Translate

Sunday, January 3, 2016

የመጨረሻዉ መጀመሪያ — አሜሪካ ለምን የአርባ ምንጭ የሰዉ አልባ አይሮፕላን ማስነሻ ጣቢያዋን መተዉ አስፈለጋት?

ከሳዲቅ አህመድ

US shuts down drone operation in Ethiopiaወደ አለም አቀፉ የዲፕሎማሲ መንደር ቀረብ ቀረብ ማለት ከጀመሩ ወራት ተቆጥረዋል። ከሐያላኑ አገራት ጋር የቀጥታ ሳይሆን የእጅ አዙር የዲፕሎማሲ ጉዞን ሳይጀምሩ አልቀሩም የሚሉም አሉ። በጠመዝማዛዉ መንገድ የሚጓዙት የዲፕሎማሲ ጉዞ ከሚፈልጉበት ቦታ እስኪያደርሳቸዉ ድረስ እምብዛም አትኩሮት አልሳቡም። እርሳቸዉ ግን እየተጓዙ ነዉ። ፕሬዝዳንት ኢሳያስ  አፈርቂ።
ዜናዉ፦

አሜሪካ አርባ ምንጭ ዉስጥ ያላትን የሰዉ አልባ አይሮፕላን ማብረሪያ ጣብያ መጠቀም ማቆሟ ታወቀ

በሱማሊያ ያሉትን አል-ሸባቦች ለማጥቃት አሜሪካ እንደ ኢሮጵያዉያን አቆጣጠር ከ2011 ጀምሮ ትጠቀምበት የነበረዉን የሰዉ አልባ አይሮፕላን ማስነሻ ጣብያ መጠቀም ማቆሟን አሶሽየትድ ፕሬስ አዲስ አበባ ያለዉን የአሜሪካ ኤምባሲ ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።
ዴቪድ ኬኔዲ የተባሉት የኤምባሲዉ ቃል-አቀባይ ለአሶሽየትድ ፕሬስ በኢሜይል በላኩት መልእክት ሁለቱ አገራት ባደረጉት ስምምነት አሜሪካ በአርባ ምንጭ የምታደርገዉ ቆይታ አስፈላጊ አይደለም።የኤምባሲዉ ቃል አቀባይ ይህንን ቢሉም የኢትዮጵያና የአሜሪካን ግንኙነት የሚከታተሉ ባለሙያዎች ክስተቱ አሜሪካ የፖሊሲ ለዉጥ ማረግ መጀመሯን አመላካች ዱካ ሊሆን ይችላል ሲሉ ይጠቁማሉ።
ለጋሽ አገራትና ፍላጎታቸዉ
የቀድሞዉ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆርጅ ቡሽ ሽብር ፈጠራን የመዋጋት ዘመቻ ማወጃቸዉ የሚዘነጋ አይደለም።ኢትዮጵያ የዚሁ ሽብር ፈጠራን የመከላከል ሚና ተሰጥቷትበምላሹ ከለጋሽ አገራት ድጎማን ስትቀበል መቆየቷ ይታወቃል።መረጃዎች እንደሚያመላክቱት አሜሪካ ለኢትዮጵያን በደንብ አርጋ ትለግሳለች። በ2008እንደ አዉሮፕያዉያኑ አቆጣጠር አሜሪካ ለኢትዮጵያ 969ሚሊዮን ዶላር ለግሳለች። በ2009 916 ሚሊዮን ዶላር፣በ2010 የለገሰችዉ ወደ 513 ሚሊዮን ዝቅ ማለቱ ይታወቃል።
አሜሪካ ኢትዮጵያን የምትለግሰው አገሪቷ ዉስጥ የሚከሰተዉን የድርቅና የርሃብ አደጋ ለመከላከል፣ድህነትን ለመቋቋም፣ ለመልካም አስተዳደር፣ ማህበራዊ ሁናቴዎች ላይ ያሉ መመሪያዎችን ለማሻሻልና ለወታደራዊ ስልጠና መሆኑን መረጃዎች ያመላክታሉ። የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የሆኑ ድርጅቶች ኢትዮጵያ ዉስጥ ከፍተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብት ረገጣ በመኖሩ አሜሪካ እና ሌሎች ለጋሽ አገራት የሚለግሱት ገንዘብ የአገሪቱን ዜጎች ህልዉና አደጋ ላይ የሚጥል መሆኑን ያስጠነቅቃሉ።
አኩሪ ስራን ሰሪ ወይስ ሽብርን ፈጣሪ?
