Translate

Monday, January 27, 2014

ስኬታማ ውድቀት (Successful Failure!)

ይሄይስ አእምሮ (አዲስ አበባ)

Ethiopian books reviewለውድቀት ስኬት “የምሥራች!” ወይም “እንኳን ደስ ያለን!” የማይባል ነገር ሆኖብኝ እንጂ ከነዚህ የደስታ ማብሠሪያ አባባሎች በአንደኛው ጽሑፌን መጀመር ቃጥቶኝ ነበር፡፡ ለማንኛውም ሀገራችን በማንኛውም ዘርፍ በገባችበት ውድቀትና ኪሣራ ምክንያት ልባችሁ ያዘነና ቅስማችሁ የተሰበረ ወገኖቼን “እግዚአብሔር ያጽናችሁ፤ የሀገራችሁን ትንሣኤም ፈጣሪ በአፋጣኝ እውን እንዲያደርግላችሁ የእግዚአብሔርን ልብ ያራራላችሁ” በሚለው የልመና ቃል ፈጣሪን እየተማጸንኩ ወሬየን ልቀጥል፡፡ ትንሽ በንዴት እንድትንጨረጨሩ ፈቃዳችሁ ይሁንልኝ፤ መልካም መንጨርጨር!

ሰሞኑን ለራሴ የጥሞና ጊዜ እንዲኖረኝ ፈለግሁና በንባባዊ አርምሞ ሰነበትኩ፡፡ በግሌ እንደብዙዎች ሰዎች ብዙ ጉድለት አለብኝ፡፡ ከነዚህ አንድኛው በመሸታ ቤቶችና በግል ግንኙነቶች ከጨዋታዎች ከምሰማው፣ ከመገናኛ ብዙኃን ከምከታተለው፣ በትምህርት ምክንያት ካገኘኋቸው አነስተኛ ግንዛቤዎችና ከጥቂት ንባቦች በስተቀር ስለሀገሬ ታሪክ ብዙም ዕውቀት አልነበረኝም፡፡ ይህን ትልቅ ክፍተት በተቻለ መጠን ለማጠጋጋት አንድ ሃሳብ መጣልኝ – ማንበብ፡፡ እርግጥ ነው የጥንታዊቷን ኢትዮጵያን ቀርቶ የትናንቷን አሜሪካን ታሪክም ቢሆን በንባብ ለመረዳት መሞከር አባይን በጭልፋ እንደማለት በመሆኑ ይህን መሰሉን ታላቅ ተግባር በአንድ ሰው ዕድሜ ማከናወን  ከባድ ብቻም ሣይሆን ከነአካቴው የሚቻል አይደለም፡፡ ግን ከለዬለት ድንቁርና በተወሰነ ደረጃ መውጣት የሚቻለው ራስን በንባብ ማበልጸግ ሲቻል በመሆኑ ጊዜየ በፈቀደልኝ ጥቂት መጻሕፍትን – ከፊተኞችም ከአሁነኞችም – ባለፉት ሦስት ወራት ውስጥ ለማንበብ ሞከርኩ፡፡ ወደ አሥር ይጠጋሉ፡፡ ከነዚህ ግንዛቤ አስገኚ መጻሕፍት ውስጥ የርዕዮት ዓለሙ “የኢሕአዴግ ቀይ እስክርቢቶ” የሚለው አንዱ ነው፡፡ እመለስበታለሁ፡፡
የአለቃ ተክለኢየሱስ “የኢትዮጵያ ታሪክ” መጽሐፍ ሌላው ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ ዶክተር ሥርግው በሚባሉ ምሁር የአርትዖት ሥራ እንደተካሄደበት ተገልጾኣል፡፡ ግሩም እሳት ነው፤ ሲያነብቡት እያቃጠለ፣ እየለበለበና ኢትዮጵያዊነትንም እያስረገመ ተነብቦ ማለቁ አይቀርም ያልቃል፡፡ ከነዚህ መጻሕፍት ውስጥ ሥልጣን የማይወዱ መሆናቸውን በማስረዳት የሕይወት ዘመናቸውን እያገባደዱ የሚገኙት ፕሮፌሰር መስፍን የጻፉት “አገቱኒ”ም በስህተት ለሁለተኛ ጊዜ አንብቤዋለሁ፡፡ “ካረጁ አይበጁ ነው”ና ደግሜ እያነበብኩት መሆኔን እስክረዳ ብዙ ገፆችን ብጓዝም ጊዜና የማንበብ ፍላጎት ሞልቶ እንደተረፈው ሰው ጨረስኩት (በዚች መጽሐፍ ላይም በጨረፍታ ብመለስ ደስ ይለኛል)፡፡ ኢትዮጵያ የማያውቋት ሁሉ ዝናዋን ከሩቅ በመስማት ውዱን ሕይወታቸውን ሣይቀር ሊገብሩላት የፈቀዱ የዓለም ዜጎች እንደነበሩ “ጥቁር አንበሣ” በሚል መጽሐፍ ተጋድሎውን ካነበብኩለት ኩባዊ ሻምበል ልረዳ ችያለሁ፡፡ ይህን “ጉራ” የምቸረችርላችሁ ስለሁለት ምክንያት ነው፤ አንዱ ጉድለትን ለማስተካከል በግድ ወደንባብ መዞር እንደሚገባን በተለይ ለወጣቱ ትውልድ ለመጠቆም ነው፡፡ ሁለተኛውን ረሳሁት፡፡
የተሣካ ውድቀት ውስጥ መግባት እኛ ኢትዮጵያውያን ብርቃችን እንዳልሆነ ያነበብኳቸው መጻሕፍት ሁሉ በኩራት ይመሰክራሉ፡፡ እነዚህም ሆኑ ሌሎች በተለያዩ አጋጣሚዎች የማውቃቸው ታሪኮቻችን የሚነግሩኝ አንድ ነገር ቢኖር እኛ ኢትዮጵያውያን አንድ የሚጎድለን የተፈጥሮ ቅመም መኖሩን ነው፡፡ ይህ የጎደለን ቅመም እጅግ መሠረታዊ ከመሆኑ የተነሣ ፈልገን ካላገኘነውና ካላስተካከልነው ከአሁን በኋላ አምስት ሚሊዮን ዓመታትም በሀገርነትና በሕዝብነት ብንኖር በዬጊዜው ከምንገባባቸው የተሣኩ ውድቀቶች መውጣት ፈጽሞውን አይቻለንም፡፡ ብዙዎቻችን አዘውትረን እንደውዳሤ ማርያም እንደምንደጋግመው ምቀኝነትና የሥልጣን ጥም በደማችንና በመቅኒያችን የመሸጉብን ስለመሆናቸው የቀድሞና የአሁን ታሪካችን ነጸብራቅ የሆኑ እነዚህን መጻሕፍት በማንበብ መረዳት ይቻላል፡፡
አልጋ ለመቀማት ወይም አልጋውን ላለመቀማት ሲል ንጉሥ አባት ልዑል ልጅን በጦርና በጎራዴና ምግብን በመመረዝ ሣይቀር የሚገድልበት፣ ነገሥታት ከሀገራዊ ልማት ይልቅ ለሥልጣናቸው ሲሉ ለብዙ አሠርት ዓመታት በማያቋርጡ ጦርነቶች ራሳቸውንና ሕዝባቸውን የሚማግዱበት፣ ለሥልጣንና ለሹመት ሲባል አንዱ ሌላውን በመርዝና በሰይጣናዊ መተትና ድግምት የሚጨራረሱበት፣ የሥልጣን አራራን ለማስታገስ ሲባል የገዛ ሚስትን ሳይቀር ለከፍተኛ መሪዎች እያቀረቡ በትዳርና በ“ፍቅር” ጡር የሚሠራበት፣ ሃይማኖትን መሣሪያ በማድረግ ሕዝብ ከእውነተኛ የፈጣሪ መንገድ እንዲወጣና የነገሥታት ባሪያ እንዲሆን የሃይማኖት መሪዎችና ነገሥታት የሚመሣጠሩበት፣ በዕብድና ወፈፌ  ነገሥታት  የደንቆሮ አገዛዝ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በረባ ባልረባው ሚዛን የማይደፋ ምክንያት እጅ እግራቸው እንዲቆረጥና በ“እኔን ያዬህ ተቀጣ” ለመቀጣጫነት የሚዳረጉበት፣… አሣፋሪ ሁኔታ ከኢትዮጵያ ውጪ በሌላ ሀገር ስለመኖሩ በበኩሌ አላውቅም፡፡ የትናንቱ ድንቁርናችን ተባብሶ ዛሬም በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን  የምናስተውላቸው የውድቀታችን መንስኤዎች ከጥንቱ የተወረሱ እንደሆኑ መገንዘብ አይከብድም፡፡
ውድቀት ምንድነው? እንዴትስ ይታወቃል?
ብዙ መፈላሰፍ አያስፈልግም፡፡ በአጭሩ ውድቀት ማለት ኢትዮጵያ ማለት ነው፡፡ ኢትዮጵያና ውድቀት በፍቺ ይመሳሰሉ፤ አንዱ ቃል ሲጠራ ሌላው ይታወሳል፡፡ ይህን ለመገንዘብ ወደ ኢትዮጵያ መምጣትና እየተዟዟሩ መጎብኘት ነው፤ በሁሉም ዘርፍ የተዘፈቅንበትን ኪሣራና ድቀት (Decadence) በአጭር ጊዜ ውስጥ ማየት ይቻላል፡፡ ልብ ማለት ያለብን ነገር ደግሞ ሕንጻና መንገድ የዕድገት ምልክት አለመሆናቸውን ነው፡፡ ኢትዮጵያ እንደዚህ ዘመን በተሣካ ውድቀት ውስጥ የገባችበት ዘመን የለም ማለት ይቻላል፡፡ የጥንት አባትና እናቶቻችን የጀመሩት ውድቀት ግዘፍ ነስቶ በአካል የታየው አሁን ባለንበት ዘመን ላይ ነው፡፡ ከታክ የማንማር፣ ጥፋትን እያሻሻልንና እያዘመንን ለሌላ ጥፋት ዝግጁ የምንሆን ዜጎች ብንኖር እኛ ኢትዮጵያውን ብቻ ነን፡፡ አሁን ያለንበት የውድመት ደረጃም ሲያንሰን ነው፡፡ የማንተዛዘን፣ አንዳችን በአንዳችን መከራ የምንደሰት፣ በአንዳችን መቃብር ላይ ሌላኛችን የሠርግ ዳስ የምንትል እጅግ ክፉዎች ነን፡፡ እውነት ቢነገር ምን ያመጣል? ምንም!!
