Translate

Wednesday, July 24, 2013

እስቲ እረጋ ብለን ደግሞ እንነጋገር… “ጭርቁምፈምቶታ ኡመታ ኢትዮጵያ”

1057430_650235654989038_1014715955_n
Abe Tokchaw
እስቲ እረጋ ብለን ደግሞ እንነጋገር…  ”ጭርቁምፈምቶታ ኡመታ ኢትዮጵያ” ወንድማችን
ጃዋር መሀመድ እኔን ጨምሮ በርካቶች የሚያደንቁት ወጣት ነው፡፡ ሀሳቦቹ አንጀት ላይ ጠብ የሚሉ ገዢ ሀሳቦች ናቸው፡፡ የሚገዙት ታድያ እንደ ገዢው ፓርቲ አስገድደው አይደለም፡፡ ጃዋር ወደው ፈቅደው የሚገዙላቸው ሀሳቦች ባለቤት ነው፡፡ እኔ ከጃዋር ሀሳቦች ጋር በቅጡ የተዋወቅሁት የቱኒዚያ አብዮት የተቀሰቀሰ ሰሞን ነበር፡፡ ስለ ቱኒዚያ እና ግብፅ አብዮቶች መንስኤ፤ አስፈላጊነታቸው  እና ውጤታማነታቸው ጃዋር ከፃፈው በተሸለ ገብቶኝ እና ተመችቶኝ ያነበብኩት መኖሩን እንጃ…
ከዛም በኋላ ጃዋር የሚሰጣቸውን ትንታኔዎች ባገኘሁት አጋጣሚ ሁሉ እሰማለሁ፡፡ ሰምቼም እስማማለሁ፡፡ ምን መስማማት ብቻ፤ የሆነ ቀን ጃዋር ምርጫ
ቢወዳደር ይምራኝ ብዬ የምመርጠው ሁሉ እስኪሆን ድረስ አክባሪው ሆኛለሁ…!
ከእለታት በአንዱ ቀን እኛ “በፌስ ቡክ አስተዳደር የኢህአዴግ ዋና የስራ ሂደት ባለቤት” የምንለው ዳንኤል በርሄ በአሁኑ ሰዓት በአልጀዚራ የሚተላለፈውን እባክችሁ ቅዱልኝ ብሎ ተማፅኖ ሲያሰማ “እኔ እንደ እናንተ አይደለሁም” በሚል “ሙድ” ልቀዳለት ወደ አልጀዚራ ጎራ አልኩ… የማከብረው ጃዋር በአልጀዚራ ስቱዲዮ ጉብ ብሏል፡፡ እውነቱን ለመናገር ጃዋርን ባየሁት ጊዜ ኖራ…  ብዬ አባቴ የሚያከብረው ሰው ሲመጣ እንደሚያደርገው በአክብሮት ከመቀመጫዬ ተነስቻለሁ…