የአሜሪካዉ ፕሬዝዳት በራክ ኦባማ በሐምሌ 20/2007 ወደ ኢትዮጵያ በተጓዙበት ወቅት “ኢትዮጵያ ሽብር ፈጠራን በመከላከል ጽኑ የአሜሪካ አጋር ናት፣ ኢትዮጵያዉያን ጠንካራ ተዋጊዎች ናቸዉ” ማለታቸዉ ይታወሳል። ኦባማ ይህንን ቢሉም፤ የኢትዮጵያ መንግስትን የሚቀናቀኑ ቡድኖች በህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ የሚመራዉ መንግስት ‘ሽብር ፈጠራ በሱማሌ ዉስጥ እንዲስፋፋ ከአልሸባብ ጋር ግንኙነት ያደርጋል፣የሶማሊያን የጦር አበጋዞች እያስታጠቀ ሽብር ፈጠራን መነገጃ አድርጓል፣የኢትዮጵያ ወታደሮችን ሶማሊያ እየላከ ያስፈጃል ሲሉ መንግስትን ተጠያቂ ያደርጋሉ።ጄከብ ጁማ የተባሉ ኬንያዊ ቱጃር በመጋቢት 25/2007 በትዊተር ገጻቸዉ ላይ በለቀቁት መረጃ “የኢትዮጵያ መንግስት አሸባሪዉን አል-ሸባብ ያስታጥቃል።አዲስ አበባ ለአፍሪካ ቀንድ አለመረጋጋት ተጠያቂ ናት።የኬንያዉ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የአፍሪካዉ ህብረትና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የኢትዮጵያ መንግስትን እንዲመረምሩ ግፊት ማድረግ አለባቸዉ!” ብለዉ ነበር። የቱጃሩ መረጃ አነጋጋሪ ሆኖ መሰንበቱ ይታወሳል።ለኢትዮጵያ መንግስት ቅርበት ያላቸዉ የመገናኛ ብዙሃን ጉዳዩን ለማስተባበል ስሯሯጡ መታየታቸዉ የሚዘነጋ አይደለም።
የእጅ አዙር ዲፕሎማሲ?
በህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ የሚመራዉ የኢትዮጵያ መንግስት ተቀናቃኝ አጎራባች አገራት ስለመጡበት ለምእራቡ አገራት የሚኖረዉ ስልታዊ አጋርነት እየቀነሰ ነዉ በማለት የሚገልጹም አሉ።የአሜሪካ ስልታዊ አጋር የሆኑ የባህረሰላጤዉ ሱኒ ሙስሊም አገራት የአሰብ ወደብን መገልገያ ለማድረግ መወሰናቸዉ አነጋጋሪ ሆኗል።
በአሜሪካ የዉጭና የዲፕሎማሲ ጉዳዮች 38 አመታትን ያገለገሉት አምባሳደር ሐርማን ኮህን በአፍሪካ ቀንድ እየተከሰተ ስላለዉ ፈጣን ለዉጥ በታህሳስ 18/2008 በግል ገጻቸዉ ላይ ጽፈዉ ነበር።…”እናንተ አቢሲኒያዉያን ሆይ!” ብለዉ የተጣሩት አምባሳደር ኮህን “እናንተ በእርስ-በርስ ግጭት ስትጣሉ…ስትጯጯሁና…ሳትነጋገሩ… የባህረ ሰላጤዉ መንግስታት ምሳቹን እየበሉባቹ ነዉ” ብለዉ አስጠንቅቀዋል። ኮህን አክለዉም የተባበሩት አረብ ኤምሬት አይሮፕላኖች ከአሰብ ያለማቋረጥ መንቀሳቀሳቸዉንና ሳዑዲ አረቢያ በአሰብ ላይ የ50 አመታት ኪራይ መዉሰዷን አመላካች ሪፖርቶች መኖራቸዉን ገልጸዋል።