ብዙ የውድቀት መከሰቻዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ አንዱ የውድቀት ምልክት የአርአያሰብዕ (Iconic Figure(s)) መንጠፍ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በተለይ ወጣቱ ትውልድ “ወደፊት እንደ እገሌ ነው የምሆነው!” ብሎ ከፊት ለፊቱ የሚያስቀምጠው ሰው እየጠፋ ነው፡፡ ዙሪያ ገባውን ብንቃኝ አርአያ የሚሆን ሰው ማግኘት እንቸገራለን፡፡ ይህ ዓይነቱ ድርቀት ዋና ሀገራዊ ኪሣራ ነው፡፡ የነበሩን መልካም ሰዎችና በሥራቸው አንቱ የተባሉ ዜጎች ብዙዎቹ ከመሬት ሥር ውለው ጥርኝ አፈር ሆነዋል፤ በጣት የሚቆጠሩ ቢኖሩም ዘመኑ ለነሱ አርአያነት ምቹ ባለመሆኑና በወቅቱ የወያኔ መንግሥት በጠላትነት ስለሚፈረጁ በሀገር ውስጥና በውጪው ዓለም ተደብቀዋል፡፡ በወቅቱ መንግሥት ትልቅ ዜጋ ማለት የወያኔን ዘረኛ መንግሥት ፖሊሲዎች ተቀብሎ በወንጀልና በኃጢኣት መመላለስን የመረጠ፣ በሰይጣናዊ ተግባራት ተጠምዶና በባዕድ አምልኮት ተጠምቆ ለሥጋው ድሎት ብቻ  የቆመ ነው፡፡ ከዚያ ውጪ በአንጻራዊ አነጋገር የተሻለ በሚባል ኢትዮጵያዊ የአንድነት ዘመን ውስጥ በምርጥ ዜግነት የሚያሳውቁ ማኅበራዊና ምሁራዊ ተግባራትን በአሁኑ የወያኔ ዘመን ማከናወን ለእሥርና ለእንግልት እንዲሁም ለስደት ይዳርጋል፡፡ ሆዳምነትና ዋልጌነት በነገሠበትና የመንግሥት መታወቂያ በሆነበት ዘመን የሀገርና የሕዝብ አለኝታ ሆኖ ብቅ ማለት ሌላው ቀርቶ ባልተፈጸመ ወንጀል – የወያኔ የወንጀል መፈብረኪያ የደኅንነት መሥሪያ ቤት በሚሸርበው የፈጠራ ክስ – ወህኒ ሊያስወርድ ይችላል፡፡ የቴዎድሮስ ካሣሁንን መስዋዕትነት ያስታውሷል፡፡ ወሩ በገባ በ22ኛው ቀን የሞተን ዜጋ ወሩ በገባ በ23ኛው ቀን ከውጪ ሀገር በመጣው ቴዲ ላይ መላከኩ የገጪውና የተገጪው ግንኙነት ምናባዊ እንጂ እውናዊ መሆኑን እንኳንስ ‹ፍርድ ቤቱ›ና ከሳሾቹ እኛም እናውቅ ነበር – ማወቅ በራሱና ብቻውን ዋጋ የለውም እንጂ፡፡ ወያኔ መርዘኛ በቀለኛ ነው፡፡ ወያኔ ከመረዘ ሳያንፈራፍር በቀላሉ አይለቅም፡፡
በአሁኑ ወቅት ምሁር አለን ማለት ያስቸግራል፡፡ አድርባይና እበላ ባይ አስመሳይ ወይም በዘመኑ ቋንቋ ‹ፎርጅድ› ምሁር እንጂ ትክክለኛው ምሁር በመብራት ተፈልጎም አይገኝ፤ አሉ ከሚባሉት ጥቂት ወጣትና አንጋፋ ምሁራንም መካከል በትዕቢትና በትምክህት የማይወጣጠሩ ልሂቅነታቸው ያላሳወራቸው  ትሁት የሕዝብ አገልጋዮችን ለማግኘት መቸገራችን አልቀረም – ከወደቁ አይቀር ውድቀቱ ሁለንተናዊ መሆን አለበትና ይህ የኢትዮጵያ ምሁራን መኮፈስ የማይጠበቅ አይደለም፡፡ ሁሉንም ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ወታደራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሃይማኖታዊ ዘርፎች ብናይ አርአያ ሊሆኑን የሚችሉ ድንቅ ዜጎችን ሣይሆን ለሆዳቸው ያደሩ አጋሰስና ግልብ ዜጎችን ነው የምናገኝ – በአብዛኛው፡፡ ሆድ ሰውነትን ሲገዛው ጭንቅላት ይጫጫና ከርስ/ቦርጭ ውስጥ ወርዶ ይወተፋል፡፡ ያኔ ኅሊና ትጠፋና ሆድአደርነት የማያፍሩባት ይልቁንም የሚኮሩባት የወቅቱ ፋሽን ትሆናለች፡፡ ሀቀኝነት እያሳፈረ ቅጥፈትና ዕብለት ያሾማል፤ ያሸልማል፡፡ በከንቱ ካልታበይንና ባለፈ የደግ ዘመን ጥቂት ታሪክ ተጀቡነን በተረት ተረት መኖርን ካልመረጥን በስተቀር ሀገራችን በዚህ አሣፋሪ ሂደት ውስጥ ትገኛለች – በችኮላ የ‹ደርግ ዘመን› ብላችሁ እንዳታነቡብኝ አደራችሁን፡፡ የሚብለጨለጨውን የቻይና ቴክኖሎጂና ሕንጻና መንገድ በዚህ ስሌት አናስገባውም፡፡ መጥፎ ነው ማለት ግን አይደለም፡፡ እነዚህ የሚታዩ ኳሻርኳራዊ የኢኮኖሚ ዕድገት ውጤቶች በተወሰነ ደረጃ በሀገር ምስል ላይ አወንታዊ ሚና ስለሚጫወቱ መልካም ነገሮች ናቸው፡፡ ውድቀታችንን ግን ሊታደጉ ወይም ሊሸፍኑና እንዳልወደቅን ሊመሰክሩ ግን አይችሉም፡፡
ለእውነት ሲል የወያኔን ግፈኛ አገዛዝ በጥናታዊ ጽሑፉ አጋልጦ ሲመረቅ የለበሳትን ጥቁር ገዋን ያስመሰገነ ምሁር እንፈልግ – ካገኘን እሰዬው፡፡ በሚያገኘው ደሞዝ ብቻ እየኖረ ሕዝብን የሚያገለግል ባለሥልጣን እንፈልግ – ካገኘን እሰዬው፡፡ (እዚህ ላይ የአቶ ገብሩ አሥራትን ከሙስና የጸዳ ስብዕና ሳልጠቅስ ማለፍ አልፈልግም፡፡ አንድ ሰው የተለዬ ቆንጆ ምግብ ያምረውና ወደገብሩ ቤት በእንግድነት ይሄዳል – ቀደም ሲል ገብሩ የትግራይ ክልል ፕሬዚደንት በነበረበት ወቅት ነው፡፡ የቀረበለት ምግብ  ግን የጠበቀው ሥጋና በአትክልትና ፍራፍሬ የታጀበ የሀብታም ብፌ ሣይሆን ተራ ቀይና አልጫ የሰላሱት ምግብ ይሆናል፡፡ ሰውዬው በግልጽነት  “እዚህ ቤት እንዲህ ያለ ምግብ ነው እንዴ እሚዘጋጀው?” ብሎ ይጠይቃል፡፡ ያገኘው መልስ “የምንኖረው መንግሥት በሚከፍለን ደሞዝ ብቻ በመሆኑ ከዚህ የተለዬ ምግብ ማዘጋጀት አንችልም፡፡” የሚል ነበር፡፡ ይህችን እውነት ለመተንፈስ አጋጣሚ እፈልግ ነበር – ዛሬ ተሳካልኝ፡፡) በሚያገኘው ደሞዝ ብቻ እየኖረ የሀገርን ዳር ድንበር የሚያስከብር አንድም ቢሆን የመከላከያ ወይም የፖሊስ  ሠራዊት መኮንን ብናገኝ ዕድለኞች ነን፡፡ የፈጣሪና የመንግሥት ሕጎች በሚያዙት መሠረት ነግዶ የሚከብር ቢያንስ አንድ ነጋዴ እንኳን ቢኖረን አሁንም ዕድለኞች በሆን፡፡ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት በቤተ መቅደስ እንደሚያንበለብለው ሁሉ በሕይወቱም ፈጣሪን የሚታዘዝ ቢያንስ አንድ ጳጳስ ቢኖረን ሎጥን ያገኘን ያህል በቆጠርነው ነበር፡፡ ቴዎድሮስ ካሣሁንንና ሻምበል በላይነህን ከመሳሰሉ በጣት የሚቆጠሩ የኪነ ጥበብ ሰዎች በስተቀር ከምንትስ ምንትስ በዘለለ የሕዝብን ብሶትና ችግር በፈጠራ ሥራዎቻቸው የሚያካትቱ የሥነ ጥበብና የኪነ ጥበብ ሰዎች ቢኖሩን መታደል ነበር፡፡ በተሠሩ በጥቂት ቀናት ወይም ወራት ውስጥ የሚፍረከረኩ የመንግሥት ቤቶችንና መንገዶችን የሚገነቡ በሙስና የተበከሉና በዕኩይ ሥነ ምግባር የተዘፈቁ ሀሳዊ መሃንዲሶች ሀገር ምድሩን ባይሞሉት ኖሮ ትምህርት ዋጋውን እንዳላጣ እንረዳ ነበር፡፡ ዘርዝረን በማንጨርሳቸው አጠቃላይ ችግሮች ውስጥ ተነክረናል፡፡ የትምህርት ጥራት አይነሳ፤ ሁሉም ዜሮ እየሆነ ነው፡፡ ለኅሊናቸው የሚታዘዙ ሠራተኞች፣ መምህራን፣ ተማሪዎች፣ ወታደሮች፣ ባለሥልጣኖች፣ ነጋዴዎች፣ ዘፋኞች፣ ደራሲዎች፣ የሃይማኖት አገልጋዮች፣ዳኞች፣ ጠበቆች፣ ግምበኞች፣ ወዛደሮች፣ …. ጥቂት እንኳን ቢኖሩን ድቀታችን መልክ በኖረው ነበር፡፡ ይህ ሁሉ የሚያሳየን የተሣካ ውድቀት ውስጥ የመገኘታችንን የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ ይህችን ሀገር እንደገና ገምብቶ ሀገር ለማድረግ ምን ዓይነት ጥረትና ስንትና ስንት ልፋት እንደሚጠይቀን ፈጣ ብቻ ነው የሚያውቀው፡፡ ብዙ ነገሮች ብቻ ሣይሆኑ ከሞላ ጎደል ሁሉም ነገሮች ከደንቡና ከሥርዓቱ ወጥተው በቀላሉ የማንወጣው አዘቅት ውስጥ ገብተናል፡፡
አንዳንዶቻችንን ሊያስከፋን ይችል ይሆናል፡፡ ግን እውነት ስለሆነ እዚህ ላይ ሳንጠቅስ ልንዘለው አንችልም፡፡ ወያኔ በሀገራችን ያነገሠው ዘረኝነት ከቃላት የመግለጽ አቅም በላይ ነው፡፡ትግሬን ተጠቃሚ ለማስመሰልና ከሌላው ሕዝብ ጋር ለማቃረን በእግረ መንገድም በእርግጥም የዘረኛውን ሥርዓት የጎሣ ተዋፅዖ በማጉላት በሥርዓቱ  እምነት የሚጣልባቸውን ዜጎች ይበልጥ ለመጥቀም ሲባል እየታዬ ባለ የተንሻዋረረ ጎጠኛ አሠራር የማንታዘበው ጉድ የለም፡፡ ይህ እግዚኦ የሚያሰኝ ጉድ በማንም ሀገር በመቼም ዘመን አልታየም፡፡ የደቡብ አፍሪካው አፓርታይድም ይህን ያህል ግፍና በደል በጥቁሮች ላይ የፈጸመ አይመስለኝም፡፡ የኛ ዋና ችግርና ለአሣራችንም ቀጣይነት አስተዋፅዖ እያደረገ ያለው ክስተት የኛ ጨቋኞች በመልክና በቀለምም በባህልና በቋንቋም ከኛው ከተጨቋኞቹ ጋር በመመሳሰላቸው ጠላትን ከወዳጅ በቀላሉ መለየትና ዘረኛውን ከጤናማው ለይተን መተማመንን በመፍጠር ለነጻነት ትግሉ መትጋት አለመቻላችን ነው፡፡ አስቸጋሪ ነው ጓዶች፡፡ አንተን ከመሰለ ሰው ጋር ታግለህ ወደምትፈልገው ድል ለመብቃት ከባድና ጊዜንና ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚጠይቅ ነው፡፡ አንዱና ትልቁ ችግር ይህ ስለሆነ እንጂ እነዚህን አረሞች ለመንቀል የማይቻል ሆኖ አይደለም፡፡ ግን ደግነቱ ይህም ያልፋል፡፡ ቆሞ ያለ የሚመስለው ግን ይጠንቀቅ!
