳወቅን፣ የእውቅናውን ደብዳቤ መስጠት ይህን ሊሰራ የተቀመጠው አካል ድርሻ ነው፡፡ እውቅና ወረቀቱን የሚሰጠው አካል ስራውን ስላልሰራ እኛ ስራ ማቆም የለብንም፡፡›› ለሚለው መልስ ስላልነበራቸው ማሰርን እንደ መፍትሔ ወስደዋል፡፡ ህገወጡን የአትቀስቅሱ ትእዛዝ ከመቀበል መታሰር እንደሚሻል እጃቸውን ለካቴና የሰጡ አባሎቻችንና አመራሮች አረጋግጠዋል፡፡
ፓርቲያችን እንደሚገነዘበው የህዝቡ የለውጥ ፍላጎት ገፍቶ በወጣ ቁጥር የአምባገነኖች መደናበር ያይላል፡፡ ሲደናበሩም ህግ ይጥሳሉ፣ ህዝብ ያሰቃያሉ፣ ሀገር ይበድላሉ፡፡ አፋኞች ያልተገነዘቡት እድሜ ልክ ዕየተጨቆኑ መኖር እንደማይቻል ብቻ ነው፡፡
አንድነት እንደዚህ አይነቱን አይን ያወጣ አፈናና ፀረ-ሕግ አካሄድ በቸልታ አይመለከተውም፡፡ በክልሉ ለመዝጋት እየተሞከረ ያለውን የህዝብ ጥያቄ ከህዝብ ጋር በመሆን መፍትሔ እንዲያገኝ እናደርጋለን፡፡ በህግም እንጠይቃለን፡፡ በክልሉ ነፃ ምርጫ እንዳይካሄድና ህዝቡ በንቃት እንዳይደራጅ እየተደረገ ያለ ጥረት አካልም ነው፡፡ ያለምንም ወንጀል የታሰሩ አባሎቻችንና አመራሮቹ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በአስቸኳ እንዲፈቱ የሚመለከተው አካል ሃላፊነቱን እንዲወጣ እያሳሰብን በደቡብ ክልል እየታየ ያለው መንግስታዊ አፈናና ፀረ-ሕዝብ አቋም መታገላችንን እንደምንቀጥል እናረጋግጣለን፡፡
ድል የህዝብ ነው!!!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ሰኔ 16 ቀን 2006 ዓ.ም
አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment