Translate

Tuesday, November 26, 2013

ከአቶ ታምራት ላይኔ ጋር የተደረገ ቃለ ምልልስ (ከአንድ ጉዳይ በቀር በርካታ ቁምነገሮች አለው)

(ዳዊት ከበደ ወየሳ) – ከአቶ ታምራት ላይኔ ጋር የተደረገው ቃለ ምልልስ አስገራሚ ነው። በአውስትራልያ የ-SBS አማርኛ ፕሮግራም ነው ይህንን ያስደመጠን – ምስጋና ይገባቸዋል። በቃለምልልሱ ውስጥ የምናውቃቸውና የማናውቃቸውን፤ በወሬ የሰማናቸውንም ሆነ በታሪክ ያየናቸውን ጉዳዮች ተካተዋል። ከራሳቸው የግል ህይወት አስተዳደግ እና አስተሳሰብ በመነሳት ስለ ትጥቅ ትግሉ ታሪክ ብዙ ብዙ ነገሮችን ብለዋል። ኢህዴን የተባለው ድርጅት ከጎንደር አካባቢ ተነስቶ ወደ ትግራይ ክልል ከመሄዱ በፊት፤ ከህወሃት ጋር የርስ በርስ ንግግር የተደረገ መሆኑን፤ ያንጊዜ ወደ ትግራይ እንዲገቡ ባይፈቅዱላቸው የርስ በርስ ግጭት ሊኖር ይችል እንደነበር ወይም ወደ ሱዳን ተመልሰው ሃይል አጠናክረው ትግራይ መግባታቸው የማይቀር መሆኑን ያብራራሉ። ከዚህም በተጨማሪ ኢህዴን በኤርትራ ላይ የነበረው አቋም ምን እንደነበረና በኋላም ከህወሃት ጋር ተቀላቅሎ “ኢህአዴግ” የተባለ ግንባር መመስረቱን፤ ከዚያም ይህ ድርጅት ከብሄራዊ ድርጅትነት ወደ ብሄር ድርጅትነት ወርዶ “ብአዴን” ስለመባሉ ይገልጻሉ። ነገር ግን ወደ ዝርዝር ማብራሪያ አልሰጡበትም። “ብዙ ነገር አለ” ብለው ያልፉታል።
እነዚህ ከላይ የገለጽናቸውን ጉዳዮች በክፍል አንድ ላይ ሊያዳምጡት ይችላሉ።

በክፍል ሁለት ላይ በተደረገው ቃለ ምልልስ ላይ ደግሞ በ1981 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የከሸፈውን መፈልቅለ መንግስት ተከትሎ፤ ኢህዴን እና ህወሃት ወደ ውህደት ማምራታቸውን ይገልጻሉ። ከውህደቱ በኋላ ከዚያም በሽግግር መንግስቱ ጊዜ የነበሩትን ውጣ ውረዶች ያብራራሉ። ገብያ መር ኢኮኖሚ ለመከተል የተደረገውን ጥረት፤ እንዲሁም እሳቸው በጠቅላይ ሚንስትርነታቸው ዘመን ያወጡት የኢኮኖሚ ፖሊሲ በኋላ ላይ ብዙ ነገሩ መሻሩ፤ በትግራይ የግል ቤቶች ተመልሰው በሌላው ክልል ግን እንዳይመለስ መደረጉ “ድሮም ስህተት ነበር፤ አሁንም ስህተት ነው” ይላሉ። ኢህአዴግ ክልሎችን በብሄር ማደራጀቱ፣ እንዲሁም ኢትዮጵያ የአሰብ ባለቤትነቷን፤ በአቶ መለስ ዜናዊ አማካኝነት እንድታጣ መደረጓ ትልቅ ስህተት እንደነበርና እነዚህን እና ሌሎች ጉድለቶችን እስር ቤት በነበሩበት ወቅት ለማየት መቻላቸውን በክፍል ሁለት ቃለ ምልልስ ላይ ገልጸዋል።
ከአንድ አስቀያሚ እንከን በቀር፤ ይህንን ቃለ ምልልስ ማዳመጡ ጠቀሜታው ላቅ ያለ ነው። እንከኑ የተፈጠረው በክፍል ሁለት ላይ “የርስዎ ሌጋሲ ምን ነበር?” ሲባሉ፤ “የሃይማኖት እኩልነት እንዲከበር ማድረጌ ነው” ብለዋል። አቶ ታምራት ላይኔ ይህንን ካሉ በኋላ፤ ከዚያ ቀደም ሲል የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮች ይታሰሩ እና ይገደሉ ነበር” ይገልጻሉ። እዚህ ላይ ጣልቃ በመግባት የግል አስተያየታችንን እናቅርብ። በርግጥ በደርግ የመጀመሪያ አመታት ሃይማኖት የተዋረደበት እንጂ የተከበረበት ወቅት አልነበረም። በመሆኑም የኦርቶዶክስም ሆነ፣ የፕሮቴስታንት ሃይማኖች አባቶች፤ በተለይም የኦርቶዶክሱ ፓትርያርክ ታስረው የተገደሉበት ወቅት ነው። በስተበኋላ ላይ ግን ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ተከፍተው አገልግሎት መስጠታቸውን ቀጠሉ። ሌላው ቀርቶ የክርስትና በአላት ሲመጡ የኦርቶዶክስ፣ የፕሮቴስታንት እና የካቶሊክ አባቶች በሬድዮ እና በቴሌቪዥን ቡራኬ መስጠት የጀመሩት በደርግ ዘመን ነበር። በተለይ በመጨረሻዎቹ አመታት የደርግ ባለልጣናት፣ የኮ/ል መንግስቱ ኃይለ ማርያም ልጆች ጭምር የግል ሃይማኖታቸውን በነጻነት ሲያካሂዱ እንደነበር ይታወቃል። በወቅቱ በነበረው የደርግ ህገ መንግስት ጭምር የሃይማኖት እኩልነት የተከበረ መሆኑ በጽሁፍ ተገልጿል።
Former Ethiopian PM Tamrat Layene
Former Ethiopian PM Tamrat Layene