ለአሁኑ ግን የዘረኝነቱ ዳፋ በሀገርህ ላይ ተቀምጠህ ሀገርህ እስኪናፍቅህ ድረስ፣ በወገንህ መካከል እየኖርክ ወገን እንደሌለህ እስኪሰማህ ድረስ፣ የጋራ እናት ሀገር እያለህ ምንም ዓይነት ዜግነት የሌለህና ባለቤት የሌለለው የመንገድ ላይ ውሻ የሆንክ ያህል እስኪሰማህ ድረስ ውስጥህን ዘልቆ በሚበረብር የሀገርና የወገን ርሀብ ትሰቃያለህ፡፡ ይህም ማለፉ ባይቀርም ለጊዜው ጭንቅላትህን ሊያፈነዳ በሚችል ሥነ ልቦናዊና እንደዬሁኔታውም ኢኮኖሚያዊ ችግር ልትወጠር ትችላለህ – በዚህ ያበዱና ለማበድም የተዘጋጁ እጅግ ብዙ ዜጎች አሉ፡፡ በ“ሰው ሀገር” እየኖርክ መብትህን መጠየቅ እንደማትችል፣ ብትሞክር ደግሞ ቢያንስ እንደሚሳቅብህና እንደሚፌዝብህ ስትረዳ ሀዘንህ ዕጥፍ ድርብ ይሆናል፡፡ ኬንያ ወይም ሆኖሉሉና ፊጂ ብትኖር የማይጓደልብህ ሰብኣዊ መብት የገዛ ሀገሬ በምትላት ኢትዮጵያህ ውስጥ ወደህና ፈቅደህ ባልሆንከው የዘርህ ማንነት ምክንያት ሲዳላብህ ስታይ አለመፈጠርህን ትመርጣለህ፡፡ ይህች ሀገር፣ ሀገር ተብላ ነው እንግዲህ እነሌንጮ ገብተው በ‹ሰላማዊ መንገድ ሊታገሉና ሕዝብን ነጻ ሊያወጡ› እንደሆነ እየተወራ ያለው፡፡ ተስፋ ስትቆርጥ አንድም ትወጣለህ አንድም ትገባለህ ማለት ነው፡፡ እኔ ተስፋ ቆርጬ መውጣት ፈልጌ መውጫ አጥቼ ቀረሁ፡፡ እነሌንጮ ተስፋ ቆርጠው ወጥተው ተስፋ ቆርጠው ሊመለሱ ነው፡፡ አንዳንዱ ደግሞ ተስፋ ቆርጦ ይወጣና ተስፋን ሰንቆ ይገባል – እንደአውራምባው ዳዊት ከበደ ያለው፡፡ ይሄ ‹ተስፋ› እሚሉት ግን መልኩ ምን ይመስል ይሆን?
ገባ ብለን በተጨባጭ እንየው፡፡ ትግሬዎች አትቀየሙኝ፡፡ እኔም ዋናው ትግሬ ነኝ፡፡ ዘመኑ ሲያልፍ ትግሬያዊ ማንነቴን እገልጣለሁ – ሊያውም አስፈላጊ ከሆነ፡፡ ያ ግን በመሠረቱ  ምንም ማለት አይደለም፡፡ ቀዳሚው ሰውነት ነው፤ እናሳንሰው ካልን ደግሞ ኢትዮጵያዊነት፡፡ እነዚህ ሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎችም – በነገራችን ላይ – ወደው አይደለም እንዲህ የሆኑት(አማራጭ አጥተው በገቡበት የወንጀል ዓለም የሚደሰቱበት አይመስለኝም)፡፡ ወደ እውነት ቢመጡ ሥልጣኑን እንደሚያጡት ለአእምሯቸው ነግረው ስላሳመኑት ነው – በዚያም ላይ ከጥንት ጀምረው የሠሯቸው ብዙ መጥፎ ተግባራት ስላሉባቸው በነዚያ ላለመጠየቅ ዋናው አብነት ሥልጣንን አጠናክሮ እስከሕይወት ፍጻሜ ወንበርን የፊጥኝ ማለት መሆኑን ያውቃሉ – በዚህ ረገድ እነሱ ስህተት የለባቸውም፤ ችግሩ የኛ የተጨቋኞች ነው – እነሱን በጋራ ትግል ላለመጣል የተዋዋልነው ፊርማ የለሽ ስምምነት ነው እየጠቀማቸው የሚገኘው፡፡ ጥቂቶች(minorities) “ተወዳድረን ሥልጣን መያዝ አንችልም፤ ብቸኛ አማራጫችን ኃይልና ጉልበት ነው” ብለው ካመኑ በየትኛውም ሁኔታ አስቸጋሪ ናቸው – የማይነቃነቁ ዓለቶች ሆነው ለብዙ ጊዜ ሊያስቸግሩ ይችላሉ፤ በሂደት ግን እንደጤዛ መርገፋቸው እንደጉምም መብነናቸው አይቀርም፡፡ እስከዚያው ግን ይሞቷታል አንጂ ሥልጣንን በፈቃዳቸው አይለቁም – “ሰላማዊ ትግል” የሚሉት ቀልድም እነሱ ዘንድ ከጨዋታነት ባለፈ በፍጹም የማይሞከር ነው፡፡ እነዚህን መሰል ጨቋኞች ዓለም የሠራቻቸውን ወንጀሎችና ሸሮች ሁሉ እያከናወኑ በሥልጣናቸውና ሥልጣናቸው በሚሰጣቸው ጥቅም ላይ እንደመዥገር ተጣብቀው ይኖራሉ፡፡ እናም የእነዚህን መዥገሮች ድርጊት ስናገር መጥፎ ድርጊት በደምና በዘር አይተላለፍምና ጤነኞች ትግሬዎች መናደድ አይገባንም፡፡ እውነቱ ባጭሩ እንግዲህ ይህን ይመስላል፡፡
ከትግሬዎች በስተቀር ሌሎች ኢትዮጵያውያን ድርሽ የማይሉባቸው የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ብዙ ናቸው፡፡ ከነዚህ መካከል የደኅንነትና መከላከያን የመሳሰሉ የፀጥታ መሥሪያ ቤቶች፣ ጅምሩክንና ማዕድናት የመሳሰሉ ከፍተኛ ጥቅም አስገኚ ቦታዎች በዋናነት ይገኙበታል፡፡ እነዚህን የመሰሉት ቦታዎች ከትግሬ በስተቀር ለሌሎች ጥብቅ ምሥጢር ናቸው – አጮልቀው እንኳን እንዲያዩዋቸው የማይፈቀድ፡፡ የማንኛውም የመንግሥት መሥሪያ ቤት ከፍተኛ አመራር ሙሉ በሙሉ ማለት በሚያስችል ሁኔታ በትግሬዎች የተያዘ ነው – በስም ደግሞ አትመን (ወያኔ በስም የማታለልን ሸር የተካነበት ገና በረሃ ሳለ ነው- “ወርቅነህ በረደድ” ወይም “ደቻሣ ኩምሣ” ቢልህ እውነት አይምሰልህ – የዚህ ተጋዳላይ እውነተኛ ስም “ሐጎስ ግደይ” “ወዲ ዕንቋይ” ሊሆን ይችላል)፡፡ የትኛውንም የመንግሥት መሥሪያ ቤት አመራር ከላይ እስከታች ብንመለከት ሁሉም ትግሬ ነው፡፡ ውሸታም አትበሉኝ፡፡ እንዳልሆንኩ በተገቢ መረጃ አስደግፌ ልናገር ነው፡፡ ለምሳሌ የአንድ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ሚኒስትር እንደ ታሪካዊ ‹መጥፎ አጋጣሚ ሆኖ› ትግሬ አይደለም እንበል፡፡ ያ ሰው አማራ ነው እንበልና እንውሰድ – እዚህም ላይ ለሥርዓቱ ዕኩያንና ዕቡያን ትግሬዎች ይህ ክስተት እንደ ‹መጥፎ የታሪክ አጋጣሚ› ተቆጥሮ፡፡ አንተ አማራ ነህ ልበልህና ደስ አለህ አይደል አሁን? አዎ፣ ደስ ይበልህ እንጂ! “ወንድምህ” – ‹ዘርህ› – ተሾሞልህ ያልተደሰትህ መቼ ልትደሰት! ግን አይምሰልህ ወንድሜ፡፡ መሾምና መሻር በችሎታና በብቃት መሆኑን ዘንግተህና አንተም ወያኔ ሆነህ በደምና በአጥንት የምታመልክ ሰው ሆነህ ዘረኝነቱ ወዳንተም ተጋብቶ የኔ የምትለውን ሰው ሥልጣን ላይ ወጥቶ ያየኸው ከመሰለህና በዚያም ከተደሰትህ ተሳስተሃል ብቻ ሣይሆን ለወያኔው ወጥመድ ተመቻችተሃል እንደማለትም ነው፤ ያ ሚኒስትር የተቀመጠው ለስምና ለፖለቲካዊ ታይታ ብቻ ነው – ከግርጌውና ከራስጌው ታኮና ትራስ ሆኖ በዐይን ጥቅሻና በስልክ የሚያንቆራጥጠው ትግሬ አለ – ለዚህ ነው ሁሉም አዛዥ ናዛዥ ትግሬ ነው የምልህ፤ ለዚህ ነው የሀገሪቱ እስትንፋስ መቶ በመቶ በትግሬዎች ቁጥጥር ሥር መሆኑን በድፍረት የማረዳህ ማለትም የማስረዳህ – አንድም ቦታ ሳይቀር ሁሉም በነሱ እይታና ቁጥጥር ውስጥ ነው፤ ያ ቦታ ከመንግሥት ኅልውና ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ይኑረው አይኑረው ለነሱ ምንም ማለት አይደለም፡፡ የቆሻሻ ገንዳም ይሁን መጸዳጃ ቤት ጥበቃ፣ ስፖርት ኮሚሽንም ይሁን  የዱር እንስሳት ጥበቃ ብቻ በአለቅነት ወይም በስለላ መልክ የሌሎች ወንድሞቹን እንቅስቃሴ የሚከታተል የሥርዓቱ ታማኝ እስከተቻለ ትግሬ አለዚያም የወያኔነት ሶፍትዌር የተገጠመለት ሌላ ሆድአደር ይመደባል፡፡ ለታይታ ከላይ የሚቀመጥ የሌላ ብሔር “ባለሥልጣን” ግን አሻንጉሊት ጉልቻ እንጂ ከራሱ አእምሮ አንቅቶ የሥልጣን ወንበሩ የሚፈቅድለትን ተግባራት ሊያከናውን የሚያስችል ቅንጣት የማዘዝ ሥልጣን የለውም