Translate

Thursday, June 5, 2014

ዶ/ር ብርሀኑን ለመጀመሪያ ጊዜ እንዳየሁት

ሁኔ አበሲኒያዊ ፒተርቦሮው ዩ.ኬ

Dr. Berhanu Nega Ginbot 7 Chairman
ግንቦት 97 ዓ.ም ለሐገራችን ፖለቲካ ተስፋን ይዞ የመጣ ትልቅ እድል ነበር የምርጫው እለት እኔም በአሁኑ ሠዓት አውስትራሊያ ከሚኖር ወዳጄ ጋር በመሆን በጠዋት ወጥተን በያዝኳት አንድ ካርድ ኢህአዴግን ለመጨረሻ ጊዜ ከስልጣን በማባረሩ ሒደቱ ተሳታፊ ለመሆን ምርጫ ጣቢያ ደርሰናል በድንገት ግን አንድ ተዐምር ተከሠተ ዶ/ር ብርሐኑ ነጋ የሠፈራችን ምርጫ ጣቢያ ለቅኝት ተገኘ አካባቢው በፉጨት ተናጋ እልልታ ጭፈራው ደራ፣ ሰው ሁሉ ዶ/ር ብርሐኑ እየሮጠ ላይ መጠምጠም ጀመረ እኔና ጓደኛዬ ሁኔታውን በአድናቆት መከታተል ያዝን ወዲያውም በአካባቢው ይገኙ የነበሩ ሠዎች ኮተቤ ደጃዝማች ወንድራድ ት/ቤት አካባቢ በሚገኝ አንድ ግሮሠሪ በመውሰድ ምግብ ሊጋብዙት እንደሚፈልጉ ነገሩት ያ ድንቅ ሠው ዶ/ር ብርሐኑ ግን አሻፈረኝ መሄድ አለብኝ ሲል ቢናገርም አንድ አዛውንት ጠጋ ብለው እንዲህ አሉት ”የኛን ግብዣ ንቀህ ካልሆነ በቀር እምቢ የምትልበት ምንም ምክንያት የለም አንተ ነፍስህን ለእኛ ስትል ለመክፈል የተዘጋጀህ ነህ እኛ ለምሳ ብንከፍልልህ ምን አለበት” ሲሉት ዶ/ር ብርሐኑ ላይ የትካዜ እና የፍቅር ፊት አነብ ነበር፡፡