የባህረ ሰላጤዉ የሱኒ ሙስሊም አገራት በየመን በኩል ያለዉን የኢራንንና የሺዓ መስፋፋት ለመከላከል ኤርትራ ላይ አትኩሮት ማድረጋቸዉ የሚታወቅ ነዉ። እነዚህ በነዳጅ ዘይት ገንዘብን ያካበቱ አገራት ከአሜሪካ ጋር ስልታዊ አጋሮች ናቸዉ። ከአሜሪካ ጋር በኢኮኖሚዉና በወታደራዊ ግንኙነት የዉዴታ ግዴታ ቁርኝት አላቸዉ። ወደ አሰብ መዘንበላቸዉና አሰብን መከራየታቸዉ ያለአሜሪካ ይሁንታ በራሳቸዉ ፍላጎት ብቻ የተደረገ ነዉ ለማለት አያስደፍርም።
ሽብር ፈጠራን ለመከላከል በሚል መርህ በሳዑድ አረቢያ የሚመራ የ34 አገራት ጥምር ጦር በታህሳስ 5/2008 ተመስርቷል። ይህ ጥምር ጦር የኪራዩን የአሰብ ወደብ አይጠቀምም ማለቱ አስቸጋሪ ነዉ። የጥምር ጦሩ አላማ ISIS እና ሌሎችን በኢስላም ስም የተነሱ አሸባሪዎችን ማመናመን መሆኑ እየተነገረ ነዉ።የአገራቱ ጣምራ ጦር የተዋቀረዉ ለፕሮፓጋንዳ ካልሆነና አላማዉ ተግባር ላይ ከዋለ፤ ISIS ብቻ ሳይሆን በሶማሊያ ያለዉም አል-ሸባብ የጣምራ ጦሩ ተጠቂ የሚሆንበት እድል የሰፋ ነዉ።ስለዚህ አሜሪካ ለምን አርባ ምንጭ ላይ የሰዉ አልባ አይሮፕላን ማስነሻ ይኖራታል? ስልታዊ አጋሬ የምትላቸዉን አገራትን በጅ አዙር ከመጠቀም ምን ይከለክላታል? ለምን የጠገበዉን አሳማ (ህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ) ትቀልባለች? ለአሜሪካ በጅ አዙር የተራበችዉን ኤርትራ ማብላት አይሻላትም ?
ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወቂ ለምን በአንድ አመት ሁለት ግዜ ወደ ሳዑዲ አረቢያ ተጓዙ?
ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወቂ መጀመሪያ በሚያዚያ 21/2008 ወደ ሳዑዲ አረቢያ በመጓዝ ከአገሪቱ ንጉስ ሰልማንቢን አብዱል አዚዝ አል-ሱዑድ ጋር መገናኘታቸዉ በአረቡ አለም በሰፊዉ የተዘገበ ቢሆንም ኢትዮጵያዉያን እምብዛም አትኩሮት የቸሩት አይመስልም ነበር። ኢሳያስ አፈወርቂ ዳግም በታህሳስ 10/2008 ወደ ሪያድ ሳዑዲ አረቢያ የሁለት ቀን የስራ ግብኝት ለማድረግ ማቅናታቸዉ በአገራቱ መካከል የጠበቀ ስልታዊ ግንኙነት መመስረቱን አመላካች ነበር።የኢሳያስን የሳዑዲ ሁለተኛ ጉዞ ተከትሎ ኤርትራ ጣምራ የ34 ጦር አገራትን ሐይል ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንደምትደግፍ ከአገሪቱ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዉጡ መረጃዎች አመላክተዋል።
ህወሃት መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት ለጸረ ሽብር ተግባር ከለጋሾች እርዳታ የሚቀበልበት አል-ሽባብ የጣምራ ጦሩ አባልና ደጋፊ በሆኑ አገራት ተከቧል። ሶማሊያ፣ጅቡቲ እና ኤርትራ ጣምራ ጦሩን ደጋፊ ናቸዉ።ስለዚህ አሜሪካ ለምን የሰዉ አልባ አዉሮፕላን ማስነሻዋን አርባ ምንጭ ማቆየት ያሻታል?