ለዚህ ለዚህማ ጠቅላይ ሚኒስትርስ ከወላይታ ተሾሞልህ የለም እንዴ? ቲያትሩን እያስታወስኩህ እንጂ አዲስ ነገር እየነገርኩህ እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡ የምነግርህን ነገር ደግሞ ለራሴው ተግባራዊ ግንዛቤ ስል ራሴው በየመሥሪያ ቤቱ እየዞርኩ የተረዳሁት ነው፡፡ ያልሄድኩበት ቦታ የለም፡፡ ከብዙ ገጠመኞቼ አንድ ሁለቱን ያህል ብቻ ለአብነት እዚህ ላይ ልንገርህ፡፡ ወደጦር ኃይሎች ሆስፒታል ባለፈው ሰሞን ሄድኩ – አንድ ዘመድ ለማሳከም፡፡ ህክምናው አነስተኛ ቀዶ ህክምና ነበር፡፡ ዘመዴን ለማከም የቀረቡት ዶክተሩም ነርሶቹም ዕቃ አቀራራቢዎቹም  አራቱም ትግሬዎች ናቸው፡፡ በዚህ ብቻ አይግረምህ፡፡ የከሰዓት ተቀያሪዎቹም ሦስቱም ትግሬዎች ናቸው፡፡ በሆስፒታሉ ተዘዋወርኩ፡፡ ከጥቂቶች በስተቀር ሁሉም የአስተዳደርና የህክምና ሠራተኞች ትግሬዎች ናቸው – የግቢው ብሔራዊ ቋንቋም ትግርኛ ነው – በዚህስ አልከፋኝም፡፡ ይህ ሁኔታ በአጋጣሚ ነው ከተባለ በትንሹ ሞኝነት ወይንም “አጋጣሚ” የሚለውን ቃል ካለመረዳት የሚመነጭ የዋህነት ነው፡፡ አንድ ወቅት አንድ ወታደራዊ ሰርቪስ መኪና ውስጥ በአጋጣሚ ተገኝቼ እንደታዘብኩት ከነበሩት አሥራ ምናምን ሰዎች ውስጥ ትግርኛ የማይናገረው ሾፌራችን ብቻ ነበር፡፡ እንዴ፣ እውነቱን እንነጋገር ካልንማ ጉዳችን ብዙ እኮ ነው፤ ለምን እንተፋፈራለን? ባይሆን እናውራውና ይውጣልን እንጂ፡፡
ወደ መንግሥት ባንኮችና ኢንሹራንሶች ሄድኩ፤ ወደ አየር መንገድ ሄድኩ፤ ወደ ዩኒቨርስቲዎችም ሄድኩ፡፡ ሁሉም በትግሬ ተጥለቅልቋል፡፡ የከተማዋ ጠረን ከዳር እዳር ወደትግሬነት ተለውጧል – ምናልባትም ‹መቐለ› ላይ ያለህ ሊመስልህ ቢችል አይፈረድብህም፡፡ አነጋገሬ ዘና ያለ እንዲሆን ያደረግሁት ሆን ብዬ ነውና ብዙም አይሰማችሁ፡፡ እናም ብዙ ቦታዎች ሄድኩ – ያው ነው፡፡ ሰዎች “ይህ ዘመን የትግሬዎች ብቻ ሆኗል” የሚሉትን ሃሜት ሊያስተባብልልኝ የሚችል አንዳች ነገር ባገኝ ብዬ ተመኘሁ፡፡ ነገር ግን አልተሳካልኝም፡፡ ትግሬ በአንዳች ምትሃታዊ ነገር እየተባዛ መላዋን የወያኔ ኢትዮጵያ በምልዓት ያዳረሳት ይህል ተሰማኝ – ማዳረሱ ለበጎ ነው ችግሬ የመድሎና የጥፋት ኃይል መሆኑ ላይ ብቻ ነው፤ ሌላውን ሕዝብ ምን በላው እስክትሉ ድረስ በትግሬዎች የመንግሥትን መሥሪያ ቤቶች በበላይነት መቆጣጠር ትገረማላችሁ – ትግሬ ስልህ ደግሞ በአባቱ ወይ በእናቱ ሊሆን ይችላል – እንዲያውም ትግርኛ የማያውቅና የማይናገርም ትግሬ ልታገኝ ትችላለህ – መሃል አገር የተወለደና ያደገ፡፡ “ትንሽ ሥጋ እንደመርፌ ትወጋ” የምትለዋ ብሂል በወያኔ ዘንድ ትልቅ ዋጋ አላት፤ ሌላውን ስለማያምኑ በተለይ ሹመት ላይ የሚያስቀምጡት ሰው ከነሱ ቁጥጥርና አመኔታ የማይወጣ እንዲሆን ይጠነቀቃሉ፡፡ አሁንም አንድ ነገር ግልጥ ላድርግ – ሌሎች ዜጎች በኃላፊነትም ሆነ በተራ ሠራተኛነት አይቀጠሩም ወይም የሉም ማለቴ አይደለም፤ እያልኩ ያለሁት ትርጉም ባለውና ወሳኝ በሆነ ደረጃ ፈላጭ ቆራጮቹ ትግሬዎች ናቸው ነው፡፡ ለምሳሌ በአንድ መሥሪያ ቤት ውስጥ ከመቶ ሠራተኞች መካከል አምስቱ ብቻ ትግሬዎች ቢሆኑ ዘጠና አምስቱ ሠራተኞች የሚሽቆጠቆጡትና የሚያሸረግዱት ለአምስቱ ትግሬዎች ነው – ከመስቀያው ነው – በጌታዋ የተማመነች ፍየል እኮ ቀንዷን በጎች መሃል ነው የምትሰካ፤ በዚህ ዓይነቱ አጋጣሚ ደግሞ እኛ ኢትዮጵያውያን ያለንን የማሸርገድ ብቃትና ለተሹዋሚ የማጎብደድ ተፈጥሯዊ ዝንባሌ መረዳት ይቻላል፡፡ ጊዜ ዘምበል ሲል ደግሞ እንዴት የመሰለ አክሮባት እንደምናሳይ ወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡
በበኩሌ በትግሬ ሁሉንም የሥልጣን ቦታዎች መቆጣጠር ብዙም አልከፋም፡፡ የሚያስከፋኝ ባለሥልጣናቱ ቦታውን የሚያገኙት በችሎታና በትምህርት ሳይሆን በዘር ቁርኝት በመሆኑና ያም ሥራን ክፉኛ እያበላሸ በመሆኑ ነው፡፡ አለበለዚያ ሥራውን በሚችሉ የተማሩ ትግሬዎች ሁሉም ቦታ ቢያዝ ግዴለኝም፡፡ አሁን ያለው ችግር ግን አይነሳ፡፡ አንድም ትምህርት የሌለው ምናልባትም የሁለተኛና የአሥረኛ ክፍል ወያኔ ትልቅ ቢሮ ይይዝና የተማረው የሌላ ጎሣ አባል በሥሩ ሆኖ ከኅሊናው ባፈነገጠ አሠራር በዚህ ማይም ወያኔ እየተረገጠ ስታዩ የሥራው መበላሸት ብቻ ሣይሆን ዘረኝነት አንዲትን ሀገር በምን ዓይነት ደረጃ ድራሹዋን እያጠፋት እንደሆነ በመገንዘብ ታዝናላችሁ፡፡ ትግሬ መሆን ብቻውን ለሥልጣንና ለሀብት ካበቃ፣ አማራ መሆን ብቻውን ጉራን ለመቸርቸርና በትምክህት ለመወጠር ካበቃ፣ ጠምባሮ መሆን ብቻውን ለንቀትና ለተዋራጅ ኑሮ ከዳረገ … ሰብኣዊነትና የጋራ ብሄራዊ ማንነት አዲዮስ! በኢትዮጵያ እየታዘብን ያለነው ጉደኛ ትንግርት ዓይነቱ ብዙ ነው፡፡ ባለፉት 23 ዓመታት የጠፋውን ጥፋት ለማረም ስንት ዓመት እንደሚፈጅ ፈጣሪ ብቻ ነው የሚያውቀው፡፡ በማይማን የተሞላውን በቅርጽ ያለ የሚመስል በይዘት ግን ደብዛው የጠፋውን የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሰው ኃይል አደረጃጀት ለማስተካከል ራሱ ከሩብ ምዕተ ዓመት ያላነሰ ጊዜን መውሰዱ አይቀርም፡፡ የተማረ የሲቪል ሰርቪስ ሠራተኛ ለማግኘት፣ በሥነ ምግባር የታነጸና  የሥራ ተነሳሽነት ያለው ዜጋ ለማፍራት ብዙ ጥረት ይጠይቃል፡፡ በአሁኑ ወቅት ለእስታቲክሳዊ ፍጆታ ካልሆነ በስተቀር የመንግሥት ሥራ በአግባቡ ይሠራል ማለት አንችልም፡፡ ከሞላ ጎደል ሁሉም የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ሕይወት ያላቸው የሚመስሉት እዚህና እዚያ በለጣጠፏቸው የማይተገበሩ መፈክሮችና “ራዕይ፣ ዓላማ፣ ተልዕኮ፣…” በሚባሉ ትላልቅ የወረቀት ጀንዲዎች ላይ በጉልህ በተቀመጡ የሚያማምሩ ጽሑፎች አማካይነት ብቻ ነው፡፡ በተረፈ የዚህና የዚያ የሥራ ሂደት ባለቤት እየተባለ በሥሩም ዕውቀትና በቂ ሥልጠና የሌለው ሠራተኛ በዘመድና በፖለቲካ አመለካከቱ እየተመደበ አለተጨባጭ ሥራ ስላውደለደለና ሕዝብን በጉቦ ስላስለቀሰ ሀገር ትለማለች ብሎ መጠበቅ የሚቻል አይደለም፡፡ አዲስ የሚቋቋሙት መሥሪያ ቤቶችም በአብዛኛው የሥርዓቱን ቀጣይነት ለማረጋገጥ የሚጠቅሙ የሀገር ሀብት አባባካኝ እንጂ ለሕዝብና ለሀገር ዕድገት የሚውሉ አይደሉም፡፡ ገመናችን ብዙ ነው፡፡