እንግዲህ  ይሄኔ ነው፡፡ ኦቦ ጃዋር እስከዛሬ ሲናገር ይስማሙኝ ከነበሩት በተቃራኒው የማይስማማኝን ነገር ሲናገር የሰማሁት፡፡ የተረገመቺቱ የአልጀዚራ ጋዜጠኛ አንድ የተረገመ ጥያቄ ጠየቀችው…  ኦሮሞ ፈርስት ወይስ ኢትዮጵያ ፈርስት… አለችው… እርሱም ኦሮሞ ፈርስት አለ፡፡ ጃዋር ይሄንን የማለት መብት አለው፡፡ ኢትዮጵያዊነት በግድ የተጫነብኝ ነው ሲልም ተናገረ፡፡ ይሄንንም የማለት መብት አለው፡፡ እኔ ደግሞ መብቴን በመጠቀም፤ አንድ ውሳኔ ላይ ደረስኩ… ጃዋር ምርጫ ቢወዳደር አልመርጠውም፡፡ እንኳንም ቀድሞ ተወዳድሮ ጉድ አላደረገኝ አልኩ… (አልጀዚራንም እረገምኩ እንድንከፋፈል አድርጎናልና፤ ዳንኤል በርሄንም ረገምኩ አልጀዚራን እንድመለከት አድርጎኛልና፤ ጃዋርንም አሽሟጠጥኩ ሀሳቡ አልረባልኝምና!)
ጃዋርን ያሰብኩት ለክልሉ አስተዳዳሪነት ሳይሆን ለሀገሪቷ መሪነት ነበር፡፡ ታድያ ለቤተዘመዶቹ ቅድሚያውን የሚሰጥ መሪ አማራሪ እንጂ ምኑን መሪ ሆነው…  ለመሆኑስ የብሄርተኝነት ጥጉ የት ድረስ ነው…. ስልም… ሽሮሜዳ ደረስኩ… እናም የመጣው ምጣ ብዬ  አሽሟጠጥኩ!
ይለይልህ ብለው የጃዋርን ሌላ ንግግር ሰዎች ካለበት ፈልፍለው አሳዩኝ… ይሄኛው ደግሞ የባሰበት ነው፡፡  ጃዋር ባደገበት አካባቢ ዘጠና ዘጠኝ በመቶው ሙስሊም ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ሙስሊም ያልሆነ ኦሮሞ ቀና ቢል “በሜንጫ ነው አንገቱን የምንለው” አለን፡፡ ልብ አድርጉልኝ ጃዋር “ኦሮሞ ፈርስት” ብሎ አላቆመም ደግሞ “ሙስሊም ኦሮሞ ፈርስት” አለን ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እኔ እና ሌላው ዋቄፈታ ኦሮሞ ጃዋርን ይምራን ብለን መርጠነው ቢሆን ኖሮ እጣ ፈንታችን ቀና ስንል ሜንጫ ነበር ማለት ነው፡፡
አንድ ጊዜ ቤተሰባዊ ዝምድናውን ያስቀደመ ሰው ማብቂያ አይኖረውም፡፡ የምለው ለዚህ ነው፡፡ በደሉ የሁላችንም ነውና በደል የሌለባት ሀገር እንድትኖረን ሁላችን በአንድ ላይ ብንተባበር የተሸለ ነው የምለውም ለዚህ ነው…! “ሁላችንም ነፃ ካልወጣን አንዳችንም ነጻ አይደለንም” የሚለው የኦባንግ ሜቶ ንግግር የሚማርከኝ ለዚህ ነው፡፡
በኦነግ ትግል ምስረታ ወቅት ከመስራቾች አንዱ የነበሩት ሀጂ ሁሴን ሱራ፤ ትግላችንን ለሁሉም ኢትዮጵያውያን እንዲሆን፤ “ጭርቁምፈምቶታ ኡመታ ኢትዮጵያ” (የተጨቆኑ የኢትዮጵያ ህዝቦች) እንበለው እና በጋራ በደልን እንታገል ሲሉ ቀደምት የኦሮሞ ታጋዮችን ለማሳመን አጥብቀው ሲከራከሩ እንደነበር ስለኦነግ ሚጢጢ እውቀት ያለው ሁሉ የሚያስታውሰው ነው፡፡ እናም ይህ ሀሳብ በኦሮሞ ዘንድ አዲስ ሀሳብ አይደለም፡፡
በአሁኑ ጊዜ ያሉ ኦሮሞ ታጋዮች የቀድሞ ንጉሳ ንጉሶችን በመኮነን በኦሮሞ ህዝብ ላይ የደረሰውን በደል ሲዘረዝሩ ይሰማሉ፡፡ እውነቱን ለመናገር በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የአማራም የኦሮሞም የጉራጌም የትግሬም ገበሬ ደልቶት የሚያውቅበት ጊዜ አላነበብኩም፡፡ ከንጉሳውን ቤተዘመዶች ውጪ አብዛኛው ህዝብ ጭቁን ነበር፡፡ ለዚህም ነበር በእነ ሃጂ ሁሴን ሱራ ዘንድ “ጭርቁምፈምቶታ ኡመታ ኢትዮጵያ” የሚለው ሃሳብ የተወለደው፡፡
በአፄዎቹ ዘመን የተበደለው እና የተጨቆነው ኦሮሞው ብቻ እንኳ ቢሆን፤ እንደ ጃዋር የመሰሉት ምሁራን ያለፈውን ታሪክ ለታሪክ ፀሀፊዎች ትተው እነርሱ በሽሙጡም ሳይደነግጡ በሙገሳውም ሳኩራሩ ለወደፊቷ ኢትዮጵያ የሚበጀውን  የመቻቻል መንገድ በመቀየስ ታሪክ ቢሰሩ መታደል ነበር፡፡