ማስጠንቀቅና ልመና
በጋምቤላ እና በኦሮሚያ ያሉ አርሶ አደሮችን እያፈናቀለ መሬትን ለሳዑዲ አረቢያና ለሌሎች አገራት ሲያከራይ የነበረዉ የኢትዮጵያ መንግስት አስመራም ተመሳሳይ ስራ በመጀመሯ ደስተኛ አለመሆኑን እየገለጸ ነዉ። በባለፍዉ የህዳር ወር መገባደጃ ጠቅላይ ሚኒስቴር ሐይለማሪያም ደሳለኝ ሳዑዲ አረቢያና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶችን ማስጠንቀቃቸዉ ታዉቋል። ለአገር ዉስጥ ጋዜጣ ቃለ መጠይቅ የሰጡት ሐይለማርያም ደሰላኝ በአሰብ ወደብ ላይ የሚያደጉትን እንቅስቃሴ ተከትሎ ኢትዮጵያ ለሚኖራት ምላሽ ሐላፊነቱን ሳዑዲ አረቢያና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ይሸከማሉ ብለዋል።
የጠቅላይ ሚኒስቴር ሐይለማሪያም ደሳለኝ ማስጠንቀቂያ ሳይሻር በከፍተኛ የኢትዮጵያ የመንግስት ባለስልጣናት የሚመራ የልዑካን ቡድን ወደ ተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በታህሳስ23/2008 በመግባት አቡ ዳቢ ፈንድ ፎር ዴቨሎፕመንት የሚባል የተራድኦ ድርጅትዘንድ በማምራት በሁለትዮሽ የእድገት፣ የመዋእለ ንዋይ እና የእርዳታ ጉዳዮች መነጋገራቸዉ ተዘግቧል።
እየቀረበ ያለዉ ለዉጥ
ህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ በጅ አዙር አሸባሪን የመዋጋት የገበያ እሽቅድም ከጁ እየተፈተለከበት ይመስላል። ኤርትራ እና የ34 አገራት ጣምራ ጦር እየተፎካከሩት ነዉ። ስርዓቱ በከፍተኛ አጣብቂኝ ዉስጥ ገብቷል። ከዚህ አጣብቂኝ ለመዉጣትም እንደ አማራጭ የወሰደዉ የጅምላ ግድያንና እስር ነዉ። ተሰሚነት ያላቸዉ ሰዎች፣አክቲቪስቶች፣ጋዜጠኞች፣የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች፣ተማሪዎች፣ መምህራንና ሌሎችም የስ ርዓቱ ሰለባ እየሆኑ ነዉ። የማሰቃያ እና የማጎሪያ እስር ቤቶች መሙላታቸዉ እየተነገረ ነዉ። በጥቅሉ በህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ የሚመራዉ መንግስት አይደለም አሸባሪነትን ሊከላከል እራሱ አሸባሪ በመሆን ለዜጎች ህልዉና ስጋት መሆኑን የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁናቴ መቃኘቱ በቂ ነዉ።
አዲሱ የኢትዮጵያ አመት ከገባበት ግዜ ጀመሮ በተለያዩ ቦታዎች ቦምብ መፈንዳት ጀምሯል። በታላቁ አንዋር መስጊድ ዉዳሴ (መንዙማ) ሲያሰሙ በነበሩ ምእምናን ላይ በታህሳስ 1/2008 የቦምብ ጥቃት ደርሷል። በጥቃቱም እስከ 18 የሚደርስ ሰዉ ተጎድቷል።ተመሳሳይ የቦምብ ጥቃት በታህሳስ 22/2008 በዲላ ዩንቨርስቲ ተከስቶ 3 ሰዎች ሲሞቱ 6 መቁሰላቸዉ ታዉቋል። ዜጎች በነቂስ ድርጊቱ የህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ ነዉ የሚል መግባባት ላይ የደረሱ ይመስላል። ይህንኑ ለማረጋገጥ እስኪመስል ድረስ ዊኪ ሊክስ የተባለዉ የመረጃ አነፍናፊ ድረ ገጽ በበመስከረም5/2004 የኢትዮጵያ መንግስት እራሱ ቦምብ አፈንድቶ በኤርትራና በኦነግ እንደሚያላክክ አዲስ አበባ ከሚገኘዉ የአሜሪካ ኤምባሲ አፈትልኮ የወጣ መረጃን ዋቢ በማድረግ ለአለም ህዝብ አሳዉቋል። ታዲያ ህወሃት ወራሹ መንግስት እንደምን በጸረ ሽብር ዘመቻ ሁነኛ ስልታዊ አጋር ሊሆን ይችላል?