በታሪክ ወደኋላም መመለስ ይቻላል። ዛሬ መሰረት የጣሉት ትላልቅ የፕሮቴስታንት አብያተ ክርስቲያናት የተመሰረቱት የቀዳማዊ ኃይይለ ስላሴ ዘመን ነው። የፕሮቴስታንት ሚሲዮኖች ወደ ኢትዮጵያ ገብተው ማስተማር እና መስበክ የጀመሩት ከአ13ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በተለይም በነአጼ ልብነ ድንግል እና አጼ ገላውዴዎስ ዘመን መሆኑን ታሪክ ይነግረናል። ሌላው ቀርቶ በአጼ ቴዎድሮስ ዘምነ የነበሩት የግል ጸሃፊያቸው አለቃ ዘነብ ጭምር የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ ነበሩ። በርካታ የፕሮቴስታንት ሚሲዮኖች በኢትዮጵያ ውስጥ እንዲስፋፉ፣ ህዝቡን እንዲያስተምሩ የተደረገው እና የተፈቀደው በአጼ ምኒልክ ዘመነ መንግስት ነው። አንዳንድ ጊዜ ታሪክን ካለማወቅ እና ሌላውን ከመናቅ በሚመነጭ ትምክህት ምክንያት ህሊናችን መጨለም የለበትም።
እንግዲህ እነዚህን እና ሌሎችም እውነታዎችን በመዘርዘር የአቶ ታምራት ላይኔ ሚዛን የማይደፋ “የኔ ሌጋሲ” ብሎ ትምክህት ብዙም ደስ የማይል ጆሮ የሚኮረኩር ነገር ሆኖብናል። ገና ለገና ከ እስር ቤት መልስ “ፕሮቴስታንት ሆኛለሁ” በማለት የሚሰነዘሩ አስተያየቶች፤ ትንሽ ለጆሮ ይጎረብጣሉ። ለምሳሌ ከዚህ ቃለ ምልልስ ቀደም ብለው አቶ ታምራት ላይኔ በጠቅላይ ሚንስትርነት ስልጣን ዘመናቸው፤ በወቅቱ የነበሩትን የኦርቶዶክስ ፓትርያርክ ከስልጣናቸው እንዲነሱ ደብዳቤ የጻፉላቸው መሆኑን ገልጸዋል። ይህን በተናገሩበት አንደበት መልሰው “ደርግ ፕሮቴስታንቶችን ያስር እና ይገድል ነበር። እኔ ግን የሃይማኖት እኩልነትን አስከብሬያለሁ። ይህም የኔ ሌጋሲ ነው።” ብሎ ማለት ብዙም ደስ አይልም። እንዲያውም ያንን ሁሉ፤ አፍ የሚያስከፍት ግሩም የሆነ ቃለ ምልልስ ያበላሸ ነገር ቢኖር፤ እንዲህ ያለው የውሸት እና አድልዎ የመሰለ አባባል ይመስለናል። ከዚህ በኋላ አቶ ታምራት ላይኔ አንድ ሌላ ቃለ ምልልስ የሚያደርጉ ይመስለናል። እንደኛ እምነት ከሆነ፤ የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር “ይቅርታ” ባይሉም እንኳን (የቀድሞ ኮሚንስቶች የሚያርማቸውን ይቅርታ አይሉምና) ቢያንስ ተመሳሳይ ስህተት ባይሰሩ ደስ ይለናል። ቢያንስ እሳቸው ከያዙት የፖለቲካ እና ሃይማኖት ውጪ ያሉትን ሰዎች አመለካከት ማክበር አንድ ነገር ሆኖ፤ ታሪክን ማዛባት ግን ደግ ስላይደለ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል።
ከላይ ከተጠቀሰው ህጸጽ ውጭ ሌላው ታሪክ፤ እንደታሪክነቱ መነገር የነበረበት፤ ህዝቡም ሊያውቀው የሚገባ በመሆኑ ቃለ ምልልሱን ደግመው ደጋግመው እንዲያዳምጡት ግብዣችን ነው።

No comments:

Post a Comment