ዶ/ር ብርሐኑ በሰው ተከቦ ምግቡን ከበላ በኋላ ህዝቡ ዶ/ር ብርሀኑ መኪናው ውስጥ እስኪገባ ድረስ ግማሹ በለቅሶ ግማሹ በደስታ ተሸክመውት ይጨፍሩ ነበር እኔም ህዘቡ ብርሐኑን ምን ያህል እንደሚወዱት ባየሁኝ ጊዜ ይህንን ድንቅ ኢትዮጵያዊ እግዚአብሔር እንዲጠብቀው እና የህዝቡን ልብ የሚያረካ ድርጊት እንዲፈፅም ሲል ከልብ ተመኘው ምንአልባት ያ የኮተቤ አካባቢ ህዝብ ፍቅር በብርሐኑ ህሊና ውስጥ እየመጣ ይሆናል ብርሐኑን እንደዚህ በየመድረኩ ህዝቡን ለማገልገል ቃል እንደገባ እንዲናገር ያስቻለው፡፡
አሁን ዶ/ር ብርሐኑ ወደ መኪናው ገብቷል የኮተቤ ህዝብ ግን ለዶ/ር ብርሐኑ ያለውን ፍቅር መግለፅ አላቆመም
ይለያል ይለያል ይለያል ዘንድሮ
የወያኔ ኑሮ
…………………….
ብርሐኑ ተስፋችን
ብርቱካን ተስፋችን
መስፍን ተስፋችን
ያዕቆብ ተስፋችን
ግዛቸው ተስፋችን
ኢትዮጵያ ሐገራችን
……………………
ተከብረሽ የኖርሺው በአባቶቻችን ደም
እናት ኢትዮጵያ የደፈረሽ ይውደም!!!!!!!!!!!
…………………………………
ብርሐኑ ያንን ህዝብ አስከትሎ ሐና ማርያም 32 ማዞሪያ ተብሎ የሚጠራው አካባቢ ደርሷል ጉዞው 02 ቀበሌ ምርጫ ጣቢያ የሚገኘውን ህዝብ ሁኔታ መከታተል ነው ሆኖም 02 ምርጫ ጣቢያ አካባቢ ሠልፍ ተሠልፈው ተራቸውን ሲጠብቁ የነበሩ የአካባቢው ሠዎች የዶ/ር ብርሐኑን ወደአካባቢው መምጣት ሲሠሙ ግልብጥ ብለው በመውጣት ብርሐኑን መተንፈሻ እስኪያጣ ድረስ አንገቱ ላይ ተጠመጠሙበት ምሳ ሊጋብዙት እንደሚፈልጉም ገለፁለት ብርሐኑ እባካቹህ ልቀቁኝ በሚል ፊት እንዲህ ሲል ተማፀነ “ወንድራድ አካባቢ ያሉ ሠዎች ምግብ ጋብዘውኝ ደስ ብሎኝ መጥቻለው እባካቹህ አሁን ሌላ ምርጫ ጣቢያ ሄጄ ሁኔታውን መከታተል አለብኝ” ሲል ቢማፀንም ህዝቡ ንግግሩን ከቁብም ሳይቆጥር ብርሐኑን ተሽክሞ ወደ ቅድሚያ ቡና ገሠገሠ (ቅድሚያ ቡና በአሁኑ ሠዓት ይፍረስ ይኑር እርግጠኛ አይደለሁም) ብርሐኑንም የህዝቡ የፍቅር መግለጫ እንደሆነ ስለገባው እንዲሁም አማራጭ በማጣትም ወደ ቅድሚያ ቡና ገባ።
ዶ/ር ብርሐኑ ኮተቤ 02 ቀበሌ አካባቢ በሚገኘው ቅድሚያ ቡና በአካባቢው ህብረተሠብ የቀረበለትን ግብዣ ከተቀበለ በኋላ ወጣቶቹ ትከሻቸው ላይ ተሸክመውት እየጨፈሩ ከቅድሚያ ቡና ወጥተው በጥላሁን ገሠሠ ኢትዮጵያ ዘፈን ታጅበው ወደ 02 ቀበሌ ምርጫ ጣቢያ ገሠገሱ በወቅቱ የወረዳው የቅንጅት እጩ ተወዳዳሪ የነበሩት ረዳት ፕሮፌሠር ቶማስ ቶልቻ የህዝቡን ፍቅር እያዩ ያለቅሱ እንደነበር አስታውሳለው፡፡ (በነገራችን ላይ ረዳት ፕ/ር ቶማስ ቶልቻ ከምርጫ 97 በኋላ በደረሰባቸው ስነልቦናዊ ጫና እጅግ ተስፋ መቁረጥ ይታይባቸው የነበረ ሲሆን ምርጫ 97 ከተጠናቀቀ ከጥቂት አመት በኋላ ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል የቅድሚያ ቡና ባለቤትም እስከአሁን ድረስ ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ ሞተው ተገኝተዋል)።
ዶ/ር ብርሐኑ ነጋ በአካባቢው ያለውን የምርጫ አካሄድ እየቃኙ ባሉበት ሠዓት ከህዝቡ እየተሠጣቸው ያለውን ማበረታቻ እና ፍቅር ቁጭ ብለው በማየታቸው ከፍተኛ ንዴት ውስጥ የገቡት የወቅቱየወረዳ 28 የኢህአዴግ ፅ/ቤት ኃላፊ የነበሩት አቶ ቢኒያም የተባሉ ካድሬ ፖሊሶችን በመጥራት ሠውዬው የምርጫ ስርዓቱ እንዲበላሽ እያደረጉ ከመሆኑም በላይ ኢህአዴግን ለመምረጥ የተሰለፉ ዜጎች ላይ ፖለቲካዊ ተፅዕኖ ሊያደርጉ ይገባል ሲሉ በማስጠንቀቃቸው ምክንያት ዶ/ር ብርሐኑ አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ በፖሊሶች ትዕዛዝ ደረሳቸው ይህንን የሠማው የኮተቤ ህዝብ ማጉረምረም ሲጀምር ዶ/ር ብርሐኑ የአካባቢውን ህዝብ አረጋግተው ወደመጡባት አሮጌ መኪና በመግባት ኮተቤን ለቀው ወደ መገናኛ ገሠገሱ፡፡