ከብሔራዊ ጭቆና ወደ ብሔራዊ ድል
ህወሃት መራሹ መንግስት በእምነት ጉዳይ ጣልቃ እንደሚገባ ክስ ይቀርብበታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዉስጥ ጣልቃ ገብቷል የሚል ለአመታት የዘለቀ ብሶት አለ። ኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች መጤ አንጃ አምጥቶ ጫነብን ብለዉ በመቃወም አለም አቀፍ ሰላማዊ ንቅናቄን ጀምረዉበታል።ህወሃት የአገሪቷን ሐብት ተቀራመተዉ፣ጥቂቶች ሐብታም ሲሆኑ ሚሊዮኖች በድህነት ማቀቁ የሚለዉ እሮሮ በሰፊዉ ይሰማል። አገሪቷ ዉስጥ የተንሰራፋዉ የርሃብ አደጋ በተፈጥሮ ክስተት የመጣ ቢሆንም የመልካም አሰተዳደር እጦት ርሃቡን የከፋ እንዲሆን አድርጎታል የሚለዉ ህዝባዊ ብሶት በሐዘና በሲቃ የሚሰማ ነዉ። የኢትዮጵያን ድንበር ቆርሶ ለሱዳን ለመስጠት የኢትዮጵያ መንግስት መስማማቱ የአገርን ሉዓላዊነት አስደፈረ የሚል ብሔራዉ ቁጭትን ፈጥሯል።በአገሪቷ ላይ የተንሰራፋዉ የመሬት ቅርምት ዜጎች በጫንቃቸዉ ላይ ሊሸከሙት ከሚችሉት በላይ ሆኖ እየተንገፈገፉበት ነዉ።
የኦሮሞ ተማሪዎች “መሬቴን አላስነጥቅም!” የሚለዉ ንቅናቄ አገራዊ ሆኖ ስርዓቱን ለመናጥ የበቃ ነዉ።ህወሃት ይህንን ሰላማዊ ንቅናቄ ለመቀልበስ በሰላማዊ ዜጎች ላይ አጋዚ በሚባለዉ ቅልብ ጦሩ የሚወስደዉ ዘግናኝ እርምጃ ህዝቡ ወደ “ህዝባዊ እንቢተኝነት” እንዲያመራ እየዳረገዉ ነዉ። ወልቃይት ጸገዴዉ ተገድጄ ትግራይ ዉስጥ ተካለልኩ ወደ አማራ ክልል ልመለስ በማለት የማንነት ንቅናቄን ጀምሯል። የጎንደሩ ገበሬ በደሙ የዋጀዉ መሬት ለሱዳን ሊሰጥ በመሆኑ እምቢኝ አሻፈረኝ ብሎ እየተነሳ ነዉ። አኝዋኩ መሬቴ ለባእዳን ተሽጦ በግፍ ተገደልኩ፣በግፍ ተፈናቀልኩ እያለ ነዉ። አርበኞች ግንቦት 7 በጦርነት ህወሃት መራሹን መንግስት እጥላለሁ ብሎ እየተዋደቀ ነዉ።
ብሶት የማይሰማበት የኢትዮጵያ ክልል የለም።ዜጎች ህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ ለ25 አመታት ባንሰራፋዉ አምባገነናዊ ስርዓት ተንገፍግፈዋል።
የማይቀር ህዝባዊ እምቢተኝነት ከፊት ለፊት ተጋርጧል። አሜሪካንም ሆነች ሌሎች ሐያላን አገራት ለህዝባዊ ጩኸት ‘ጆሮ ዳባ ልበስ’ ያለዉን ህዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ ጣል-ጣል ቢያረጉ አይገርምም። የሚገርመዉ ‘ከማይታወቅ መልአክ… የሚታወቅ…’ ብለዉ በህወሃት ላይ ተስፋ ቢያረጉ ነዉ። አሜሪካንም ሆኑ ሌሎች በኢኮኖሚ የበለጸጉ አገራት ቅድሚያ ለብሔራዊ ጥቅማቸዉ ነዉ የሚሰጡት። አገራቱ ብሔራዊ ጥቅማቸዉ ህወሃት ጋር አለመኖሩን ቢረዱትም ያቺን የመጨረሻዋን ሰዓት የሚጠብቁ ይመስላል። ታዲያ!…ዉድና ጠቃሚ የጦር መሳሪያዎቻቸዉን ወደ ሌላ ቦታ መዉሰዱ መጨረሻዉ እየጀመረ አይመስልምን? “የመጨረሻዉ መጀመሪያ!” ለማንኛዉም ልብ ያለዉ ልብ ይበል።

No comments:

Post a Comment