ዛሬ በወዳጃችን ጃዋር ድረ ገፅ ላይ “በዲያስፖራ ያለውን የወቅቱን የኢትዮጵያ ፖለቲካ በማስመልከት በአውሮፓ የኦሮሞ ወጣቶችና የሴቶች ማህበራት የጋራ መግለጫ” የሚል ፅሁፍ ተመለከትኩ፡፡

በተለይ ደግሞ ይቺ አንቀፅ ቀልቤን ሳበችው፡፡
“እኛ በአውሮፓ የኦሮሞ ወጣቶችና የሴቶች ማህበራት በአሁኑ ወቅት በአልጀዚራ ላይ ቅድሚያ ኦሮሞ ነኝ በማለቱ ብቻ በፖለቲካ ምሁሩ ጀዋር ላይ የተከፈተውን የሀሰት ዘመቻ ማውገዝ ብቻ ሳይሆን ለመከላከልም በመገደዳችን ይህ አይነቱ አጼያዊ ዘመቻ እስኪያቆም ድረስ ከቅርብ ጊዜ በፊት ከሰላም ወዳድ የአንድነት ሀይሎች ጋር የጀመርነውን የቅርርብ ዲያሎጎችና የሀሳብ ልውውጦች በይበልጥ ልንገመግምው ወስነናል። ”
እኔ ጃዋርን ብሆን ኖሮ ይህንን ፅሁፍ በራሴ ድረ ገፅ ላይ አላትምም ነበር፡፡  ምክንያቱም ጃዋር የዚህ ማህበር አባል አይደለም እርሱ የሚኖረው አሜሪካ ነው፤ መግለጫው ደግሞ “በአውሮፓ  የኦሮሞ ወጣቶችና  የሴቶች  ማህበራት  ያወጡት ነው፡፡ የአደባባይ ሰው ሲሆኑ ትችትም ሙገሳም እንደሚመጣ የታወቀ ነው፡፡ ለሚሰነዘርብን ትችት በሙሉ ዘመዶቻችን መግለጫ እንዲያወጡልን ከመጋበዝ ራሳችን ነጥብ በነጥብ ለመመለስ መሞከር የተሸለ ነው፡፡
ማህበሩም ቢሆን ጃዋር ላይ የሚሰነዘር ትችት ኦሮሞ ላይ የተሰነዘረ አድርጎ በማየት “…ከሰላም ወዳድ የአንድነት ሀይሎች ጋር የጀመርነውን የቅርርብ ዲያሎጎችና የሀሳብ ልውውጦች በይበልጥ ልንገመግምው ወስነናል።” የሚል ትልቅ ፖለቲካዊ አንድምታ ያለው መግለጫ ማውጣቱ አስገራሚ ነው፡፡ ትልቅ ሀገራዊ ራዕይን አንድ ሰው ተነካ ብሎ እንደውም አንጫወትም ብሎ ለማቋረት መዳዳት ለማን እንደሚጠቅም ፈጣሪ ይወቅ…!
ጃዋር ወደፊትም ቢሆን ጥሩ ሲሰራ መመስገኑ መጥፎ ሲሰራ መተቸቱ የማይቀር ነው፡፡ ለትችቱ ምለሽ ለሙገሳውም ምስጋና መስጠት ያለበት ጃዋር እንጂ ዘመዶቹ አይደለንም፡፡
በአሁኑ ወቅት ትልቁ አሳሳቢ ችግር “ጭርቁምፈምቶታ ኡመታ ኢትዮጵያ” (የተጨቆኑ የኢትዮጵያ ህዝቦች) አለመተባበራቸው ነው፡፡ እኔ ብቻ ነኝ የተበደልኩት ብሎ የራስን ችግር ብቻ አግዝፎ ማየት እና ማሳየት የትም አያደርስም፡፡ (ብዬ አስባለሁ… ማሰብ መብቴ ነው! (በሌላ ቅንፍ ደግነቱ ይሄንን ችግር ሀገር ውስጥ ብብዛት አላየሁትም…))
ጎበዝ ለማንኛውም “በስጫው”ን ትተን  እስቲ ረጋ ብለን እንነጋገር…!
“በስጫ”… ማለት የአራዳ ብሄረሰብ ቋንቋ ሲሆን ትርጓሜውም ብስጭት ማለት ነው፡፡

No comments:

Post a Comment