ንግዱን ያየን እንደሆነ አነስተኛና ጥቃቅን ከሚባሉት የሥርዓቱ ዕንባ ጠባቂዎች ጀምሮ የአንበሳውን ድርሻ ይዘው ያሉት ወያኔዎች ናቸው – ከአዲስ አበባ የንግድ ማዕከላትና ሱቆች ውስጥ፣ በአዲስ አበባ አስፋልት ከሚሽከረከሩ ዘመናዊ አውቶሞቢሎች ውስጥ፣ በየምሽቱ ዳንኪራ ከሚረግጡ ዜጎች ውስጥ፣ በየሉካንዳውና በየመጠጥ ቤቱ በጮማና ዊስኪ ከሚቀማጠሉ ‹ኢትዮጵያውያን› ውስጥ ስንቱ መቶኛ ኢ-ትግሬ ሊሆን እንደሚችል ገምቶ መናገሩ ሆድ ሊያስብስ ስለሚችል ሆድ በሆድ ይፍጀው ይቀመጥ፡፡ (እዚህ ላይ ቅድም በኢሳት የተከታተልኩት አንድ ቃለ መጠይቅ ትዝ አለኝ፡- አሥራት አብርሃም የተባለ ሰሜነኛ ከግዛው ጋር ሲነጋገር እንደሰማሁት የኢትዮጵያ ችግር እርሱና መሰል አመለካከተኞች እንደሚሉት የንግሥናው ነገር ከሸዋ ወደ ትግራይ ወይም ከትግራይ ወደሸዋ የመምጣት ጉዳይ አይደለም፡፡ እንደዚያ ያለው ንትርክ ጉንጭ አልፋ የሽፋን ተኩስ ዓይነት ነው፡፡ ዋናው ትግሬ ነገሠ ወይም አማራ ተሻረ የሚለው ሳይሆን የኅልውና ጉዳይ ነው፡፡ ትግሬና አማራ በሥልጣን መፈራረቃቸው እንግዳ ነገር አይደለም፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ወያኔ ባመጣው የዘር በሽታ መነደፉና በግፍ አገዛዝ ክፉኛ መሰቃየቱ ግን በታሪካችን ታይቶ የማይታወቅ እንግዳ ነገር ነው፡፡ ስለዚህ ችግሩን እስከዚህ አታሳንሱት – አታውርዱት፤ ችግራችን ከነገሥታት ምርጫ ጋር ፈጽሞውን የሚያያዝ አይደለም – ከጭቆና መግረር ጋር እንጂ፡፡ በከፊል አማራ ያልነበረው መንግሥቱ 17 ዓመታትን በገዛ ጊዜ የዘር ችግር እንዳሁኑ በፈጠጠ ሁኔታ አልነበረም፤ ሕዝቡም ‹ኦሮሞ ገዛን፤ የሸዋ አማራ ይሁንልን!› ብሎ አልጮኸም፡፡ አማራው መልካም ገዢ ካገኘ ሥልጣን ቀረብኝ ብሎ አካኪ ዘራፍ የሚል አይመስለኝም – ትግሬም ሆነ ሌላውም ሕዝብ እንዲሁ፡፡ ይቺ ማምታቻ ናት፡፡ እዬዬም ሲዳላ ነው ወገኖቼ፡፡ ጥድቁ ቀርቶብኝ አሉ …)
ትግሬ ሆኖ ፖለቲካን ከጠላ ወደንግዱ መግባትና ለሌሎች በተዘጋጋ ለርሱ ግን በተመቻቸ የጨዋታ ሜዳ “በመነገድ” በአንድ አዳር ሊከብር ይችላል፡፡ ንክኪ ከሆንክ አንድም ሳንካ ሳይገጥምህ የሀብት መንገድህ ሁሉ አልጋ በአልጋ ይሆንልሃል፡፡ ሌላ ከሆንክ ግን ሁሉም ይከረቸምብህና ብቸኛ አማራጭህ ስደትና ድህነት ይሆናል፡፡ አንዲት እህቴ አንድ ንግድ ትጀምራለች፡፡ ሰዎቹ ይመጡባትና እርሷ በወር የተጣራ ሁለት ሺህ ለማታገኝበት ንግድ በዓመት 62 ሺህ ብር ግብር ክፈይ ይሏታል – ወያኔ ጋ ማሰብ ብሎ ነገር የለም፡፡ በግልጽ ሂድ ላይሉህ ይችላሉ – እንድትሄድ ግን ያደርጉሃል፤ ውጣ አይሉህም እንድትወጣ ግን ያስገድዱሃል፡፡ ያቺ ዘመዴ ምን ከምን ታምጣና ትክፈል?  ኪሣራዋን ተከናንባ የባሏን እጅ እያየች ተቀምጣለች፡፡ አንተን በእነሱነት ከጠረጠሩህ ምንም ምክንያት ሳያስፈልጋቸው እንዳትኖር ማድረግ ይችላሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ከንግድ ውጪ እያስወጡ ሙልጭ ድሃ ያደረጓቸውን ወገኖቻችንን ቤቱ ይቁጠራቸው፡፡ የምትሠራበት ቤት የመንግሥት ከሆነ ለነሱ አሸወይና ነው – ኪራይና ግብር ይቆልሉብህና ተማርረህ በራስህ ጊዜ ውልቅ ብለህ እንድትወጣ ያደርጉሃል፤ በማግሥቱ በጥንቱ አነስተኛ ኪራይና በዝቅተኛ የፍሬ ግብር ግምት የነሱን ሰው ያስገቡበታል፤ ስንትና ስንት የትግሬዎች ሱቅና ትላልቅ ንግድ ቤት በግልጽ ካለቫት ሲሸጡ እያየህ ባጠገባቸው የምትገኝ ሚጢጢዬ የሌላ ሰው ሱቅ ግን ካለቫት ስትሸጥ ብትገኝ አሣር ሲገጥማት ታያለህ – እነሱን ማንም አይቆጣጠራቸውም፤ በአንዲት ሀገር ውስጥ ብዙ ዓይነት ዜጎችና ሁለት መንግሥታት በግልጽ የሚታዩት ኢትዮጵያ ውስጥ መሆኑን ስትገነዘብ በደረስንበት የዝቅጠት ደረጃ ታርር ትደብናለህ – ግን እውነትም ሰዎች ስንባል ከእንስሳትም የወረድን ምን ያህል ከንቱዎች ነን? የሚሠራውን ግፍ ስትሰማ ይሰቀጥጥሃል፡፡
ባለኝ መረጃ መሠረት በውድ ትምህርት ቤቶች ከሚማሩ ተማሪዎች መካከል ከ95 በመቶ በላይ የነሱ ልጆች ናቸው፤ ሌላው መንደር ያውደለድላል ወይም እንደሚፈጭ ጥሬ ጎዳና ላይ ተሰጥቶ ይውላል፡፡ የመንግሥት ት/ቤት ተብዬዎቹ ውሎ መግቢያ እንጂ ትክክለኛው የመማር -ማስተማር ሂደት የሚካሄድባቸው አይደሉም፡፡ በየቦታው የሚገነቡ ሕንጻዎችና የንግድ ተቋማት የነሱው እንደሆኑ ሁሉም ይናገራል፡፡ ከነሱ ውጪ ሌላው ነግዶም ሆነ ሠርቶ መብላት እንዳይችል በህግ የተገደበ ይመስላል፡፡ ለነገሩ ህግ የሚባል ነገር የለም፤ ሀገሪቱ በኳስ አበደች ዓይነት ጰራቅሊጦሳዊ ያልተለመደ የጉሽ ጠላ ስካር ውስጥ ትገኛለች፡፡ ለምሳሌ አትቀደም እንጂ ሰው ቢገድልህ ተከታትሎ በደለኛን ወደህግ የሚያቀርብ አካል ለማግኘት ትቸገራለህ፤ በኪነ ጥበቡ ይነጋል፤ ይመሻልም፡፡ የሙስናው ነገርም የጉድ ነው፡፡ በፖለቲካ አይሁን እንጂ ወንጀለኛን ወይም በሕግ ሥር የሚገኝን ሰው ለማስፈታት ጉቦ ከከፈልክ ባደረበት ወይም በዋለበት ማረፊያ ቤት አይውልም ወይም አያድርም ፡፡ ከሚነዳው የሕዝብ ትራንስፖርት መኪና አንድ ሰው በር ከፍቶ ዘልሎ ሲወርድ በመሞቱ ምክንያት የተከሰሰ አንድ ሾፌር ፍርድ ቤት በነጻ ካሰናበተው በኋላ ፖሊሶች አሥረው 17 ሺህ ብር ገደማ በሚስቱ በኩል አስመጥተው እንደተከፋፈሉ የሰማሁት በቅርቡ ነው፡፡ ሀገርህ ያለች ትመስላለች እንጂ በቁሟ ሞታልሃለች፡፡ ህግ ወደ ተራ ነገርነት ተለውጦ የምንተዳደረው በጉልበትና በሙስና ብቻ ሆኗል፡፡  በደሞዝ መተዳደር ስለማይቻልና ስለቀረም በሙስና የማይሠራ ነገር የለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንኳን ብትሄድ ጥሩ የመቃብር ቦታ ለማግኘት፣ ረጂም የጸሎት ፍትሀት ለማግኘት፣ የሰበካ ጉባኤ አገልግሎት ለማግኘት፣ የልደት ሠርቲፊኬት ለማግኘት፣ አገልጋይ ከሆንክ ደህና ገቢ ወዳለው ደብር ለመዛወር፣ የድቁና ወይም የቅስና ማዕረግ ለማግኘት፣ በጠያፍ ድርጊት የክህነት ሥልጣንን ላለማጣት፣በቄሰ ገበዝነት ጥሩ ቦታ ለመሾም/ለመመደብ… ካለጉቦ አይሞከርም፡፡ ውድቀት ከዚህ በላይ ካለ እኔ አላውቅም፡፡  ሥርዓቱ የሞሰነ (የጠፋ) ስለሆነ የዚህ ሁሉ ጥፋት እስፖንሰሩ ወያኔ ነው፡፡ (በአንዲት ጨዋታ ለምን ፈገግ አላሰኛችሁም – አንድ ሦስት የሚሆኑ ሙስሊም ጓደኛሞች ሶላት ላይ ናቸው፡፡ አንድ በቅርባቸው የነበረ ሌላ ሙስሊም ሣንቲሞችን በብዛት ከኪሱ ያወጣና እየሰገዱ እንዳሉ ሆጨጭ አድርጎ አጠገባቸው ይበትናል፡፡ በተንቃጨለው የሣንቲም ድምፅ ሰጋጆቹ ከስግደቱ ተናጥበው ወደተንቃጨለበት ሥፍራ ሁሉም በአንዴ በደመ ነፍስ ዘወር ይላሉ፡፡ ያኔ ያ ተንኮለኛ ሰውዬ “ይህንን ዱኣ እንኳን አላህ እኔም አልቀበለውም” አላቸው ይባላል፡፡ ለምን ትዝ አለኝ ግን?አዎ፣ ልብንና ኩላሊትን የሚመረምር የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ሞኝ የሚመስለን የሃይማኖት ሰዎች እጅግ ብዙ ነን፡፡ እርሱንና የርሱን እየረሳን ወደ ዓለም ብንጠፋና ከወንበዴዎች ጋር ብንወግን የወንበዴዎቹን የመጨረሻ ዕጣ እንጋራለን፡፡)