እኔና ጓደኛዬ ይህንን ሁሉ ትዝብት ታዝበን እየተነጋገርን ቀናቶች አልፈው ሳምንታቶች ሔደው ሰኔ አንድ ላይ ደረስን በዛች የተረገመች ቀን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የምርጫውን መጭበርበር ተከትሎ ባሠሙት የተቃውሞ ድምፅ በአጋዚ ወታደሮች ተይዘው ወደ ሠንዳፋ ሲያቀኑ ከቀሪው የኮተቤ ህዝብ ጋር በመሆን ተማሪዎቹን በመንደራችን አሳልፋቹህ አትወስዱም ስንል መሳሪያ ከያዙ የአጋዚ ወታደሮች ጋር ግብግብ ፈጠርን ሁኔታው በዚህ አላበቃም መንገዶች በትላልቅ ድንጋዮች መዘጋት ጀመሩ የፖሊስ መኪናም ኮተቤ መምህራን ኮሌጅ አካባቢ መቃጠሉ ተሠማ አሁን የመከላከያ ኃይሉ በአንድ እዝ ስር ሆኖ በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ እጅ በአዋጅ ስለገባ ትዕዛዝ ከጠቅላይ ሚኒስቴሩ ወደገዳዮቹ አጋዚዎች ደረሠ የኮተቤ አስፋልት በአንድ ወገን ምንም ባልያዙ በወንድራድ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች፣ በኮተቤ መምህራን ኮሌጅ ተማሪዎች እና በአካባቢው ነዋሪዎች በሌላ ወገን መሳሪያ በታጠቁ አጋዚዎች ተወሯል በእዚህ ወቅት አንድ አስደንጋጭ ነገር ተከሠተ የደጃዝማች ወንድራድ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ህፃናት ተማሪዎች ከት/ቤታቸው ተለቀው አጋዚ ወታደሮችን ሲያዪ በድንጋጤ ወደ ተለያዩ ቦታዎች ይሯሯጡ ነበር ህፃናቶቹን ለማሸሽ ወደት/ቤቱ የጎረፈው ህዝብ ላይ ተኩስ የጀመሩት አጋዚዎች የመጀመሪያውን ነፍስ አጠፉ የተገደለችው የደጃዝማች ወንድራድ የ4ኛ ክፍል ተማሪ የነበረች ህፃን ልጅ ነች አንዳንድ ሠዎች መጀመሪያ የተገደለችው ሽብሬ ደሳለኝ እንደሆነች ይገልፃሉ ነገር ግን እኔ እስካለኝ መረጃ ቅድሚያ ስትገደል በአይኔ ያየሁት ያቺን አንድ ፍሬ ልጅ ያቺን ዛሬ ላይ ብትኖር ገና ዩኒቨርሲቲ ተማሪ የምትሆን ያቺን እናቷ ናፍቃት እናቷ ላይ ልትጠመጠም ስትገሰግስ የነበረች የአጋዚ ጥይት እራት የሆነች የወንድራድ ት/ቤት ዩኒፎርም የለበሠች ህፃን ተማሪን ነው፡፡
ከዚያ ግድያው ቀጠለ የኮተቤ ወጣቶችም የተወሰኑ አጋዚዎች ላይ ጉዳት አደረሱ በዛ ግርግር መሐል እስከአሁን ምክንያቱ ሊገባኝ ባልቻለ መልኩ 33 ቁጥር አውቶቡስ ከግርግሩ መሐል ተገኘች የአካባቢው ወጣቶች ሹፌሩን አስወርደው ወንድራድ ት/ቤት ደጃፍ ላይ አጋዩት ሰኔ ሁለትም የትራፊክ ፖሊስ ሞተር ሲቃጠል አጋዚዎች ግድያቸውን እና አፈሳቸውን ቀጠሉ እኔና ጓደኛዬም የአፈሳው እጣ ደርሶን ሠኔ 3 ሠንደፋ ከበርካታ የሐገራችን ህዝቦች ጋር ታሠርን እስከተፈታንበት ህዳር 8 1998 ዓ.ም ድረስ የተለያዩ ግጭቶች ኮተቤ አካባቢ ይሠሙ እንደነበር ለመታዘብ ችያለው፡፡
ያ ኮተቤ ላይ ህዝቡ ተሸክሞት ሲጨፍር የነበረው ምሁሩ ዶ/ር ብርሐኑ እና ጓደኞቹ የኢህአዴግን ምክር ከሠሙት ከእነልደቱ ተለይተው እስር ቤት ገቡ ዳግመኛ ብርሐኑን ሳላየው ብርሐኑም ተሠደደ እኔም…
ሁኔ አበሲኒያዊ
ፒተርቦሮው ዩ.ኬ

No comments:

Post a Comment