ትግሬዎች ተሳስተዋል፤ “የትኞቹ ትግሬዎች?    “ በሚል ፀጉር አንሰንጥቅ፡፡ ኩይሃ ወይም እንደርታ ገጠር ውስጥ በላቡ አፈር እየገፋ የሚኖር ገበሬ መቼም ተሳስተሃል ልል አልችልም፡፡ ስለዚህ የተሳሳቱት ትግሬዎች ሕወሓትን አምልከውና አምነው ኢትዮጵያን ለማውደም ታጥቀው የተነሱትን እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህኞቹ ትግሬዎች ይህን ያህል ገሃድ የወጣ ዘረኝነት ውስጥ መግባት አልነበረባቸውም፡፡ መሪዎች ሊሳሳቱ ይችላሉ፡፡ ተራዎቹ ዜጎች ግን ከትዝብት በሚያልፍ እስከዚህ ደረጃ ጭልጥ ብለው ወርደው በተሳሳቱ መሪዎች የጥፋት ጎዳና መትመም አይጠበቅባቸውም ነበር፡፡ ምክንያቱም “ነገ” የሚባል ጦሰኛ ቃል አለ፡፡ የትናንትን ታሪክ ማንበብ ያሰኘኝ – ቀደም ብዬ እንደተናገርኩት – ዛሬን ከትናንትና ትናንትንም ከዛሬና ከነገ ጋር በማስተያየት መጪው ጊዜ ምን ሊሆን እንደሚችል በመገመት ለመተንበይ ነው፡፡ እንደዚያም ይቻላል፡፡ እናም እተነብያለሁ -  ነገ ለትግሬዎች ክፉ ቀን ይሆናል፡፡ አሁን ላይ ሆኜ እንደሚታየኝ የእኔን መሰል ደጋግ ትግሬዎች ሸክም ከባድ ነው፡፡ በትግሬነቴ ብዙ መሥራት የሚገባኝ አሁንና ለወደፊትም ብዙ የሥራ ጫና እንዳለብኝ ይሰማኛል፡፡ በወንድሞቼና በእህቶቼ ተላላነት ምክንያት እየሆነ ባለው ነገር ሁሉ አዝናለሁ፤ ማዘን ብቻውን ግን የታሪክን ቅጣት እንደማያስቀር እረዳለሁ፡፡ እናም በትግሬነቴ  ሸክሜ ብዙና የሚያጎብጥም መሆኑን የምገነዘበው ከዚህ አኳያ ነው፡፡ ዶክተር ኃይሉ አርአያ፣ አብርሃ በላይ፣ ኤልያስ ክፍሌ፣ አብረሃም ደስታ፣ አስገደ ገ/ሥላሴ፣ ፀጋዬ ገብረ መድኅን፣ ጌታቸው ረዳ(የኢትዮሰማይ ድረገጽ አዘጋጅ)፣ … እና ሌሎችም ጥቂት የማይባሉ ብርቅዬ ትግሬዎች እየደከሙ ያሉት ሦስተኛውን ዐይናቸውን ፈጣሪ ስለከፈተላቸውና የነገን የፈጣሪና የታሪክ ፍርድ ከወዲሁ በማወቃቸው እንጂ እንደትግሬነታቸው ቢሆን ውጪ ያሉት ወደሲዖሊቱ  ኢትዮጵያ በመግባት ቢፈልጉ ሚኒስትር ቢፈልጉ የናጠጠ ነጋዴ ሆነው በደናቁርት ወንድሞቻችን አገዛዝ ሥር ሥጋቸውን በምቾት ሊያኖሩ በቻሉ ነበር፡፡ ግን ግን “ከሰው መርጦ ለሹመት፣ ከእንጨት መርጦ ለታቦት” እንዲሉ ነውና እነዚህ በሁለት እሳት ውስጥ ሆነው እየተለበለቡ የሚገኙ ትግሬ ወገኖቻችን ሁሉንም እንዳመጣጡ እንዲቋቋሙ ፈጣሪ ትግስቱንና ችሎታውን ሰጥቷቸው ኢትዮጵያ የሁሉም ዜጎቿ እኩል ሀገር እንድትሆን እየተደረገ ባለው ሁለንተናዊ ትግል የበኩላቸውንና አቅማቸው የፈቀደላቸውን ያህል በመታገል ላይ ይገኛሉ፡፡ እግዚአብሔር ከነሱም ጋር ይሁን፡፡
የወደፊቱ ጊዜ ከአማራነት ስሜት፣ ከትግሬነት ስሜት፣ ከኦሮሞነት ስሜት፣ … በጥቅሉ ከጎጠኝነት ስሜት በአፋጣኝ መውጣት የሚጠበቅብንና የምንገደድበትም ጊዜ ነው፡፡ በተመሳሳይ የቂሎች ዘፈን ነጋሪት እየደለቅን በከንቱ የምንጠፋፋበት ዘመን ማብቂያው ላይ የደረሰ ይመስለኛል፡፡ ለዚህ አስከፊ አደጋ ያጋለጡን ብዙ ታሪካዊ አጋጣሚዎች መኖራቸው እውነት ቢሆንም የአሁኑ ትውልድ ከአንጋፋዎቹ ንዝህላልነት ብዙ የሚማርና የራሱን መፃኢ ዕድል የተቃና እንዲሆን ጥረት የሚያደርግ ይመስለኛል፡፡ በተቆፈረለት ጉድጓድ እየገባ ለማለቅ የቆረጠው ትውልድ በሂደት ለአዲሱ ትውልድ ሥፍራውን እየለቀቀ ይሄድና ወደመላው ዓለም የተበተነው ሥልጡኑ ኢትዮጵያዊ በአዲስ የአብሮነት ስሜት አዲሲቷን ኢትዮጵያ ገንብቶ እያንገሸገሸው ካለው የስደት ኑሮ ሊገላገል የወሰነ ይመስለኛል፡፡ አሮጌው ትውልድ ከነተንኮሉና ከነከፋፋይ ቅራቅንቦው ወደታሪክ መዝገብነት የሚከተት ይመስለኛል፡፡ በዘር መሳሳብና በአንድ ቅጽበት የናጠጠ ከበር የሚኮንት ጊዜ ተወግዶ በወዝና በላብ ተሠርቶ የሚከበርባት ኢትዮጵያ ልትፈጠር ዳርዳርታው የተጀመረ ይመስለኛል፡፡ (የአንድ ባለሥልጣን የዘመድ ልጅ አሠራ ሁለተኛ ክፍል እምቢዬው ይለዋል፡፡ በአንዲት ቀጭን ደብዳ ከሞሰበ ስሚንቶ በዱቤ ስሚንቶ እንዲወስድ ይደረጋል፡፡ ወዲያውኑ ያን ስሚንቶ ሸጦ ከወጪ ቀሪ 4 ነጥብ ምናምን ሚሊዮን ብር በከፈተው የባንክ አካውን ውስጥ ዘጭ ይልለታል – በድንጋጤ አለመሞቱ እሱው ሆኖ ነው – በአሁኑ ሰዓት ቢጠሩት የማይሰማ የልጅ ቱጃር ነው፤ እሱን መሰሎች ደግሞ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ አሉ፡፡ እኔ ብሆን በደስታ ብዛት ሞቻለሁ፡፡ እኛ እንዲህ ነን፡፡ ወያኔ እንዲህ ነው፡፡ በአንድ ሌሊት ወገኑን ማክበርና በአንድ ሌሊት ተመሳሳይ ደግሞ የሚጠላውን ወደ አሰቃቂ ድህነት በማውረድ ማማቀቅ የሚችል ሕወሓት ብቻ ነው፡፡)
የሸዋ አማራ ለቀብራራው ጎንደሬ እንደባሪያ የሚቆጠርበት ዘመን ነበር፤ አማራነት እንደ ልዩ ትምክህት እየተቆጠረ በባዶው የሚኮፈሱበት፣ ከባዶ እግር ሳይወጡና ትከሻ ላይ ያለቀን መርዶፋና አቡጄዲ ሳይቀይሩ እንዲሁ በከንቱ በዘር የትውልድ ሐረግ የሚኩራሩበት ዘመን ነበር፡፡ በአማራነት ሥራ መያዝ ወይም አለመያዝ፣ በትግሬነት ሥራ መያዝ ወይም አለመያዝ፣ በኦሮሞነት ሥራ መያዝ ወይም መልቀቅ የገሃዱ እውነታ አሳዛኝ ነፀብራቅ ነበር፤ አሁንም በባሰ ደረጃ እንደቀጠለ ነው፡፡ ደረጃው ይለያይ እንጂ የአሁን ጥፋቶች አሁን አልተጀመሩም ቢባል ማጋነን አይደለም፡፡ እውነትን እንዳለ መቀበል የንስሃ መጀመሪያና የፅድቅ መንገድ ስንቅ ነው፡፡ የነበሩን ችግሮች ናቸው ግዘፍ ነስተው ኅልውናችንን እስከመፈታተን የደረሱት፡፡ ወያኔ የጀመረው ጥፋት የለም፤ ግን አራቀቀና ጫፍ አደረሳቸው፡፡ ስህተትን ወርሶ በዐዋጅ ማፅደቅና የመንግሥት መለያ ማድረግ የወያኔ ተፈጥሮ ሆነ እንጂ ቀድሞም ስህተቶች ነበሩብን፤ አልነበሩብንም ማለት ሞኝነት ይመስለኛል፡፡ የአሁኑ ትውልድ ግን ከራሱ ታሪክና ከየሚሰደድበት ሕዝብ ብዙ እየተማረ የወደፊት ሕይወቱን አስተካክሎ በዘልማድ ሳታጣ ያጣች የምትባለዋን ሀገሩን በቁጭትና በእልህ በጋራ ለመገንባትና በፍቅርና በመተሳሰብ ለመኖር የሚረባረብ ይመስለኛል – ነገ፡፡ ምን እስክንሆን እንጠብቃለን? በዓለም ፊት ከዕቃነት ከመቆጠር የበለጠ ምን ሊደርስብን ይችላል? ከአሁን ዘመን በበለጠ ብሔራዊ ክብራችን የተዋረደበት ዘመን የለም፡፡ እናም ሁሉም ነገር እንደሚፀነስና እንደሚወለድም፣ እንደሚያድግና አርጅቶም እንደሚሞት በወያኔ አድጎና ጎምርቶ ለአካለ መጠን የደረሰው የብሔራዊ ክብራችን ውድቀትና የጋራ ማንነታችን መደብዘዝ አሁን በማርጀቱ የማይቀርለትን ሞት እየሞተና በአንጻሩ የወደቀው ክብራችን ትንሣኤውን የሚቀዳጅበት ብሩኅ ዘመን እየመጣ ይመስለኛል፡፡ ብዙ እውን ሊሆኑ የሚችሉ የሚመስሉኝ ነገሮች እየታዩኝ ስለሆነ ወያኔዎች በተስፋ መቁረጥ አትውቀሱኝ፡፡ በል በል የሚለኝ አንዳች ነገር ስላለ ነው እንጂ እናንተን ለማስቀየም ፈልጌ አይደለም፡፡
ወደነማን እናንጋጥ? መሲሆቻችን እነማን ናቸው? ወጣቱ ምን ከነማን ይማር?
እመለስባቸዋለሁ ወዳልኳቸው ሁለት ነገሮች ልመለስ፡፡ ሰው በጠፋበት ዘመን አንዲት ሴት ልጅ ከርቸሌ ውስጥ ተገኘች፡፡ ይህች ልጅ ርዕዮት ዓለሙ ናት፡፡ አንድ የዐረብ ሀገር ተረት ባማርኛ ላስታውሳችሁ፡፡ “እከክ የሰጠ ጥፍር አይነሳም፡፡” ተፈጥሮም እግዜርም አንድ ተመሳሳይ ሕግ ያላቸው ይመስላል፡፡ በጨለማ ውስጥ ብርሃን እንዲጸነስ ያደርጋሉ፤ በብርሃንም ውስጥ ጨለማ፡፡ እነዚህ ነገሮች እየተፈራረቁ የሕይወትን ምንነት በአሉታዊና በአወንታዊ መልኮች ጎልተው እንዲታዩ ያደርጋሉ – አንዴ ይነጋል፤ አንዴ ይጨልማል፡፡ ምናልባት ባይነጋና ባይጨልም ኖሮ ማን ያውቃል ሕይወት ትርጉም አልባ ልትሆን ትችል ነበር፡፡ ስለዚህም ይመስላል እልም ባለ የተስፋ መቁረጥ ዘመን ውስጥ ተስፋን የሚያጭሩ ጥቂት ዜጎች ከወደቀው ትውልድ ውስጥ ብቅ የሚሉት፡፡ ስለዚህም ይመስላል ቆመናል የሚሉት በወደቁበት ሰዓት ከታናናሾች መካከል ታላላቆች የሚነሱትና የአርአያነትን መቅረዝ ከፍ አድርገው ይዘው እንደመጥምቁ ዮሐንስ በምድረ በዳ የነጻነትን ፋና የሚያበሩት፡፡ ስለዚህም ይመስላል ብዙዎች ወድቀው እንደዓሣማ የገማ ጭቃ ውስጥ ሲርመጠመጡ ጥቂቶች የኅሊናቸውን ጥሪ ተቀብለው በአካላዊ ስቃይ ለሚገኝ መንፈሣዊ ሃሴት የሚተጉትና ታሪካቸውን በወርቃማ ቀለም የሚጽፉት፡፡ ሕይወት ታላቅ ዩኒቨርስቲ ናት፤ ብዙ አየን -  እያየንም ነው፡፡
ርዕዮት እግዚአብሔርና አላህ የሰጡን የኢትዮጵያ ዕንቁ ልጅ ናት፡፡ ርዕዮት በችግራችን ጊዜ ፈጣሪ የሰጠን እንስት ኤፍሬም ናት – “ኤፍሬም” ማለት “በመከራዬ ጊዜ የሰጠኸኝ ልጅ” ማለት ነው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ ርዕዮት ብዙ ያነበበች መሆንዋን ከመጽሐፏ መረዳት ይቻላል፡፡ መስዋዕትነት ከማወቅ ጋር ሲሆን የሠመረ ይሆናል፡፡ ማወቅ ብዙ ትናንሽ ግን አዘናጊ የሆኑ ዓለማዊ ነገሮችን እንድንንቅ፣ ታጋሽና አስተዋይ  እንድንሆን፣ ከሚጠፋና ከሚጠወልግ ዝናና የዓለም ሀብት ይልቅ ለማይሞት የሀገርና የወገን ክብር እንድንተጋ… ያደርገናል፡፡ ይህን በርዕዮት፣ በእነእስክንድር ነጋና አንዱዓለም አራጌ አማካይነት እያየነው ነው፡፡ ብዙዎች ሊሸከሙት የከበዳቸውን ቀምበር እነሱ ተሸከሙት፡፡ የኛ ክርስቶሶች እነሱ ናቸው፡፡ የኛ ቤዛዎች እነሱ ናቸው፤ ብዙዎች ሲከዱን እነሱ ከጎናችን ሆነው ስለኛ የኛን መስቀል ተሸከሙ፡፡ ልደቱ አያሌውን የመሰለ ከሃዲ በወጣበት ማኅጸን እስክንድር ወጣበት፡፡ ሙሉጌታ አሥራተ ካሣ በወጣበት ማኅጸን አንዷለም አራገጌ ወጣበት፡፡ ገነት ዘውዴ በወጣችበት ማኅጸን ርዕዮት ዓለሙ ወጣችበት፡፡ ለጊዜው ማለት የምንችለው እንዲህ ብቻ ነው – ሌላ ምን ማድረግ እንችላለን? ምንም፡፡  እውነተኛ የሕዝብ ድምፅ የሚከበርበት ጊዜ ሲመጣ ግን በተለይ ይሁዳዎች ተገቢ ፍርዳቸውን እንዲያገኙ በፍትህ አደባባይ በግልጽ እንጮሃለን፡፡
ባነበብኩት የ204 ገጽ ስብስብ ሥራዎቿ ውስጥ ይህች ወጣት ሴት ጋዜጠኛና ለዜጎች መብት ተሟጋች ያልዳሰሰችው ማኅበራዊ ችግር የለም፡፡ ከይዘቶቹ በመነሣት ነው ልጂቱ ብዙ ያነበበች መሆንዋን የተገነዘብኩት፡፡ ለስኬታማው ውድቀታችን እንደ አንድ ማሳያ ይሆነኛል ብዬ ካሰብኩት ውስጥ የአንድ ዘምቦለል ኢትዮጵያዊን ታሪክ ከርዕዮት መጽሐፍ ጠቅሼ መናገር እፈልጋለሁ፡፡
“… በዘመናችን ከሚገኙ ታዋቂ ሰዎቻችን መካከል አንዱ የሆኑት አንጋፋው የማሰታወቂያ ባለሙያ አቶ ውብሸት ወርቃለማሁ በአንድ ወቅት ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ያደረጉት ቃለ ምልልስ ይታወሰናል፡፡ በቃለ ምልልሳቸው ሴትና መኪናን ቶሎ ካልቀያየሩት ባሕርይው እንደሚበላሽ ሊያስረዱን የሞከሩት አቶ ውብሸት ሁሌም ለብሰው ከሚታዩት ካባ ጋር አብረው የጠቀስነውን ብቃት (የሕዝብ ሰው የመሆንን ብቃት ማለቷ ነው) አለመጎናጸፋቸውን እንረዳለን፡፡” (ገጽ 177)
ርዕዮት የጻፈችበት ርዕሰ ጉዳይ እንስታዊነት (ፌሚኒዝም) በኢትዮጵያ ያለበትን ችግር ነው፡፡ የጠቀሰችው ሰውዬ ታዋቂና ዝነኛ ነው – አርአያ ሊሆን ይገባው የነበረ ነገር ግን እንደኔ አመለካከት ኢትዮጵያዊ ጨዋነትን ገደል የከተተ ብኩን ዜጋ ነው – መፍረድ ቀላል ነው መቼም፡፡
ታዋቂነት ዕዳ ነው፡፡ ብዙ መዘዝ አለበት፡፡ አንድ ሰው ታዋቂ ከሚሆን ይልቅ የማይታወቅ ቢሆን ይሻለዋል፡፡ ከታዋቂነት ጋር የሚመጡ በርካታ ችግሮች አሉ፡፡ ውሎውና አዳሩ ሁልጊዜ በክትትል ውስጥ ነው – እሱ ተኝቶ የማይተኙለት ሰዎች አሉ፤ በበጎም በክፉም፡፡ ታዋቂ ሰው በባህርይው እንደ መላእክት የሆነ ያህል ወይም እንዲሆን የሚጠበቅበት መሆኑን የሚያመላክቱ ሁኔታዎች ሞልተዋል፡፡ ለአንዳንድ የዋህ ታዛቢ ታዋቂ ሰው የማይጠጣና የማይሰክር፣ የማይቆጣና የማይሳደብ፣ ከእንትን የራቀ ድንግላዊ፣ የማይዋሽና የማይቀጥፍ፣ … በጥቅሉ ፍጹም ሰው አድርጎ የማየት አዝማሚያ አለ፡፡ ግን ስህተት ነው፡፡ ሰዎች እንደመሆናቸው ሰው የሚሆነውን ይሆናሉ፤ ሰው የሚያደርገውን ያደርጋሉ፤ ሰው የሚኖረውም ይኖራቸዋል፡፡ ልዩነቱ ግን በነሱ ጎልተው እንዲወጡ የማንጠብቃቸው ብዙ ነገሮች መኖራቸው ነው፡፡ እነሱም መጠንቀቅ የሚገቧቸው እኛም ከነሱ የምንጠብቃቸው በአነስተኛው ማሟላት የሚገቧቸውን ሥነ ምግባራት ማሟላት ሲያቅታቸው ካስቀመጥናቸው ከፍ ያለ ቦታ አውርደን እንፈጠፍጣቸዋለን – እንደውብሸት፡፡ ለኔ ውብሸት ማለት አርአያ ሊሆን የማይችል እንዲሁ ተራና ቅሌታም ሽማግሌ ነው፤ ዕድሜውም ሆነ ያሳለፈው ተሞክሮ ያላስተማረው ከነማሙሽነቱ የሸበተ የእንጨት ሽበት ነው፤ ካባውን የሚያወልቅልኝ ሰው ስንት ጊዜ ፈልጌ አጣሁ፡፡ በባህል ማፌዝ ነው ሰውዬው የተያያዘው፡፡ ካባውን እንዲያወልቅ ብትነግሩልኝ ውለታ አለብኝ፡፡ ከ15 እና ከ16 ዓመት … ነውር ነው!
ይህን መሰል የእንጨት ሽበት በሞላባት ሀገራችን ውስጥ ነው እንግዲህ እነቴዲ አፍሮ ስለጨዋ ባህላችን እየዘመሩ እነውብሸት እያፈራረሱት የሚገኙትን ባህላችንን እየጠገኑ የሚገኙት፡፡ እግዚአብሔር የነዚህን ደጋግ ዜጎች ጸሎት ምህላቸውን ይቀበል ዘንድ፣ ምድራችንን ዳግም የጨዋዎች መፍለቂያ ያደርግልንም ዘንድ እንለምነው፡፡
ወደፕሮፌሰር መጽሐፍ ስመጣ፡-
በዩንቨርስቲ ኮሌጅ የክፍል ኃላፊ የሆንኩት በመከራ ሰው ጠፍቶ ነው፤ ገፋፍቶ የክፍል ኃላፊ እንድሆን ያደረገኝ ዠቪ ያቬትዝ የሚባል እሥራኤላዊ ዲን ነበረ፤ ወደ አገሩ ለዕረፍት ሲሄድ ተጠባባቂ ሆኜ በሱ ቦታ እንድሠራም አግባባኝ፤ … (ገጽ 8)
የዩንቨርስቲው ሠላሳኛ ዓመት ሲከበር የአገልግሎት ሽልማት ስለሚሰጠኝ በበዓሉ እንድገኝ ፕሬዝደንቱ [ዶክተር]ዱሪ መሀመድ ነግሮኝ ነበር፡፡ በዩንቨርስቲ ኮሌጅ አንዲት ኤሊ አለችና እስዋ ትቀድመኛለች፤ ለስዋ ስጣት፤ አልመጣም፤ ስሜን አትጥራ ብዬው ነበር፡፡ ግን ባልነበርሁበት ስሜ ተጠራ፡፡ የደርግ አሥረኛ ዓመት ሲከበርም ልሻን እንደሚሰጠኝ ሰምቼ የጥሪ ካርዱ ላይ ባለ ስልክ ደውዬ እንደማልገኝ አስታውቄ ቀረሁ፤ በሌለሁበት አሁንም ስሜ ተጠራ፤ በጃንሆይ ዘመንም ወደ ፅሕፈት ሚኒስቴር ሄጄ ልሻን እንድቀበል ተነግሮኝ አልሄድኩም፡፡ … (ገጽ 13)
ፕሮፌሰር በነዚህ አባባላቸው ምን ማለት እንደፈለጉ ባውቅ ደስ ባለኝ፡፡ በመሠረቱ ሥልጣንን መውደድና መጥላት ግለሰባዊ ጉዳይ ነው፡፡ አያጣላም፡፡ ነገር ግን ሁሉም ሰው ሥልጣንን ቢጠላ ሀገርን የሚመራት ሰው እንደማናገኝ መረዳት ይገባል፡፡ ስለዚህም ሥልጣንን መጥላት ወይም ከሥልጣን መሸሽ ሁልጊዜ የጤናማነት ምልክት እንደሆነ ተደርጎ መወሰድ ያለበት አይመስለኝም፡፡ መተኮር ያለበት ሥልጣንን በአግባብ የመጠቀም ጉዳይ ላይ ነው፡፡ ሥልጣንና ሽልማትን መጥላትን ለመግለጥ የሚከድበት መንገድ ደግሞ የጨዋነትን ፈር የተከተለ ሊሆን ይገባዋል፡፡ አንድ ሰው አደረገው ተብሎ ለሚታመን መልካም ተግባር እንሸልምህ ሲሉት ለዔሊዋ ስጧት ብሎ ማጣጣል ከሞራል አንጻር ምን ሊባል እንደሚችል በበኩሌ ይጨንቀኛል፤ ለዚህም ነው በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ይህን ክፍል ሳነብ የሚገባኝ ነገር አጥቼ ወይም እንዲገባኝ የማልፈልገው ሊገባኝ ፈልጎ ሲፈታተነኝ ያን ጠልቼ በሃሳብ የናወዝኩት፡፡ ሰውን እንደመረዳት ያለ አስቸጋሪ ነገር የለም፤ ማለት በፈለገው ማለት ያልፈለገውን ወይም ማለት ባልፈለገው ማለት የፈለገውን ለመገንዘብ እንደመቃጣት የሚከብድ ነገርም የለም፡፡ በዚህ የፕሮፌሰር የሥልጣን አልወድም ገለጻ የገባኝ ነገር ሣይገባኝ ቢቀር እንደሚሻለኝ ተመኘሁ፡፡
በመሠረቱ ሹመትን ጠልቶ ዋና ትኩረቱ ከሹመት ጋር ስለሚያያዘው ፖለቲካ ማውራት አይቻልም፤ ሹመት በዓለም ብቻም ሳይሆን በገዳማትም አለ፡፡ ሀገርን ለማቅናትም ሹመት የግድ አስፈላጊ ነው፡፡ እውነተኛና ለሕዝብ በቀናነት የሚሠራበት ሹመት ሊጠላ አይገባም፡፡ በሌላም አነጋገር ሹመትንና ሥልጣንን አምርሮ መጥላት ባለሥልጣናትንና ሹሞችንም አብሮ እንደመጥላት ያህል ሊያስቆጥር ይችላል፡፡ ሥልጣንን በመጥላትና በማስጠላትም ተጨባጭ ቁም ነገር መሥራት የሚቻል አይመስለኝም፤ ዓላማው ግልጽ አይደለምም፡፡ ሥልጣንን የሚጠላ ሰው ደግሞ ስለሥልጣንና ስለፖለቲካ የሚናገረው ነገር ላይ የተወሰነ ጥላ ማሳረፉ አይቀርም፡፡ ያልተዛባና ፍትሃዊ አስተያየት ስለመስጠቱም አጠራጣሪ ነው፡፡ ቀድሞውን አወንታዊ እይታ የለውም ተብሎ ስለሚገመት ነጻና ገለልተኛ አስተያየት ይሰጣል ተብሎ አይገመትም፡፡ …
ላጠቃልል ነው፡፡ የሕዝብ ሰው መሆን ከፍ ሲል እንደጠቆምኩት ከባድ ነው፡፡ ሰውን ማክበር ያስፈልጋል፡፡ ትሁት መሆን ይገባል፡፡ ከአፈንጋጭ ስብዕና ለመራቅ ዘወትር መጠንቀቅ ያስፈልጋል፤ በዚህች ምድር የሚያኮራና እንድንታበይ ሊያደርገን የሚችል አንድም ነገር የለም፡፡ ሁሉም አላፊና ጠፊ ነው፤ ሀብትን ብል ይበላዋል፤ ዕውቀትን ‹ምሥጥ› ያነክተዋል፤ የዝናን ወርቃማ ቀለም ዘመን ያደበዝዘዋል፤ መልክና ውበት የዕድሜ ሽብሽባት ያጠወልገዋል፡፡ ምን ቀረን? ምንም! አንድ በትምህርትም ሆነ በሌላ ነገር ዕውቅናና ስመጥርነትን ያገኘ ሰው ከግል ሕይወቱ ሥምረት ጀምሮ ለሌሎች አርአያ ለመሆን መትጋት ይጠበቅበታል፡፡ ትዳርን ማክበር፣ ሃይማኖታዊ ትዕዛዛትን በተቻለው መጠን ማክበር፣ ሥነ ልሣናዊ የመግባባት ደረጃዎችን መለየትና በአግባቡ መጠቀምን መልመድ (ለምሳሌ አንተ እና አንቱ የሚባሉ አጠቃቀሞችን፣ የማዕረግ ስሞችን እንደዬሁኔታው መገልገልን ማወቅ …)፣ በወገን ችግር ጊዜ ቀድሞ መድረስንና ከልብ ለመርዳት መሞከር፣ ከምንም ዓይነት ዕብሪታዊና ትዕቢታዊ የአነጋገር ሥልት መለየት … ይጠበቅበታል፡፡ የተገነባ ስም እንደሚናድም መረዳት ተገቢ ነው፡፡ ብዙ አብነቶችን መጥቀስ ቢቻልም አላሙዲን ብቻ ይበቃናል፡፡  (ሰው ባጣንበት ዘመን ሰው የሆኑን እነቴዲ አፍሮና ታማኝ በየነ የሰይጣናዊ የልብ እብጠት ሰለባዎች እንዳይሆኑብንና እንዳይሰናከሉብን በበኩሌ እጸልያለሁ፤ ሁላችንም እነዚህን ወገኖች እንዲያበዛልን በአቋማቸው እንዲያጸናልንም እንጸልይላቸው፡፡ የሰው ዐይን ድንጋይ ይሰብራልና ከዐይን ያውጣልን፡፡ ሰው አልበረክትልን ብሎ ተቸግረናልና ይህን ሾተላይ ፈጣሪ እንዲያነሳልን ወደላይ እንማጠን፡፡)
እንዲያው ግን ሌላውን ነገር ሁሉ ልርሳውና አርአያ የሚሆን ሰው ጌታ በኪነ ጥበቡ አስተካክሎ ይስጠን – ከየዘርፉ፡፡ ደግሞም ይችላል፡፡ ከቁጣ የራቀ፣ ከትዕቢት የተቆራረጠ፣ ከትምክህት የተፋታ፣ ከጥበብ የተጋባ፣ አስተዋይነትና ትህትና ሞልቶ የተረፈው፣ ቅን አሳቢና ለሀገር ለወገን ተቆርቋሪ የሆነ የሕዝብ ሰው ይስጠን፡፡ ሁሉን ነገር ማድረግ የማይገደው የኢትዮጵያ አምላክ እኛንም ባሕርያችንን ገርቶ እንደገና ይፍጠረንና እርስ በርስ የምንተሳሰብ፣ ደገኞችና አስተዋዮች ያድርገን፡፡ ለዘመናት ከሚጨፍርብንና እግር ከወርች በማሰር ኮድኩዶ ከያዘን የምቀኝነት አባዜ ነጻ የወጣን እንሆን ዘንድም ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፤ አሜን በሉ፡፡ ኧረ አቅላቀችንን ይመልስልን ወገኖች! ተበታትነን ቀረን እኮ፡፡ ብዙ ቢናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራልና በነገር እንዳላሰለቻችሁ ነገሬን ሳላንዛዛ ባጭሩ እዚህ ላይ ልቋጭ፡፡

1 comment:

  1. ሚስተር ቤንጃሚን የኢሜል ዝርዝሮችን እነሆ ፣ Lfdsloans@outlook.com ፡፡ / ወይም ደግሞ ንግዴን ለመጀመር በ 90,000.00 ዩሮ ብድር የረዳኝ WhatsApp + 1-989-394-3740 እና እኔ በጣም አመስጋኝ ነኝ ፣ እዚህ አንድ ነጠላ እናት ነገሮች እንዳላደረጉ መንገድ ለመፍጠር እየሞከርኩ ነው ፡፡ ከእኔ ጋር ቀላል ይሁኑ ግን ንግዴ እየጠነከረ ሲመጣ እና እያሰፋ ሲሄድ እያየሁ በሚስተር ሚስተር እርዳታ ፊቴ ላይ ፈገግታ አሳየኝ ፡፡ የገንዘብ ድጋፍን መፈለግ ወይም በዚያ ንግድ ውስጥ መከራን ማለፍ ወይም የመነሻ የንግድ ሥራ ፕሮጀክት መጀመር መፈለግ ይህንን ማየት እና ከችግራቸው ለመውጣት ተስፋ ሊኖረው ይችላል ... እናመሰግናለን ፡፡

    ReplyDelete